Friday 9 December 2011


የጐንቻው !

ወዮላቹህ፤የቀን ጅቦች ሳታስቡት፤መሸባቹህ፤             

ሕዝብ መሽጓል በዋሻቹህ፤መሸሸጊያም የላቹህ፤

አጥንት ነካሽ ‘የቄራ ውሾች’፤ተራብታቹህ፤

ስትጮሁ ለከርሳቹህ፤የሕዝብ እሮሮ ነቅፋቹህ፤

ምንደኞቹ፤ሕዝብ-አገር በቅርጫ ያረዳቹህ፤                       

ምረነኛ፤ጉጅሌዎች ‘ስጋ-በስጋ’ የደለባቹህ፤

እርም እምነት የበላቹህ፤በዘር በደም ተሳክራቹህ፤

የወየናቹህ፤በእብሪት በጥጋብ ተወጥራቹህ፤

ጎኁ ቀዷል፤ሊያባራ ነው ምጣችን፤ምጣታቹህ፤

በዓለም መስትዋት የበቀል ቁና ፍዳቹህ፤

ተቆልሏል፤አበሳቹህ፤ልክ ያለፈ ስንክሳራቹህ            

እንዳይነቱ ግብራቹሁ፤የአደባባይ ፍጻሜያቹህ፤

እንደ ቱኒዙ፤ግብጽ፤ሊብያ፤ ነው እጣ ፋንታቹህ።



በቁስላችን እሾህ የምትሰዱ፤የወያኔ፤ቁንጮዎች፤

እሾሁ ሲነጣጠር ወደ አይናቹህ በሚሊዎኖች፤

በሞተ ሰዓት የሟርት ሽብር ከበሮ ደላቂዎች፤

ስንቱን ክቡር ዜጋ ጭቃ ቀቢ፤የአገር ጉድፎች፤

የምታስሩ፤የምትገርፉ፤ወንድም፤ እህት፤ወላጆች፤

ቴሬሪስት፤ድራጊስት፤አልካኢዳ፤አልሸባብ ’ ክሶች፤

የወንበዴ ታርጋ ለጣፊዎች፤ምህረት የማትሹ፤ቂሎች፤

‘ዝና-ስሙ’ ለናንተ እንጂ እድራችሁ አጥፍቶ-አጥፊዎች፤

በፓርላማ፤በ‘አረንጓዴው አደባባይ’፤ባዶ አኬልዳማዎች፤

አይሰሩምና የ‘ጋዳፊ’ መፈክሮች፤የቅጥፈት ስልቶች፤

ወዮላቹህ! ፍጻሜያቹህ፤ለምህረትም-ለተረትም አይመች።



በግንባራችን የደቀናቹህ የወያኔ ‘ጠብ-አንጋቾች’፤

ቃታ ከሳበ ጣታቹህ ዛሬም ልትገድሉ የሕዝብ ልጆች፤

ቅጽፈት ናቹህ፤የሰማይ የምድር ዘላለም ሙቶች፤ 

በህግና በፍትህ ስም የምትቀልዱ ዳኛ ጠበቆች፤

የምታንገላቷቸው፤የትውልድ የሰላም አንኳሮች፤

የአገር-ሕዝብ አውራ፤ንግሥት ናቸውና እስረኞች፤

ዛሬ አስተውሉ፤እንዳይነድፏቹህ ኋላ ‘ሆ!ብለው ንቦች።                  

የኔሰው ገብሬ፤ የዳውሮ ዋርካው፤ ምሁሩ ሻማ፤በራሱ ለቆ፤

የጋረደንን የፍርሃት ድባብ በኃይዎቱ፤ውጋገን ለኛ፤ፈንጥቆ፤

አይሆንምና ደመ-ከልብ ቃል በምድር፤ቃል በሰማይ፤ተሰንቆ፤

እንዲጧጧፍ ትግላችን በየጉልቻው፤አናዳጆችን ማግዶ፤አስጨንቆ።



ወዮላቹህ! ወያኔዎች፤‘ሙባረክን’፤‘ጋዳፌን’ ያዬ፤

እዝነ-ልቦናቹህ፤ካልፈራ፤ዓይነ-ህሊናቹህ፤ካላዬ፤

እንደ ደመራ ልትሞቁን ከዳዳቹህ፤ሕዝብ ሲቃጠል እየታዬ፤

ኢትዪጵያዊ በግፋቹሁ እየጋዬ፤ንስሃቹህ፤ከዘገዬ፤

ወዮላቹህ፤ወገን ጥዶ ያብስላቹህ መስቀል ከቦ እያጋዬ።





እነሆ፤የተዳፈነው እሳት፤ተቀጣጥሏል፤ሰደዱ፤

የተቆጡት፤የቆረጡት፤በየማዕዘኑ፤ሊነጉዱ፤

‘የፎጡን’፤ግንብ፤ሊንዱ፤ቅቦችን ሊያስርዱ፤

ወዩላቹህ!፤ሕዝብ ሃያል ነውና የቁጣ ክንዱ፤

መውረጃቹህ ይኸኔ ነው፤ብትሰሙ፤ብትዱ፤

በግብጽ ‘ሙባረክ’፤ሕዝብ የናቁት፤ ‘አንበሳ’፤

እንደ ጨርቅ አልቀው ሲጓጓዙ በሳንሳ፤

አልጋ ወራሾች፤ተሳስረው ከንጉሱ፤የቁም እሬሳ፤

የሊቢያው ‘ጋዳፊ’፤ሕዝብን በስድብ አርክሰው፤

ተያዙ፤አይጥ ጉድጉድ ተወትፈው፤በቆሻሻ ማኩሰው፤

የሞት-ሞት፤ ሞቱ፤ያልማሩትን ሕዝብ ምህረት ለምነው፤

ወዮላቹህ! ወያኔዎች፤በደመ ነፍስ፤ያላቹህ፤

ቅንጣት እምነት ካላቹህ፤በደል ጥፋታቹሁን፤አምናቹህ፤ 

ግቡ ንስሃ ፤ባለቀ ሰዓት ሽብር አሳሩን ትታቹሁ።


 





ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነፃነት መስዋዕቱ፤ ሰማዕታቱ የኔሰው ገብሬ!  ዳውሮ-ዋርካ
በወያኔ በደልና ግፍ ተንገብግቦ ሕይዎቱን በአደባባይ ለወገኑና ለሐገሩ መስዋዕትነት በቁሙ እሳት አጋይቶ የመጨርሻውን የሕይዎት ዋጋ ለከፈለው ጀግናው ወጣት ምሁር የኔሰው ገብሬ መታሰቢያ ትሁንልኝ።

እነሆ አምላካችን ነፍሱን ይማርልን፤ ለወላጅ ቤተሰቦችም ጽናትን ለመላው ኢትዮጵያ ሕዝብ በሙሉ ቆራጥነትን፤ እሻለሁ፡ ወንድማችን ደመ-ከልብ ሆኖ እንዳይቀር መልዕክቱን፤ተቀብለን መስዋዕትነቱን ግብ እናድርስ፡ የትግሉን ሰደድ አቀጣጥለን፤ለድል እንብቃ፤የሰማዕታቶቻችንን ነፍስ ይማር።

የወጣቱ ምሁር የኔሰው ገብሬ እንደ ቱኒዚያው መሐመድ ቡዋዚዚ ለዓረብ ሕዝብ ተምሳሌ ሆኖ በርካታ ህሕዝቦንችንና አገራትን ከዘመናት ከባርነት ያልተለየ አገዛዝ ነፃነት እንዳቀዳጀና እያቀዳጀም እንዳለው ሁሉ፤ የቆራጡ ወንድማችን ገድልም ለኛ ለኢትዮጵያዊያን ብቻ ሳይሆን እንደኛ በጨካኝ፤ገዥዎቻቸው ስር ለሚማቅቁ፤ ጥቁር አፍሪቃዊያን ወገኖቻችን ሁሉ፤የነጻነት ቀንዲል ይሆናል።

የጐንቻው!      yegonchaw@yahoo.co.uk










Thursday 8 December 2011

የብሶት ምጥ!


የጐንቻው!

ሃያ ዘመን ሕዝብ ያረገዘው፤ውል እድሩ፤ የብሶት-ምጥ፤

የተጣባ ከውስጣችን፤ሕመማችን ሥር የሰደደ አለቅጥ፤

ሲያስጨንቅ ሲያስጠብበን፤የኖረ፤ሲያንቆራጥጥ፤

ስንድህ በእንብርክክሽል’ በውስጣችን  ሲገላበጥ፤

የሁለንተናችን ግልግል ውስጠ-ደማሚት እበጥ፤

አልፈነዳ፤ አልወለድ፤ ብሎ፤ወገን በሕቡ፤ሲናጥ፤

በቁርኝት አሳስሮን፤እጅ መዳፉችን፤ሲላጥ፤

ግፍ፤ቆሰቆሰው፤ሊያቀጣጥሉን፤‘የቀኑ ሰዎች’ በፈሊጥ፤

ስም እያዋሱን ‘ሞግሸነት’ መዘባበቻ፤ሽብር ስላጥ፤             

ባጐረስን እየተነከስን፤ሲገፉን፤ኖረው፤ከድጥ ወደ ማጥ፤

‘ብሶት ወለደን’ ብለው፤ያነገሱት፤የእንግዴ-ልጅ ምጥማጥ፤

የትውልድ ተስፋ የምያመክኑ፤ለእሳት ዳረገውን ለረመጥ፤

በስለን አረናል፤በየጐጇችን፤እየተቃጠለን፤ሳንገላበጥ።

Wednesday 7 December 2011

አሻቅበው ቢተፉ፣ ተመልሶ ባፉ!

