Saturday 6 November 2010

ዳግመኛ ፈጣን ምላሽ የሚጠይቅ የኅብረት ጥሪ።

ዳግመኛ ፈጣን ምላሽ የሚጠይቅ የኅብረት ጥሪ።

የሀገራችንና የህዝባችን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሁናቴ ያገባናል በማለት ለሚከተታሉ ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን የሀገሪቷ የፖለቲካ ምኅዋር ይህን ይመስላል ብሎ ገለጣ ለመስጠት መሞከሩ ለቀባሪው አረዱት እንዳይሆንብን እንሰጋለን። ስለዚህም የታወቀዉን ጉዳይ ደግሞ በመዘርዘር አንባቢን አናሰለችም።
ከዚህ ቀደም እንደገለጽነዉ ሁሉ ሀገራችን በአንድ ፈላጭ ቆራጭ ግለሰብና ድርጅት መዳፍ ዉስጥ ገብታ ትሰቃያለች። ያልተቋረጠ የሲቃና የመከራ ጥሪም ታቀርባለች። እኛን ልጆቻንም ትማጸናለች።

በተለይም ከ2010 ምርጫ በኋላ መንግሥት በወሰደው ባፈጠጠና ባገጠጠ አምባገነናዊ እርምጃ ሁሉንም ዓይነት ተቃዋሚዎች “ወግዱልኝ” በማለት በመንግሥት ተብዬዉም አፈራረጅ ህጋዊ ሆነ ህገ ወጥ በሰላም የሚታገል ሆነ በጠብመንጃ ሁሉን ተቃዋሚዎች አንድ ናችሁ ብሏል። አንድም የሚያጠራጥርም ሆነ የሚያፈናፍን ቀዳዳ እንዳይኖር በእብሪት ተወጥሮ ዘግቶታል። በሁሉም ተቃዋሚ ኃይሎች ላይ መሠሪ ሴራዎችን መሸረቡንና የባለጌ ዱላውንም መሠንዘሩን ቀጥሏል። ከእንግዲህ የቀረው የህብረትና የህብረት ትግል ብቻ ነዉ ብለን እናምናለን። ይህን የምንለው ያለበቂ ምክንያት አይደለም፤ ይህን የምንለው ይህ ጥያቄ ሕዝብ አጠንክሮ እየጠየቀው ያለ ጥያቄም በመሆኑ ነው። ለነገ የማይባል የሕዝባችን ጥያቄ ነው!! ታዲያ ይህን የሕዝብ ጥያቄ በበቂ ስንመልስ ነው ሕዝቡ ዳር እስከዳር አብሮን ሊሠለፍ የሚችለው። ስለገዥው አምባገነን ግለሰብና መንግሥቱ ምንነት፤ በሕዝቡ ላይ ስለሚፈጽሙት ግፍና በደል፤ ስለመብት እጦትና ጥሰት፤ ስለድንበር መሬታችን ለባዕዳን መሰጠት፤ ስለ ለም የእርሻ መሬት ለባዕዳን ስለመቸብቸቡ፤ ስለሀገራችን ሉዓላዊነት መደፈርና ክብርዋ መዋረድ፤ የዘር ጥላቻ በመራገቡ ስለሀገራችን ወደመፈራረስ አደጋ መገፋት፤ ስለከፋ ድህነት ዳር እስከዳር መስፋፋትና ስለናጠጡ ጥቂት ሃብታሞች ቅንጦት፤ ስለ ባዕዳን ጣልቃገቦች ጎጂ ሚና፤ … ወ.ዘ.ተረፈ እየተናገርን ይህንን ሁኔታ በኅብረት ትግል እናስወግድ ሲባል ልናመናታ አይገባም እንላለን።

ከዚህ ቀደም ባሰራጨነዉ “ፈጣን ምላሽ የሚጠይቅ የኅብረት ጥሪ” ላይ ሃሳባችንና እንዲሁም ይጠቅማሉ ያልናቸዉን ሀገራዊነትንና ዲሞክራሲያዊነትን እኩልነትን የሚያንጸባርቁ አራት ነጥቦች አቅርበናል። ከዚህ ቀጥሎ በመጀመሪያው ጥሪ ላይ የቀረቡትን ነጥቦች፥ መሰረታዊ እምነታችን ስለሆኑ፥ ማስገባት ተገቢ ይመስለናል።

