Saturday 31 March 2012

“ ሞት የሚፈራ ሙት ”


 ሞት  የሚፈራ  ሙት                የጐንቻው!

ከሰው ተራ ወርዶ ክብሩ ሲንኳሰስ፤

የሰብ ስብዕናው ቃል-አቡ ሲጣስ፤

ማተቡ ግማዱ ከአንገት ሲቦጠስ፤

የእምነቱ መሰረት ታቦቱ ሲረክስ፤

ስርዎ ስሪቱ ተክሉ ሰው ሲፈርስ፤

የሞተው ሞት ፈርቶ ገዳዩን ሲያነግስ፤

ደመ ነፍስ ይኖራል የማይላወስ።



በእራሱ መቃብር የሚንከላወስ፤

ሞት ኑሮ ሆነና የማይኰስኩስ፤            

ወዶ እሚጋቡበት የአደባብባይ ዳስ፤

ተዝካር መጠራሪያው የሰርጉ ድግስ፤

በድን ያሸለበው ‘አስከሬኑ ነፍስ’፤

ሞትን ሙጥኝ ብሎ ኑሮ ዋቢ ቢስ፤

በግፍ በበደሉ እንዳይከሰስ፤እንዳይወቀስ፤

ዳኛና ህሊና ሙት እሚያስጨርስ፤

ሙቶ የሸፈተው ወንጀለኛ ነፍስ፤

ቢጠሩት አይሰማ ቢወጉት ደንደስ።



ጥቃት፤ስቃይ፤ሊያመልጥ ማደንዘዣ ፈውስ፤

የሞት ሞቱን ሙቶ፤ቁም እሚያስለቅስ፤

ኑሮን ሙቶ ሊሸሽ ምሽጉን ሲምስ፤

ትንሹን ሞት፤ሊሞት የሚልወሰወስ፤

ለቀን ጆሞራዎች እርካሽ በለስ፤

ምናል? ፍራት ገድሎ፤ጀግና ቢወደስ።



በአገር ባድባራችን ገዳማት፤ሲያፈርስ፤

የጻድቃኖች አጽም ቆፍሮ እሚምስ፤

‘ገነት ፍሬ’ አማሎ ‘ሸንኮራ እጽ-በለስ’፤

ለእሸትም አይበቃ ለአውድማም አይደርስ፤

ለአንዳችንም አይበጅ የባዕዳን ድግስ፤

‘ደም እየጠጁልን’ እንዳንጫረስ፤

አያቀባብርም በግፍ ሞት ሲነግስ።



ጥፋተኛው ልማት የሺህ ዘመንት ጦስ፤

ደን መንጥሮ ችግኝ ቀጠና ሊያውርስ፤

አረብ ጨው ያጋጠው ግራኙ መለስ

ቀኝ እጁ ‘አላሙዲ’ ‘የዮዲት’ ጥንስስ፤

የንጉሡ ጥዋ ሞልቶ አገር ሲፈስ፤

አድባራት ሊያከትም ገዳማት ሊያፈርስ፤

‘መስቀል የቆረጠ’ ‘ጨረቃው ንጉስ’፤

መነኩሴ ሊያጠምቁ ‘ዋልድባ’ ድፍርስ፤

ከቀያቴው አፈር ሥጋ ደም ልውስ፤

ሞትን ድል በመቱ መነኰሳት ነፍስ፤

በአምላክ አገልጋዮች በንቁ መንፈስ፤
ሞትን እንግደለው ምዕመናን ተነስ።   

የጐንቻው!    yegonchaw@yahoo.co.uk

No comments:

Post a Comment