ወንድሙ መኰንን

አኬልዳማ (חקל דמא)ጥሬ ቃሉ የተገኘው ከአርማያክ ቋንቋ ነው። አርማያክ ጌታ እየሱስ ክርስቶስ በዚህች ግፍ በሞላባት ምድር ላይ ሲኖር ይናገርበት የነበረ ቋንቋ ነው። ዓለም ይኸን ቃል የወሰደው ከመጽሐፍ ቅዱስ ነው። የሐዋሪያት ሥራ ም. ፩ ቁ. ፲፱ እና የማቴዎስ ወንጌል ም፡ 27 ቁ፡ 8 ላይ ቃሉ ተጽፎ እናገኘዋለን። ነገሩ እንዲህ ነበር። ያኔ ይሑዳ የተባለ ከሀዲ ጌታን በ30 ብር (30 pieces of silver) አሳልፎ ሽጦት ነበር። ልክ የኢትይጵያን መሬት፣ ዛሬ ለባዕዳን እንደሚቸበችበው፣ ከሀዲ የወያኔ መንጋ እንደማለት ነው። ጌታ በግፍ ከተሰቀለ በኋላ፣ ታዲያ ይሑዳ ተጸጽቶ 30 ብሯን መልሶ “ተቀበሉኝ” አለ። ቀጣፊ! ከፋዮቹ፣ የደሙ ዋጋ ወደ እነሱ እንዳይመጣ ሰግተው፣ በዚያ ገንዘብ የአንድ ሸክላ ሠሪ መሬት ለእንግዶች መቃብር ይሆን ዘንድ ገዙበት። መሬቱንም አኬልዳማ ተባለ። ትርጉሙም፡ “የደም ምሬት” ማለት ነው። ጸረ እግዚአብሔር የሆነ ሌባ ወያኔ ቃሉን ከማያምንበት መጽሐፍ ቅዱስ እንደልማዱ ዘርፎ፣ ተጨማለቀበት! ለነገሩስ፣ “ሰይጣን ሀጃውን ለሟሟላት ሲከጅል፣ አንዳንድ የሚበጁትን ቃላት ከመጽሐፍ ቅዱስ ይጠቃቅሳል” ማለት ይኸው አይደል!

ወንጀል ፈጻሚው፣ ሰላማዊውን ሰው መልሶ ወንጀለኛ አድርጎ ድራማ ወይም ትርዒት መሥራትን ወያኔ የተካነበት ዘዴ ነው። አሳሪው ዕብሪተኛ የወያኔ መንጋ፣ ሕዛባችንና ወገናችን ላይ የሚያደርሰው ሰቆቃ አንሶት፣ አሁን ደግሞ የግፍ ግፉን፣ ሰው አስሮ እያሰቃየ፣ በስቃይ ብዛት ተገደው መሣሪያ በግንባራቸው ላይ ተደግኖ ሰለባዎቹ ስቃዩ እንዲቀልላቸው በሚለፈልፉት ላይ እየተመሠረተ እራሱ ሊዝናናበት (ተሳስቶ ዕውነትም ቢናገር የሚያምነው መቸም የለምና) ትርዒት መሥራት ከጀመረ ውሎ አድሯል። አሁን ደግሞ ይባስ ብሎ “አኬልዳማ ” የሚል ሶስት ክፍል ድራማ ሠርቶ ቅስማችንን ሊሰብር፣ በኢትዮጵያ ተሌቪዥን ለቀቀው። “እንደልማደህ ቅደድ” በሉት እንግዲህ! ትንሹን ውሸት ወያኔ እንዲሸፍነው፣ ሌላ ያንን የሚያሳንስ ትልቅ ውሸት መዋሸት ነበረበት። ትንሹን ወንጀሉን ወያኔ የሚያቀለው ሌላ ግዙፍ ወንጀል ፍጽሞ የበፊተኛውን ወንጅሉን በማደንከይ ነው።



ክፍል ፩፡ የእምዬን ወደ አብዬ

በክፍል ፩ ድራማ ወያኔ ከዚህ በፊት እራሱ በደኖ ላይ በፈጸመው የወገናችንን ጭፍጨፋ ወንጀል ያላንዳች እፍረት በሚያመቸው መንገድ እንደገና ከልሶ (ኤዲት አድርጎ) አቀረበ። አንድ ጥሩ ማስጠንቀቂያ ግን በአንድ ቆንጆ ድምጽ ባላት ሴት ንባብ ይጀምራል። እሱም፤ “ይኸ ፕሮግራም ከ13 ዓመት በታች ያሉ ሕጻናት እንዲያዩት አይመከርም” የሚል ነው። ደግ ብላለች። ይኽች ብቻ ናት ከዚያ ሁሉ ቆሻሻ የምትለቀም ደግ ነገር። ለዚያውም ቆሻሻ ውስጥ ለቅመው በልተው ሊሚያድሩ ሕጻናት ከታሰበ ባለት ነው። ለታሪክ ተመዝግቦ መቀመጥ አለበት። http://www.diretube.com/ethiopian-documentary/akeldama-part-1-video_25cf45af1.html ጉድ በሉ ጃል! ገደል ውስጥ እጃቸው ከኋላ ታስሮ ከነነፍሳቸው ተወርውሮ የተፈጠፈጡት ሕጻናት፣ ሴቶች፣ ወንዶች ሬሳ በገመድ እየተንጠለጠለ ሲወጣ ይታያል። ከተንቀሳቃሽ ስዕሉ በታች የተጻፈው “ኦነግ የፈጸመው ወንጀል” የሚል ነው። እ?? አይ አንተ አምላክ! አይ አንተ ፈጣሪ! ኦነግ በዚያን ጊዜ ከወያኔ ጋር የጊዜያዊ መንግሥት አካል አልነበር? ታዲያ ወያኔ ያኔ ምነው ሕግ አላስከበረ? የያኔው የወያኔ ጠቅላይ ሚኒስቴር፣ የአሁኑ ጴንጤ፣ ታምራት ላይኔ አልነበር፣ “ሽርጣም እያለ ይሰድብህ የነበርዉን አሁን በለው” እያለ ሕዝብን በሕዝብ ላይ ሲያነሳሳ የነበረው? የአዛኝ ቅቤ አንጓች! የነዚያን ንጹሀን ሰዎች ደም ደመ-ከልብ ሁኖ እንዲቀር ማን ነበር አድበስብሶት ያስቀረበት!? ያኔ አንዲት ቃል ያልተነፈሰው ይኸ የገዳዮች መንጋ፣ ዛሬ ያንን እራሱ የፈጸመውን ወንጀል ሌላ አካል እንደፈጸመው አቀነባብሮ ሲያቀርብ፣ ማንን ለማታለል ነው? ለነገሩ፣ አቶ ዲማ ነገዎ የተባሉ የኦነግ የአመራር አካል በኢሳት ቀርበው እንዳስረዱን ከሆነ፣ በጊዜው ነገሩ በነጻ አካል እንዲጣራ ኦነጎች ጠይቀው፣ ወያኔ እንዳዳፈነው ነው።ታዲያ ዛሬ ወያኔ እራሱ የፈጸመውን የአረመኔነት ወንጀል፣ እንደመሣሪያ መልሶ ሲጠቀም ማንን ለማታለል ፈልጎ ነው። ምነው እኛን ቤተሰብ አልቆባቸው የሚያለቅሱትን ንግግር ሙሉ በሙል አላውጣም ይኸ ጋጠ-ወጥ ቀጣፊ! “ቤተሰቤን ያስጨረሰው መለስ ዜናዊ ነው” አልነበር ያሉት? ያንን ቆርጦ ማውጣትን ምን አመጣው? ይኽ ሁል ሸንካላ ዝባዝንኬ፣ እነ ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን፣ ርዕዮት ዓለሙን፣ የአንድነቱን ወጣት መሪ አንዱዓለም አራጌን ... ወዘተ በግፍ ማሠሩን ለመሸፈን መሆኑ ነው? ትልቅ ውሸት ተብሎ ካልተተረጎመ፣ ምን ፋይዳ ሊፈይድለት ነው? ይኸን ጉዳይ፣ አርቲስት ታማኝ በየነ በጥሩ ሁኔታ በኢሳት ቴለቢሽን ላይ ሂዶበታልና፣ እዚህ ላይ ገታ አድርጌ እንድታዳምጡ አንባቢን እጋብዛለሁ። አምላካችን ይባርክኽ፣ ታማኝ!