፩. በኢትዮጵያ አንድነትና የግዛት ሉዓላዊነት ላይ ግልጽና የማያወላውል ጽኑ እምነት መያዝና ማሳደር
፪. በየድርጅቶች ውስጥና በምንሰባሰብበት የኅብረት ማዕቀፍ ዉስጥ ዴሞክራሲያዊ አሰራርን ለማስፈንና በአገራችንም የሕግ የበላይነት እንዲኖር ጸንቶ መታገል
፫. በኢትዮጵያ ሕዝብ መካከል ምንም ዓይነት አድላዊነት እንዳይኖርና ሁሉም በሕግ ፊት እኩል ዜጎች መሆናቸዉን ማመንና በተግባርም ማስረገጥ
፬. የህወሓት/ኢህአዴግ መንግሥትና ሥርዓት የአፈናና የጭቆና ሥርዓት በመሆኑ መለወጥና በዴሞክራሲያዊ አስተዳደር መተካት እንዳለበት ማመን

ለመጀመሪያ ጥሪያችን ከበርካታ ሀገር ወዳድና ከዴሞክራቲክ ግለሰቦች በጎ አበረታችና ጠቃሚ ምላሾች አግኝተናል። በጣም ገንቢ የሆኑ ምክሮችም ለግሰዉናል። ከሁሉም በላይ የተጀመረውን የኅብረት ምስረታ ጥረት ከግብ ለማድረስ በሚደረገው ታላቅ ተግባር ላይ ተባባሪነታቸዉን ገልጸዉልናል። ሁሉንም ከልብ እናመሰግናለን። በጀመሩት ቀና ጎዳናም እንዲቀጥሉና አብረን የምንችለውን ሁሉ እንድናደርግ እናሳስባለን። እስከዛሬ ድረስ ጥሪውን አግኝተውም ሆነ ስለ ጥሪው ሰምተው ለጥሪው አዎንታዊ መልስ ያልሰጡትን ወገኖች፤ በተለያየ መልክና ደረጃ የተሰባሰቡትንም ሆነ ገና ያልተሰባሰቡትን፤ ይህንን ሀገራዊ ተግባር እንዲቀላቀሉና የበኩላቸዉን እንዲያደርጉ በአክብሮት ወገናዊ ጥሪ እናቀርባለን።

ለጥሪያችን በጎ ምላሽ በመስጠት፥ በኅብረት ምሥረታው ተግባር የባለቤትነት ድርሻችሁን በመውሰድ አብሮ ለመጓዝ ለወሰናችሁ ድርጅቶች አክብሮታችንን እንገልጣለን። ለምትቀርቧቸዉና ለምትግቧቧቸዉ የመሰባሰቡን ዓላማ በማስረዳት ኢትዮጵያዊያን በአንድ ጥሩ ውጤት ሊያመጣ በሚችል የአንድነት ሃይሎች ጥላ ሥር ይበልጥ እንድንሰባሰብ ጥረታችንን እንቀጥል።

ዛሬም እንደ ትላንትናው ለሀገር ወዳዱና ዲሞክራሲያዊ ለሆነው ኢትዮጵያዊ ሁሉ ጥሪያችንን እናድሳለን። አንዳንዶቻችን በነጠላና በየግላችን የምናደርገው ጉዞ ዉጤት ያመጣል ብለን ብናስብም እንኳ እስካሁን ያለው ተሞክሮ የሚያስተምረን ሃሳብንና ኃይልን በአንድነት አስተባብሮ ከመታገል የተሻለ አማራጭ እንደሌለ ነው። ሕዝቡም በሙሉ ልብ ሊሳተፍ የሚችለው ያኔ ነውና!!

ስለዚህም የጋራ እናታችን የሆነችው ኢትዮጵያ በጭንቅና በመከራ ሲቃ ተቀስፋ ተይዛለች። እኛም ልጆቿ ጥሪዋን በመቀበልና እምባዋንም በማበስ አቤት እንበላት።

አድራሻችን
 ኢ--ሜይል-- consult4eth@gmail.com
 ቴሌፎን ---
 ከአውሮፓ ሲደወል 0039/329-784-6515
 ---ከአሜሪካና ካናዳ 011/39/329-784-6515

No comments:

Post a Comment