http://www.youtube.com/watch?v=PUMRnjrKL0c

የመለስ ዜናዊ አገዛዝ የፋሽስት አገዛዝ መሆኑ ጸሞቀው ሀቅ እኮ ነው። መለስ ዜናዊ እኮ በዘር ማጥፋት ተወንጅሏል። በጋምቤላ፣ በዚሁ አሁን ሊያታለለን በሚሞክረው በበደኖ እልቂት፣ የአርባ ጉጉ ጭፍጭፋ፣ የወተር፣ የእንዳየሱስ፣ የኦጋደን የአንድ መንደር መንደደድ በመሳሰሉት ዓለም-አቀፍ ፍርድ ቤት፣ ፋይል እንዲከፍት የጀኖሳይድ ዎትች ፕረዝደንት ዶክተር ግሪጎሪ ስታንተን አመልክተው ውጤቱን እየተጠበቀ እኮ ነው። ያውላችኋ! http://redsea1.websitetoolbox.com/post/Tigray-The-Looming-Genocide-By-Dr.Gregory-Stanton-5558857

አሁን ወያኔ የእምዬን ወደ አብዬ ማዞሩ፣ ያ እንዲደመሰስለት ይኾን? መለስ ዜናዊን የሚጠብቀው የሊቢያው ጋዳፊ ዕጣ ፈንታ እንደሆነ ማወቅ አለበት። አንድ “ውኒጥ-ዝኒጥ” የለም! “በነጻ ገቢያ ተሽጦ ገንዘብ የሚያወጣ” የተባለለት ጭንቅላት፣ እንደጋዳፊ የተፋትን መልሶ በአፉ እስኪውጣት ድረስ አያስቀርለትም።

ክፍል ፪፡ የሌባ ዓይነ-ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ

የወያኔን ቅጥፈት ባየሁ ቁጥር፣ ሁሌ ትዝ የሚለኝ፣ አንድ ፒያሳ ያጋጠመኝ፣ ከዚህ በፊት የተረኩላችሁ የሌባ ገጠመኝ ነው። ልድገምላችሁ። ከጓደኛዬ ጋር ወደ አራት ኪሎ ለመሄድ ታክሲ አቁሜ ልሳፈር ስል፣ አንዱ ጎረምሳ ገፍትሮኝ፣ “ታክሲ፣ መርካቶ!” ብሎ ጮኸ። መገፍተሬ ሳያንሰኝ፣ አንደኛው እጁ እኪሴ ውስጥ ግብቶ ሲበረብኝ አገኘሁት። በደመ-ነፍስ፣ ባለኝ በሌለኝ ኃይሌ ተጠቅሜ የሞት ሞቴን እጁን ከኪሴ አውጥቼ ሳይታወቀኝ ጠመዘዝኩት። ታዲያ የወያኔው ብጤ፣ ዓይን-አውጣ ሌቦ ትኩር ብሎ ዓይኔን እያየ በንቀት ፌዝ፣ “በቃህ ነቅተሀል! ልቀቀኝ! የማነው ገገማ!” ብሎኝ አረፈው። ትልቅ ጥፋት ያጠፋሁ መስሎኝ ተደናብሬ ለቅቅኩት። እየሰደበኝ ሄደ። ወያኔ ማለት ከዚያ ሌባ የባሰ ዓይን አውጣ ነው። አያድርስባችሁ! እስቲ ይኸኛው የውሸት ቋጠሮውን በሁልተኛው ክፍል አብረን እናፍተልትለው። http://www.diretube.com/ethiopian-documentary/akeldama-part-2-video_30d42597c.html

ኤዲያ! “ዕድሜ ዘልዛላው” አሉ እኚያ አሮጊት! “የሞኝ ለቅሶ መልሶ መልሶ” ይባላል። ይኸ ሁለተኛው ክፍል፣ ከዚህ በፊት “ሲሉ ሰምታ ...” በሚል ርዕስ የተቸሁበትን ትርዒት ነው የተደገመብን። የያኔው ትችቴ ኢትዮሜዲያ፣ በአዲስ ቮይስ፣ በኢኤመኤፍ እና በዓባይ ሜዲያ ቁጥሩን የማላውቀው ሕዝብ ሲያነበው በራሴ ብሎግ ብቻ ከ10 ሺ ሰው በላይ አንብቦታል

 (http://wondimumekonnen.blogspot.com/2011/09/blog-post.html)።

ብዙ ስድብም ከወያኔ ቡችሎች ቀምሼአለሁ። እዚያ ላይ መጨመር የምፈልገው አለኝ። ወያኔ በሻዕቢያ ተጠፍጥፎ ተሠርቶ፣ ተዘርቶ፤ ተኮትኵቶ አድጎ፣ ለሥልጣን የበቃ ድረጅት ነው። ሻዕቢያ አባቱም እናቱም ነው። ዛሬ ከሻዕቢያ ጋር ተነጋገራችሁ ብሎ ሌሎችን መኰነኑ፣ የሌብነት ሌብነት ነው። እነዚህ፣ በአንድ አልጋ ካልተኛን፣ ባንድ ማዕድ ካልበላን፣ በአንድ ጉድጓድ ካልሸናን ብለው ሥቃያችንን ያበሉን የኢትዮጵያ ጥንድ ጠላቶች አልነበሩምን? ለመሆኑ፣ ከዚህ በፊት ማን ነበር፣ ከሻዕቢያ ጋር ኢትዮጵያን የወጋት! ያደማት! ያለባሕር በር ያስቀራት! ማን አባቱ ነበር፣ ኢትዮጵያን አኬልዳማ ያደረጋት! ከሀዲ የወያኔ መንጋ አልነበረም ወይ! የማን እናት ናት ለምሆኑ አሥመራ ድረስ ሂዳ ለኤርትራ ነጻነት ድምጽ የሰጠችው? ሰሞንን ከዳዊት ከበደ መጣጥፍ አንድ ነገር ተማርኩ። ምን ይላል መሰላችሁ?

“ሆኖም በኣዲ ቛላ፣ ኤርትራ ውስጥ ተወልደው ያደጉት የመለስ ዜናዊ እናት ወ/ሮ አለማሽ ገብረልዑል፤ በምኒልክ ቤተ መንግስት ውስጥ ሲደበቁ፤ ሌሎች ኤርትራዊያን ግን “የአይናቸው ቀለም አላማረንም” ተብለው ተባረሩ። ከነዚህ ተባራሪዎችም መካከል አድዋ ውስጥ የነመለስ ዜናዊ ጎረቤት የነበሩት ሴትዮ፤ “እኔ ለኤርትራ ድምፅ የሰጠሁት ከአለማሽ ጋር አብረን ሄደን ነው። እሷ ኢትዮጵያ ውስጥ እየኖረች እኔ መባረር የለብኝም።” ብለው እያለቀሱ ቢለምኑም የአይናቸው ቀለም አላማረምና እያለቀሱ የአድዋ ከተማን ተሰናበቱ።”

ለመሆኑ ከወያኔ የበለጠ፣ የሻዕቢያ ደንገጡር በዚህ ምድር ላይ አለ? ከመለስ ዜናዊ የበለጠ፣ የሻዕቢያ ጠበቃ ከየት ሊመጣ ነው? እኛም እናውቃለን። እነሱም ያውቁታል። እኛ እንደምንውቅባቸሁ እነሱም ያውቁታል። ለመሆኑ ማንን ለማደናገር ነው? ለምንኛውም፣ የሚከተሉትን ከህደቶች ለታሪክ መዝግባችሁ አኑሩት! አቦይ ሰበሀት የተባለው ወያኔ፣ “የኤርትራ ነጻነት አደጋ ላይ የሚወድቅ ከሆነ፣ ኢትዮጵያን ብትንትኗን አውጥተን ለኤርትራ ነጻነት እንደገና በረሀ እንግባለን” ያለበት ከነድምጹ ያውላችሁ! http://www.aigaforum.com/audiovideo.html። የካሀዲ የልጅ-ልጅ ከሀዲ መለስ ዜናዊ በኤርትራ የ“ናጽነት” ቀን ተግኝቶ፣ “የጠላቶቻችሁን አከርካሪ ላንዴና ለመሸረሻ ጊዜ ሰብረነዋል” ብሎ ሲቃ እየተናነቀው የተናገረው ከነድምጹ ያውላችሁ። http://www.fettan.com/Documents/Harvesting_of_Planted_Ethnic_Discord.pdf.

ትግርኛ ከሆነ የሚቀናችሁ ትግርኛውም ይኸውላችሁ!

http://www.fettan.com/Documents/Harvesting_of_Planted_Ethnic_Discord.pdf

እና የሻዕቢያ የጓዳ ገረድ ማን ሁኖ ነው እኛኑ መልሶ ልብ የሚያደርቀው? በየትኛው ሞራሉ ነው ማንንም በሻዕቢያ አሸክርነት ሊኮንን የሚችለው? ከወያኔ የበለጠ የሻዕቢያ ተላላኪ ነበረ ወይ?! አይኖርም! አለቀ! ደቀቀ! ዕውነቷ ይኽቺ ናት! በነገራችን ላይ ወያኔ፣ እኔ ከተጣላሁት ሰው ጋር ለምን ተነጋገራችሁ ብሎ የሚኮርፍ አባ ጉልቤ ታዳጊ ሞልቃቃ (bully boy) አይመስላችሁም? ስለአሸባሪነት ከተነሳም፣ ከወያኔ የበለጠ አሸባሪ ከቶ ከየት ሊመጣ ነው?። ዛሬ የሽብርተኝነትን ሕግ የቀዳሁት ከአሜሪኖቹ ነው የሚለን አሸባሪ፣ ስለሱ አሸባሪነትስ፣ በአሜሪካኖቹ የሚሉትን ያውቅ ይሆን? ይኸውላችሁ ሀቁ!

http://www.start.umd.edu/start/data/tops/terrorist_organization_profile.asp?id=4287

ወያኔ ጭርሶ ተጨማልቋል። ጭምልቅ ብሏል! አንድ ወራዳ ሥራ ይሠራና ሰው “ግድ! ጉድ!” ሲል ከዚያ የባሰ ወራዳ ሥራ ሠርቶ ነው ነው የመጀመሪያውን ግዙፍ ውራዳውን ሥራ በቀጣዩ ሱፐር ግዙፍ የቀድሞውን ውርደት የሚያደንከው። “ኢህአዴግ መስማትና ማየት የተሳነው መንግሥት አይደለም!” እያለ መልስ ሲቀባዥር ሰምተነዋል ትርዒቱ እዚህም ይደግማል። አንደኛ መስማትና ማየት የተሳናቸው እዚህ ላይ “እሪ” ማለት አለባቸው። ሰብአዊ መብታቸው በአንድ አባ ጉልቤ ጠቅላይ ስቃይ ተደፍሮባቸዋል። ሁለተኛ፣ እነ እስክንድርናና የአንደነትን መሪዎች ለማሰር ሲነሳሳ ያደረገው የፓራላም ድንፋታው ገና ለግና ሕግን ያለቦታው እንደሚጠቀም (abuse of power) እየነገረን ነበር። የሕግ ያለህ! መቼም የጊዜ ጉዳይ ነው። “የሽሮ ድንፋታ እንጀራ እስኪቀርብ” ነበር የተባለው? ይኸቺ ጊዜ ታልፋለች! እያንዳንዱ ምድረ-ወያኔ መንጋ ኢትዮጵያና ሕዝቧ ላይ ለፈጸመው የክህደትና የወንጀል ሥራ እንደ አጎቱ፣ እንደ ኃይለሥላሴ ጉግሳ ይጠይቅባታል። ወያኔዎቹ ብቻ ሳይሆኑ፣ ጀሌዎቹም ጭምር የሚጠይቁበት ጉዳይ ነው። ግፍ በዝቷል። ጽዋው ሞልቶ ፈሷል! ይቅርታ የሚባልበት ጊዘ አልፏል። አንገሽግሾናል!

እንዲያው በሞቴ፣ እነአንዳርጋቸውና ብርሀኑ ነጋ ምንኛ የወያኔን ካምፕ እንቅልፍ ነስተውታል ጃል! እኛ እኮ እዚህ እንሱን የምናያቸው እንደማንኛውም ተራ ዜጎች ነው። ጉድ እኮ ነው! እኔ እንዳርጋቸውን በመጠኑም ቢሆን አውቀዋለሁ። የምንገናኝበትም ሁኔታ አለ። በወያኔ የሽብርተኝነት ሕግ፣ እኔም እንደ እነስክንድር ሽብርተኛ ነኝ ማለት ነዋ! ቆይ እንጂ! በአንድ ወቅት አንዳርጋቸው፣ የወያኔ ማዘጋጃ ቤት ሹም አልነበር እንዴ! ታዲያ ከአንዳርጋቸው ጋር የተነካካ ሁሉ ሽብርተኛ ከሆነ፣ ከዚህ በፊት ቀጥሮት ሲያሰራው የነበረ ወያኔስ ምን ሊባል ነው? አንዳርጋቸው ሳያውቅ ምናልባት ከሽብርትኞች ጎራ በገባበት ዘመን ሳይከሰስ፣ ዛሬ ከሕዝብ ወገን ሲሆን ነው “አሸባሪ” ሲሆን ነጉር ሁሉ የተገለቢጦሽ ነው። ለመሆኑ አንዳርጋቸው ማንን ነው የሚያሸብረው! ወያኔን ከሆነ እያሸበረ ዕንቅልፍ የሚነሳው፣ ነገሩ ሌላ ነው። እንደኔ ያለው ተራው የኢትዮጵያ ሕዝብ ግን፣ አንዳርጋቸው የወያኔ ስለባ ከመሆኑና የሕዝብን ብሶት ከማጋባቱ በስተቀር ሽብርተኛ አድርጎ አያየውም። ለመሆኑ ለ17 ዓመታት ሙሉ ሕዝቡን በጠብመንጃ፣ በቦምብ ሲያጋዩት በርሀ ከርመው፣ ላለፉት 20 ዓመታት ደግሞ ስልጣን ላይ ፊጥ ብለው ሕዝቡን የሚያሸብሩት፣ አሸባሪዎች ምን ሊባሉ ነው? አሸባሪዎቹስ የምኒልክን ቤተመንግሥት በጉልበት የያዙ የኢትዮጵያ ጠላቶች፤ የተገንጣይዋ ኤርትራ ጠበቃዎች፣ እነመለስና ግብረአበሮቹ ናቸው። ይኸንን የምንለው እኛ የወያኔ ስለባዎች ብቻ አይደለንም። የዓለም ታዛቢዎችም ብለው ጨርሰውታል። ከፈለጋቸውሁ ይኸውላችሁ! http://www.youtube.com/watch?v=4WsV6fJJ51Q።

ክፍል ፫፡ ወያኔያዊ እኵይ ከፋፋይ ድርጊት በትርዒት

ወያኔ እስካሁን ከሠራው የወራዶች ትርዒት ሁሉ ሶስተኛው ከፍል የሚግለማ ነው።

http://www.ethiotube.net/video/16614/Must-Watch-ETV-Documentary--Akeldama--Part-3--The-case-for-Ginbot-7

ኤጭ! የፊተኞቹን ሁለቱን ርሷችው! ይኸን ትርዒት ነው ልብን ብግን የሚያደርገው። ሰው ሁሉ ልብ ብሎ አድምጦት ወስኖ ከነዚህ መዥገሮች ለመላቀቅ ቆርጦ መነሳት ያለበት።

ያን ዓይኑ እንደጉርጥ የተጎረጠረጠ ሞጋጋ ዝግጀት አቅራቢን፣ ከየት አገኙት? አስጠሊታ! ጻረ-ሞት (gohst) የመስላል። የካድሬነት እንጂ የጋዜጠኝነት ሙያ የማይታይበት የወያኔ ዕቃ! እዚህም ክፍል ውስጥ አንዳርጋቸው ጽጌና፣ እነዶክተር ብርሀኑ ነጋን በመኮነን በማላዘኑ ይቀጥላል። በዚህ አቀራርብ፣ የግንቦት ሰባትን አባላት የሆኑትንም ያልሆኑትንም እየጨፈለቀ ይዘባርቃል። ጽሑፉ፣ ወይም ስክሪፕቱ፣ በመለስ ዜናዊ የተደረሰ የዘረኞች ድርሰት መሆን አለበት። ለዛው ሙጥጥ! ትልቁ ኢሰብዓዊ የሆነው ድርጊቱ፣ በእስር ቤት ይዞ የሚያሰቃያቸውን ሰለባዎቹን (victims) በዱላና በመሣሪያ እያስፈራራ እያቀርበ ማናዘዝ ነው። በነገራችን ላይ በደርግ ዘመን እንደዚህ ስቃይ የበዛበት ወጣት፣ ዱላው እንዲቆምለት “ታንክ ከወላጆቼ ቤት ጓሮ ቀብሬአለሁ” ብሎ መርቶአቸው ጉድጓድ እንዳስቅፈረ ይተረካል። ቀለደብን ብለው እዚያው ገድለዉት በቆፈሩት ጉድጓድ ቀብረውት ሄዱ። “Under duress” ወይም “በሥቃይ ተይዞ” የሚባል ሕጋዊ አንቀጽ በዓለም ሕግ እንዳለ የወያኔ ቦዘኔ መንጋ ያውቅ ይሆን? መንግሥቴን ሊገለብጡብኝ ነው ብሎ አስሮ ደብድቦ እነ አቶ አሳምነው ጽጌና ብርጋዴር ጀኔራል ተፈራ ማሞ፣ ሌተና ኮሎሌል የሺዋስ አጥናፈ፣ ሌተና ኮሎኔል አስቻለው አምባቸው ላይ የፈበረከባቸውን ሸር እዚህም ደገመው። እነ ደበበ እሸቱ ላይ ተጠቀመ። እነዚያ ላይ የተጠቀመው ዘዴ፣ ከሥቃይ ብዛት አንደኛው በሌላው ላይ መስካሪ አንድርጎ ማስለፍልፍ ነበር። አሁንም ያንኑ አደረገው። ኤሊያስ ክፍሌ የግንቦት ሰባት አባሉ ሁኖ ቀርቧል። የውሸት ውሸት! ሀፍረተ ቢሶች! ኤሊያስ የወያኔን እርኩስ ሥራ ከማጋለጥ በስተቀር የማንም ፓርት አባል ሁኖ አያውቅም። ሲያስፈልገውም፣ ግንቦት ሰባትን ሲያብጠለጠለው እናነበዋለን። እሺ የኤሊያስስ ይሑን፣ አበበ ገላውን መክሰሳቸው፣ በደኅና ሕሊናቸው ነው? “የአራት ኪሎው ማም ቂሎ” ብሎት አልፈው ጓደኛዬ!

ከሁሉ ከሁሉ የሚገርመኝ፣ ወያኔ በደል በፈጸመ ቁጥር ዓይኑን ብልጥጥ አድርጎ “ይቅርታ ጠይቁኝ” ማለቱ ነው። ዓይኑ ይጥፋና! አንድ “ታዲዮስ አንተነህ” በሚል ስም የሚጽፍ የወያኔ ቡችላ ሰሞኑን ምን ያለኝ መሰላችሁ። የስድብ ጋጋታዉን ካዥጎደጎደው በኋላ፡ “ይልቅ ይቅርታ ጠይቀህ፣ ከሕዝብ ወግን ተቀላቀል” ነበር ያለኝ። በጣም ስለገረመኝ፣ ለብዙ ደቂቃዎች እዚያ ዐረፍተ-ነገር ላይ ፍዝዝ ብዬ ቀረሁ! ይገርማል! ይኸ የባንዳ ልጅ ባንዳ አገር ሻጮችን “ይቅርታ ጠይቅ” ይበለኝ!!! እኔን ነጻውን ስደተኛ ዜጋ ከማይደርሱበት የስደት ቤቴ “ይቅርታ ጠይቅ” ሊሉኝ የደፈሩ ወራዶች፣ እነዚያ በቁጥጥሩ ሥር ያሉትንማ እንዴት ያሰቃዩአቸው? መለስ ዜናዊ አንዴ ሲጨማለቅ የሰማሁት ትዝ አለኝ። “ከኦነግ የበለጠ የጎዳን የለም። ዳሩ ግን መሪዎቹ ይቅርታ ስለጠይቁን በሰላም በቦሌ በኵል አገር ለቀው እንዲሄዱ ፈቅደንላቸዋል ሸኘናቸው። ፕሮፌሰር አሥራት፣ ከሆነግ የበለጠ በደል እኮ መንግሥታችን ላይ አላደረሱም። ይቅርታ ቢጠይቁን ልንለቃችሁ እንችላለን ነበር ያለው ለጥያቄ አቅራቢው የውጭ ጋዜጠኛ! ወይኔ የሰውዬው ልጅ! በኋላስ! የቅንቅጅት መሪዎችን አፍሶ በአሰረ ማግስት፣ ተላላኪዎችን “ሽማግሌ” ተባዮቹን ጉዶች ልኮ ምን ነበር ለማግኘት የተሟሟተው? “ይቅርታ ይጠይቁኝ” ነበር ያለው። ከብዙ ውትወታ በኋላ “ይቅርታዋን” እንደፈለጋት አገኛት። ለመሆኑ “ይቅርታዪቱ” ከልባቸው መስሎት ይኾን? ዳሩ ግን፣ ከፋፍሎአቸው የሚፍልገውን አግኝቷል። ከተለቁቁም በኋላ፣ ብትንትናቸውን አውጥቶ እንዳይነሱ አደረጓቸዋል። “አከርካሪአቸውን መታን!” ብሎም ፎከሯል!

በእስር እንግልትም ቅስም መስበር ልማዱ ነው። ቅስም ለመስበር ደግሞ የማይጠቀመው ወራዳ ሥራ የለም። ለምሳሌ አንዷ የኦሮሞ ብሔራዊ ጎንግሬስ አባል ላይ ያደረሰውን በደል የቀድሞ ባለሥልጣናቸው የነበረ ሰው ሲነግረኝ፣ ሰውነቴን ሰቀጠጠኝ። አንድ የነሱ፣ ሰላይ አድናቂዋ መስሎ ቀረባት። እሥሯም ጉዳይ አስፈጻሚ መስሎ ጉድ-ጉድ እያለ አመኔታዋን አገኘ። በኋላ፣ እንዴት አድርጎ እንደመረዛት፣ እራሷን እንድሰት እንዳደረጋት፣ ከዚያ በኋላ እሷ ሳታውቅ ወራዳ ፎቶዎች እንዳነሳት፣ ወደ ልቧ ስትመለስ የወያኔ መንጋ ያንን ፎቶግራፍ አሳይቷት በወገኖቿ ላይ እንደትዘምት እንዳስገደዳት (blackmail)፣ ቅስሟን እንደሰበረና ከትግል ውጪ እንዳደረጋት አጫወተኝ። ከዚያ በኋላ ያች ጀግና ልጅ ሰው አልሆነችም። “አንቀጽ 39 ለነሱ ለአናሳዎቹ ይረዳቸው እንደሆነ እንጂ ለኛ ለብዙኃኑ ኢትዮጵያውያን ኦሮሞዎች ምናችንም አይደለም” ያለችው ጀግና ስነ-ልቦናዋ ተሰልቦ ከጨዋታ ውጭ ሆነች። አገር ጥላም በረረች። ያለችበትም አይታወቅም። ጭጭ ምጭጭ አደርጋት!

እህታችንን ብርቱካን ሚዴቅሳን እሥር ቤት ምን እንዳደረሰባት እስካሁን በግልጽ የተነገረ ነገር የለም። ብቻ ያደረገውን አድርጎ ያችን የአንበሳ ግልገል፣ “አጥፍቸአለሁ! ይቅርታ!” አሰኝቷት ለቀቃት! ይቅርታውን አግኝቷል። ብርትኳን ከስነ-ልቦናዋ ቁስል እያገገምች ነው። ብርቱካን! እንወድሻለን! አይዞሽ! በርቺ! ባለሽበት፣ አምላካችን ካንቺ ጋር ይኹን። እልባችን ቀርጸነሽ ይዘንሻል! የኛዋ ኦንግ ሳን ሱኪ!

ወያኔ ምን ጊዜም ቢሆን አስገደዶ ይቅርታ ቢያስብል፣ ልባዊ ይቅርታ ከማንም ኢትዮጵያዊ አያገኛትም! ሰው በድሎ ይቅርታ ጠይቁኝ የሚል አምባገነን ምናልባት ወያኔ ብቻ መሆን አለበት። ይኸ እንከፍ ቡድን ሰው አሰቃይቶ ይቅርታ ቢያሰኝ ዕውነት ያስገበረ ይመስለው ይኾን? እንዚህ መንጋዎች ከጫካ ከወጡ ሀያ ዓመት ቢደፍኑም፣ አሁንም እንደ ዱር አውሬ ነው የሚቅበዘበዙት። ከሁሉ ከሁሉ የሚያሳዝነው፣ በጁ ይዞ ካስለፈለፋቸው ሰዎች ሁሉ፣ የደበበ እሸቱ ቅስም መሰበር ነው። ጀግናው ደበበ፣ ተሰበረላቸው! ጀግናው ደበበ ግንቦት ሰባትን አወገዘላቸው። ብርሀኑ ነጋን ሰደበላቸው! ሲናገር የሰከረ እንጂ በብሩህ ልቦናው እንዳለ አይመስልም። ጸጉሩ ተንጨባሯል። ያበደ ነው የሚመስለው። “መንግሥት እኮ በግልጽ አስቅምጧል” ይላል ደበበ ዕንባ እየተናነቀው። “ግንቦት ሰባት አሸባሪ ድርጅት ነው ብሎ አስቀምጧል። እዚህ አገር ሁኜ፣ በየዕለቱ የሚሰጠውን መረጃ እያየሁ፣ አሸባሪ ነው ተብሎ ከተፈረጀ ድርጅት ጋር ለምንድነው፣ በምንም መልኩ ይኹን ግንኙነት ያደረግኩት! ይኸ ነው የሚያስጸጽተኝ” እያለ በራሱ ላይ የፈርዳል! በቤታቸው አዋርደውታል! ቅስሙን ሰበረውታል! ወንድሜን!!! የሚፈልጉትን ብሎላቸው ከእስር ቤት ወጣ። በነሱ ቤት አብቅቶለታል! ከዚህ በኋላ ሰው የሚሆን አይመስላቸውም። እኛ ግን እነሱ እንደፈለጉት አናወግዘውም። ማንም ሰው በጠላት እጅ ሲወድቅ፣ ጠላት የሚፈልገውን ተናግሮ ስቃዩ እንዲቀርለት የሚያደርገውን መለፍለፍ የሥነ-ልቦና ሊቃዉንት በግልጽ አብራርተውታል። ፒ ኤ ዲ (ዶክተሬት ድግሪ) ተሠርቶበታል። ነጻ ሲወጣ ዕውነቱን ይናገራል።

ስለእስክንድር ማለት የምፈልገው ነገር አለ። ወያኔ ያን ሁሉ ማስፈራራት ካደረሰበት በኋላ፣ መጽሐፉን እንዳይታትም ከለከለው። ያንን መጽሐፍ ጓደኞቼና እኔ ልናሳትምለት ታጥቀን ተነስተን። አንድ እስክንድር ያስጠነቀቀኝ ጉዳይ ቢኖር፣ ያንን መጽሐፍ ለማሳተም ከተሰብሰብን ቡድን መሀል አንድም የፖሊቲካ ድርጅት አባል እንዳይኖር ነበር ያለኝ። የትኛው ፍርድ ቤት ቀርቤ ዕውነቱን ልመስክር! ወይኔ የአቶ ሰውዬው ልጅ! በዚህ የተነሳ፣ ሌሎች ፈቃደኛ የሆኑቱን ሶዎች ሁሉ ነበር አይሆንም ብዬ ያስቀርሁት። መጨረሻ ላይ አንዳንድ ነገሮች ስላሳሰቡኝ፣ “እኔ የወያኔ ነቃፊ ስለሆንኩኝ፣ ምናልባት በኔ ምክንያት እንዳያጠቁህ፣ ሌላ ሰው ልወክልና ጀርባ ልሰለፍ” አልኩት! “የለም! አንተማ ወደ ጀርባ መሰለፍ አያስፈልገህም! ጓደኞቼን ሁሉ ወያኔ ሊመርጥልኝ አይችለም። የፖሊቲካ ድርጅቶችን ብቻ አስወግድ። ወያኔ ሊያጠፋኝ ሲነሳ ምንም ዓይነት ተጨባጭ ምክኒያት ሊኖረው አያገባም። ሳያመካኝ ይብላኝ!” ነበር ያለኝ። ይኸ ሰው ነው እንግዲህ፣ ከሻዕቢያና ከግንቦት ሰባት ጋር ግኑኝነት አለህ ተብሎ ለእስር የተዳረገው። ቢኖረውሳ! የአሜሪካን፣ የእንግሊዝ፣ የፈረንሳይ ጋዜጠኞች አፍጋኒስታን ተራራ ድረስ ሂደው ታሊባንን ያነጋግሩ የለም እንዴ! የሕሊና ደንቆሮ!

ወያኔ የመሀይም ጥርቅም ነው። ከጫካ እንደውጧት አንድም ያልተለውጡ የወንበዴ መንጋ የተጠራቀሙበት ዋሻ ነው። የሰላጠነ አገርማ፣ የሕግንና የሚዲያን ልዩነት ጠንቅቆ ያውቃል። ለፍዳዳው የወያኔ አፈ-ቀላጤ “ይኸ አገር እኮ በሕግና ሥነ-ስርዓት የሚመራ ነው ብሎ ሲመጻደቅ” ስሰማ ሊያመኝ ተናነቀኝ። በሕግና በሥነ-ሥርዓት የሚመራ አገርማ ውስጥ፣ በመጀመሪያ ደረጃ፣ በፍርድ ቤት የተያዘውን ጉዳይ በሜድያ ላይ፣ ያዉም በከሳሹ በመንግሥት ቴሌቪዥን ወጥቶ አይዝረከረክም። ነጻ ፍርድ ቤት ቢኖርማ እንዲህ ዓይነት ብልግና መንግሥት ሲፈጽም ሲያይ ጉዳዩን ወርውሮት ተከሳሾችን በነጻ ይልቅ ነበር።

በዚህ ፊልም፣ በጣም አስቂኝና አሰልቺ የግንባታ መንግስሥት ተረት-ተረት ሲተላለፍ እንሰማለን። ይገርማል! የጥፋቱ ገዥ የልማት መንግስት ነኝ ለማለት ይጣጣራል! ሰው ጦሙን ማደሩን ማን በነገረው! በልማት አመካኝቶ ገንዘብ ለመሰብሰብ እንዳበደ ውሻ ይሯሯጣል። ያ ቀላባጅ ፕሮግራም አቅራቢ እንዲ ሲል ፕሮግራሙን ይደመድማል።

“ለአሸባሪዎቹና ለዕኵይ ተግባራቸው ቀዳዳ ከፍተን ዕድል ከፈጠርንላቸው አንድ ቀን ከዚህ ቀደም እንዳደረጉት ሁሉ፣ አባት፣ እናት፣ እህት፣ ወንድም ወይንም እጅግ የምንወዳትን ሕይወታችንን ሊነጥቁን እንድሚችሉ መርሳት የለብንም። አሁንም፣ ሽብርተኝነት የመኖራችን ሕልውና ሥጋት እየሆነ መጥቶብናል። በመሆኑም እያንዳንዱ ዜጋ አካባቢውን በንቃት መጠበቅ ይኖርበታል። ለሀገሩ ሰልምና ልማትም ዘብ መቆም ይጠበቅበታል። እኛ ኢትዮጵያውያን ከሰላማንና ከልማታችን በላይ የሚበልጥብን ምንም ነገር የለም። አሸባሪዎቹ፣ በጥፋት መንገዳችው ሲዳክሩ፣ እኛ በሕዳሴ መንገዳችን እንቀጥላለን።”

ውይ! ተባለ እንዴ! ይኸን ሁሉ ሲለፈልፍ ታዲያ፣ አሜሪካ ውስጥ፣ በመንታ ሕንጻዎች ላይ የደረሰውን አደጋ ፊልም እያሳየ ነው። እሱ ስለሌለው ልማቱ ሲደሰኩር፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ እንደነቃበት ከዚህ በታች ባለው የጸሎት መርዶ እናርዳውና እኛም በበኩላችን ቅስሙን እንስበረው። አሁንም ከሩቁ ወዳጄ ከጋዜጠኛ ከዳዊት ከበደ ያገኘሁት፣ ወያኔን “ሕዳሴ” እያለ “የአባይ መገደቤ ነው፣ ገንዘብ አምጡ” እያለ ሲይስጨንቅቸው፣ የአዲስ አበባ አራዳ ወጣቶች የደረሱት ጸሎት ነው።

የአባይ ህዳሴ ፀሎት

አባያችን ሆይ፣
በበርሃ የምትኖር፤
ስምህ ይመዝገብ፣ ግብርህም ይምጣ።
ማረፊያህ በግብፅ እንደሆነ፤ እንዲሁም በህዳሴው ላይ ይሁን።
የእለት ውሃችንን ስጠን ዛሬ፤
ደሞዛችንን ይቅር በለን፤
እኛም የጠየቁንን እንደምንሰጥ።
አቤቱ ወደ ቦንብ ግዢ አታግባን፤
ከብድር አድነን እንጂ።
ቦንድ ያንተ ነውና፤
አይ መብራት ኃይል፤
ለዘለአለሙ፤
አሜን።

ወያኔን ለማስወገድ ሁላችንም ከመተባብር ሌላ ምርጫ የለንም። ታስረው የሚንገላቱትን ወንድሞቻችንና እህቶቻችንን ከጎናቸው ከመቆም ሌላ አማራጭ የለንም። ወያኔ ሺህ ጊዜ ትርዒት ቢያቀነባብር፣ ለራሱ ይዝናናበት እንደሆን እንጂ ሀቋን አይቀይራትም። እስከዘልዓለም ልባችንን አያገኛትም! ውጭ ያለነው፤ ወያኔ ላይ ማመጽ አለብን! እያንዳንድህ! እያንዳድሽ ወግኔ ታጥቀህ ተነስ! ታጥቀሽ ተነሺ! ወያኔ ላይ፣ ጥርስህን ንከስ! ጥርስሽን ንከሺ! ልብህን ዝጋበት! ልብሽን ዝጊበት! አበቃ!|

Wednesday 2 November 2011


Aninet's Organ -

Wednesday 5 October 2011


ሰንደቅ ዓላማችን
ከወንድሙ መኰንን፣ ኤልስበሪ፤ ኢንግላንድ፣ መስከረም ፳፬ ቀን ፪፼፬ ዓ. ም
ወያኔ ወደ ሥልጣን የመጣው የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ እያጋየ ነበር። የጨው መቋጠሪያ ጨርቅም አድርጎት ነበር፡፡ በመጣም በነጋታው ሕገ-መንግሥቴ የሚለውን መጨቆኛ መሣሪያ ለማጽደቁ ኑ ብሎ በጠራቸው የሱ ብጤ ዘረኞች ስብሰባ ላይ ሰንደቅ ዓላማችን፣ ሲዋረድ፣ ሲብጠረጠር እንደነበር ለታሪክ ዩ-ትዩብ በተባለው የዘመኑ የድምጽና የተንቀሳቃሽ ስዕል ማሳያ የድረ ገጽ ማሳያ ላይ ለሕብረተሰቡ ለዕይታ በቅቶ ይገኛል።
ያንን ጉድ ስንሰማ ስንቶቻችን በገንን።
ሰንደቅ ዓላማችን እንዳገራችን እራሷ ባለታሪክ ናት። ሰንደቅ ዓላማችን፣ እነሱ እንዳሏት “ጨርቅ” ብቻ ሳትሆን ስንት ደም የፈሰሰባት ወድቃ የተነሳች ልዩ የታሪካችን መዘክርና የማንነታችን ማብሰሪያ ሰንደቅ ናት። በነገራችን ላይ በተለምዶ “ባንዲራ” ትባል እንጂ ትክክለኛው አጠራሯ “ሰንደቅ ዓላማ” ነው። ባንዲራ በጠላት ወረራ ጊዜ እንድንቀበለው ወራሪዎች የዶሉብን ወይም የተበከልንበት “አልለቅ” ያለን የጣሊያን ቃል ነው። ጠላት ወርሮን አራዳን “ፒያሳ”፣ አዲስ ከተማን “መርካቶ” እንዳላትና ለሌሎቹም ካክዛንቺስ፣ ፖፖላሬ፣ ባምቢስ ብሎ ሰይሞ ተጣብቀውብን እንደቀሩት የቦታ ስሞች እንደማለት ነው። ባህር ምድርንስ ኤርትራ ብሎ ሰይሞ አይደል ጉድ ያፈላብን!
ከአምስቱ ዓመታት የጠላት ወረራ በስተቀር ይኽች ሰንደቅ ዓላማ ለብዙ መቶ ዓመታት ዓርማችን ሁና አገልግላለች። ቀይና አርንጓዴው ቦታ ቢቀያየሩም፣ ብጫው ከመሀል ሁኖ ከኛ ጋር የኖረች አርማችን ናት።
ሰንደቅ ዓላማችን ከ ፲፰፻፸፫ (1881)[1]  እስከ ፲፰፻፹ (1887) ዓ.ም. ድረስ ይኸን ስዕል እንደምተመስል ከታሪክ መዘክር ማውቅ ችለናል።










በአጼ ምኒልክና በንግሥተ ነገስታት ዘውዲቱ ምኒልክ ዘመን መንግስታት ከ፲፰፻፹ (1887) እስከ ፲፱፳፰ (1936) ዓ. ም. ሰንደቅ ዓላማችን፣ ምንም ዓይነት ምልክት ያልተለጠፈባት ሁና እንደሚከተለው ተሽሞንሙና እናገኛታለን።













ይኸች ሰንደቅ ዓላማ ነበረች፤ አደዋ ድረስ ዘምታ በአሸናፊነት ወደ አዲስ አበባ የተመለሰችው። ይኽችን ሰንደቅ ዓላማ መሆን ነበረባት ዘርዓይ ድረስ በጁ ጨብጦ የብዙ ጣሊያኖችን አንገት በጎራዴ ሮም ላይ የቀላው። መሰረቷ ሶስቱ ቀለማት ናቸው።
መቸም ታሪካችን ውጣ ውረድ የሞላበት ነው። ጠላት በ፲፱፳፰ (1936) ዓ.ም. ሲወረን፣ ሰንደቅ ዓላማችንን እንደወያኔዎቹ አብጠልጥሎ ሳይሆን በክብር አውሮዶ አታጥፎ ካስቀመጠ በኋላ፣ የራሱን፣ የኢትዮጵያ፣ የኤርትራ እና የሶማሌ ውሁድ የምስራቅ አፍሪካ ጣሊያን ኤምፓየር ብሎ ሰይሞ “ባንዲራ” ሠርቶ አንጠለጠለላት። የኛ ሰንደቅ ዓላማ “ወደቀች” የሚባለው በዚህ የአምስት ዓመት የጠላት ወረራ ነበር። ዕውነቱ ግን ጠላት ሰንደቅ ዓላማዋን ከጃንሆይ ግቢ አውረዳት እንጂ አልወደቀችም። ሰንደቅ ዓላማዋ አርበኞችን ተከትላ በረሀ ገባታ ተዋጋች እንጂ አልተጣለችም። ሰንደቅ ዓላማችንም እንዳባቶቻችን እራሷን ችላ አርበኛ ናት! ያችን ሰንደቅ ዓላማ ያከበረና የያዛት ሁሉ በአሸናፊነት እንደሚወጣ የተመሰከረላት በዚህን የችግር ጊዜ ብሩህ ተስፋ ነበረች። የሚከተለውን የምሥራቅ አፍሪካና “ባንዲራ” የነመለስ አያት እና መሰሎቻቸው ባንዳዎች ያጎበድዱላት ይሆን ይሆናል እንጂ የኛዋስ በየዱር ገደሉ ስትውለበለብ ነበር። "ባንዲራ" ማለት ይኽች ናት። በቃሉም ውስጥ “ባንዳ” ይገኝበታል። ሌላም አስጸያፊ ቃል በውስጧ ይገኝባታል።። አልለውም ግን። 
-

በየአደባባዩ ከሞቅዲሾ እስከ አሥመራ ይኸንን “ባንዲራ” ብላ ጣሊያን ብታውለበልበውም፣ የኛ ዕውነተኛ ሰንደቅ ዓላማ ግን አርበኞቹ ባሉበት ሁሉ፣ ሲንቀሳቅሱ ከፍ አድርገው ተራ በተራ ሲሸከሟት፣ ሲያርፉ፣ በየእንጨቱ እያውለበለቧት በየዱር በየገደሉ ተሟሟቱባት። በቆላ በደጋ ለአምስት ዓመታት ተዋግተው ነጻነታቸውን ሲያስመልሱ፣ ኦሜዴላ ላይ በግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የተወለበለበች ሰንደቅ አሸናፊዋ ዓላማችን አረንጓዴ፣ ብጫ፣ ቀይ የሆነች ሌጣ መለያችን ይኽች ነበረች። ቀዩና አረንጓዴው ቦታ እንዴት እንደተቀያየሩ ለታሪክ ባለሙያዎች ትቼዋለሁ።



















በኋላ ላይ ግን ያው ዘውዱን የጫነ አንበሳ ተቀምጦበት ኦፊሴላዊ በሆነ ቦታ ላይ ሲውለበለብ፣ በየመሥሪያ ቤቱ፣ በየትምሕርት ቤቱ ይወጣና ይወርድ የነበረው የግድ ዘውድ ያያዘ አንበሳ ያለበት ሳይሆን መሠረታዊው አርንጓዴ ብጫና ቀይ ሰንደቅ ነበር። መሠረቱ ምንጊዜም ሶስቱ ቀለማት ናቸው። ንጉሡም ሆኑ ባለሟሎቻቸው የሚያውቋት ያችኑ በአረንጓዴ ብጫ ቀላማት ያንቆጠቆጠችውን ሰንደቅ ዓላማችንን ነበር። ትርጉሙም፣ አርንጓዴ ልምላሜንና ዕድገትን፣ ብጫው ዕምነትን (በእግዚአብሔር ማመንን) እና ቀዩ ኢትዮጵያዊው ሁሉ ኦሮሞ፣ አማራ፣ ጉራ ጊሚራ፣ ወላይታ፣ አደሬ፣ ሲዳማ ትግሬ፣ እስላም ክርስቲያን ሳይል በአንደነት ደሙን አፍሦ፣ አጥንቱን ከስክሶ የወጃትን አገራችንን የሚያወሳ መሰዋዕትነትና ጀግንነትን ነው። አንድም ሰው፣ “ወድቆ በተነሳቸው ሰንደቅ ዓላማችን” ሲባል፣ ቀጥ ያላል። ሰንደቅ ዓላማችን የራሷ የሆነ ልዩ ክብርና ልዩ ፍቅር ሕዝባችን ዘንድ ነበራት።

እያንዳንዱ ሕብረተሰብና እያንዳንዱ ቤተሰብ ጋ ይኸች ሰንደቅ ዓላማ የየበተሰቡ እንደ አንድ አባል ሁና ነበር የኖረችው። ዛሬም አለች። በትግራይ፣ አንድ ትልቅ ሰው ሲሞት ክብሩ የሚለካበት፣ ሬሳው ሰንደቅ ዓላማ ለብሶ ወደ ቤትክርስቲያን ሲሄድ ነው። ያንን እንኳ ወያኔዎች አልተገነዘቡትም! ታዲያ ዘውድ የግድ ያለበት አልነበረም፣ አይደለም። ዘውድ ያለበት የሚውልበለበው ኦፊሴል በሆነ ንጉሡ ወይም እንደራሴአቸው ባለበት ብቻ ነው። ይኸች ሰንደቅ ዓላማ ከ፲፱፳፰ (1936) እስከ ፲፱፻፷፮ (1974) ኦፊሴላዊ በሆነ ቦታ ቻ ከዘውዱ ተውለበለበች። በየትምሕርት ቤቱ ሲትወጣ፣
ደሙን ያፈሰሰ ልቡ የነደደ፣
ባርበኝነት ታጥቆ ጠላት ያስወገደ፣
ንጉሡን አገሩን ክብሩን የወደደ
ነጻነቱን ይዞ መልካም ተራመደ፡፡
ገናናው ክብራችን ሰንደቅ ዓላማችን፣
ያኮራሻል አርበኝነታችን፡፡

እየተባለ እየተዘመረ ትወጣ ነበር። የሚሄድ ሁሉ በያለበት ይቆማል።
ሲትወርድ ደግሞ

ተጣማጅ አርበኛ በአገር መውደድ ቀንበር፣
ገዳይ ድል አድራጊ ደም አፍሳሽ ወታደር፣
አንቺን እያሰበ ይጓዛል ሲፎክር፣
ሰንደቅ ዓላማችን የነጻነት አገር

እየተባለ ሲዘመር አሁንም የሚንቀሳቀስ ሰው ቀጥ ይላል፣ የተቀመጠ ተንስቶ ቀጥ በተጠንቀቅ ይቆማል።

በ፲፱፻፷፮ (1974) ደርግ ሥልጣን ስይዝ፣ እስከ ፲፱፻፷፯ (1975) ዘውዱን አውርዶለት በኦፊሴል ሲጠቅም የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ግን ሌጣው እንዳለ ሕዝቡ ይጠቀምበት ነበር። ትንሽ ቆይቶ ደርግ ኦፊሴሊያዊ በሆነ ቦታም ጭምር በየስብሰባው ያለ ዘውዱ አንበሳውን ያስቀምጥበት ጀመር


መሠረታዊውን አረንጓዴ ብጫ ቀዩን ግን ማንም ሊደፍር አልሞከረም። እንዲያውም መስከረም ፪ ቀን ፲፱፻፷፯ (1975) አምበሳውንም እስካናካቴው አነሳውና ሌጣ አርንጓዴ ብጫ ቀይ ኦፌሰሊያዊ ለሆነ ስብሰባ ሁሉ ሳይቀር የሚውለበለብ ተደርጎ መጠቀም ተጅምሮ ነበር።


ወዲያው፣ ትንሽ ቆይቶ ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት፣ "የሕብረሰብዓዊት ኢትዮጵያ ጊዚያዊ ወታደራዊ መንግሥት" አርማ ቀርጾ መህል አስቀመጠና ኢፊሴሊያዊ በሆኑ ቦታዎች ይጠቅም ነበር፡፡ ሕዝቡም ሆነ መሥሪያ ቢቶች ግ ን ልሙጡን ከመጠቀም የሚያስገድዳቸው ሕግ አልነበረም፡፡



በኋላ ላይ ደርግ “ሕብረተሰባዊት ኢትዮጵያ”ን ሲያውጅ አንድ ያንን የሚያንጸባርቅ አርማ አስቀምጦበት ነበር። ልብም ያለው የለም። እነሱም ሆኑ ሕዝቡ ግን ያው ምንም ዓርማ ያልነበረበትን ነበር ይጥቀሙ የነበሩት።
በኋላ ላይ በ፲፱፻፸፯ (1985) ዓ.ም ላይ “የኢትዮጵያ ሕዝባዊ ዲሞክራሲያዊ መንግሥት” መሰረትኩ ሲል አርማውን ቀየረ።


ሌጣው ግን ምንጊዜም የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማነቱን እንኳን መከራከርና የጠየቀም አልነበረም። እንዴት ተደርጎ! ሁሉም አረንጓዴ ብጫውን አቅፎ በየቤቱ በየበዓላቱ ያውለበልብ ነበር።

በታካችን ሰንደቃላማችን የተዋረደችው ከወራሪው ጣሊያን በበለጠ በዚህ በወያኔ ዘመነ ፍዳ፣ ዘመን ኩነኔ ነው። አንደኛ፣ ከበረሀ ጀምሮ ቤተመንግሥት እስኪደረስ ድረስ ሰንደቅ ዓላማችን ወያኔ እንዳቀጠለና፥ እንደቀደደ፥ እንደረገጠ ነበር። አዲስ አበባን ሲቆጣጠር በሰላም የመከላከያ ሚኒስቴርን ሲረከብ እንደወራሪ ሰንደቅ ዓላማዋን ወዲያው እንደማይሆን አድርጎ አውርዶ የወያኔን ሰንደቅ ዓላማ በቦታው ተካ። ሰው እሪ ብሎ ሲጮኽበት ተገዶ በቦታው መለሰው። ይኸ ከሀዲ ቡድን ሕዝባችንን ልብ አያውቀውም እንበል? ከዚያ በኋላ ሰንደቅ ዓላማውን ለመቀየር ያልሸረበው ደባ፣ ያልፈተለው ተንኰል አልነበረም። በብዙ ሰው ትግል አረንጓዴ ብጫ ቀዩ ተረፈ። በ፲፱፻፹፬ (1992) የዘረኞች መንጋ ተሰብሰቦ ከመጀመሪያ በዩቲዩቡ ፊልም ላይ እንደታየው ዶልቶ፣ “የብሔር-ብሔረሰብነትን እኵልነት የሚያበስር” ብሎ በ፲፱፻፹፰ (1996) ላይ በክብ ሰማያዊ ኣምባሻ መሰል ዙሪያ ውስጥ የተሠራ ኮከብን ለጠፎበት “ህንካችሁ ትክክለኛው ባንዲራችሁ ይኽች ናት” ሊለን ሞከረ። የሆዳችንን በሆዳችን ይዘን ዘግተነው ትክክለኛውን መጠቀሙን ሕዝቡ ቀጠለ።


ቆዩኝማ! ማን ነበር ያ ስም አይጠሬ ይኸን ኮከብ ግንባሩ ላይ የለጠፈው? 
ማንም ክፍል ሥልጣን ሲይዝ የራሱን አርማ በኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ላይ መለጠፉ የተለመደ እየሆነ መጥቷልና እሱስ መሆኑ ባላስገረመም ነበር። የነሱ አምባሻ አሽታሮት ብዙም ባልደነቀን ነበር። ዳሩ ግን፣ እየቆዩ በሄዱ ቁጥር ሌጣውን የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ የያዘ ሁሉ የነሱን ኮከብ ካላስቀመጠበት ለነሱ ሰጥ ለጥ ብሎ አለመገዛቱ እየመሰላቸው መወንጀላቸው ነው።
ይኸ ሰንደቅ ዓላማ የአባቶቻችን ደም የፈሰሰበት፣ አጥንታቸው የተከሰከሰበት ነው። ብዙ መስዋዕትነት ተከፍሎበታል። በዚህ ምክንያት ማንም ሰው ተነስቶ የሚቀልድበት ወይም የፈለገውን ለጥፎበት ሊያርክሰው አይችልም። ወያኔ ሰንደቅ ዓላማችንን እንዳጎደፋት፣ መጥቶ ዛሬም በጉልበት ሥልጣን ጨብጦም እንዳዋረዳት ይገኛል። የሱ አሽታሮት የሌለበትንም “ባንዲራ” ሳይሆን አርንጓዴ ብጫ የያዘውን ሁሉ ወንጀለኛ በማድረግና በማሰር ሕዝባችንን ማሰቃየት ጀምሯል። ይኸንንም ከሚከተለው የአሜሪካን ድምጽ ሬዲዮ ቃለ መጠይቅ በመኢአዱ መሪ በእንጅነር ኃይሉ ሻውልና በአንድ የወ በወያኔ አፈቀቀላጤ ኃብታሙ ሚሚ በሚባለው መሀል የተካሄዱትን ክርክሮች በመስማት መረዳት ይቻላል።
ኮከብ የሌለው ባንዲራ ከዚህ ሥርዓት ጋር ምንም ግንኙነት የሌለው ባንዲራ ነው። ያ ሥርዓት ፈርሷል። በብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ትግል ፈርሷል! በሚገባ ለመስቀመጥም የጨቋኝ ሥርዐት ምልክት ነው። ዛሬ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦችና ወደዘር ጭቆና ዳግም ላለመግባት በጋራ ቃል ገብተው ነው ... አንድነታቸውን ለማጠናከር እየሠሩ ያሉት። ... ስለዚህ ከዚህ አንጻር ስናይ አንደኛ ባንዲራ እንደሚታወቀው ሰንደቅ ዓላማ ከስሙ እንደሚገለጸው የአንድን ሥራዓት አላማ ነው የሚገልጸው። የኛ የፌዴራል ሥራዐታችን ዓላማ የፌዴራሉ መንግሥት ባንዲራ ኮከብ ያለው ነው። ያኛው ሥርዓት የራሱ ዓላማ የነበረውና የወደቀ ሥርዓት ነው። ዳግመኛም የማይመለስ ሥርዐት ነው። ... እንግዲህ ያንን ሰንደቅ ዓላማ አውለበልባለሁ ብሎ ማለት ጸረ-ሕዝብነት በወንጀልም የሚያስጠይቅ ነው። ከዚያም ባሻገር በኢትዮጵያ ብሔር ብሐረ ሰቦች መበቶች እንደማመጽ የሚቆጠር ነው። ያንን ለስቀል መሞከር ሕገ-ወጥነት ነው። ሕገ መንግሥቱንም መተላለፍ ነው።
ኃብታሙ ሚሚ እንደዛተውም የወያኔ ኮኮብ የሌለበትን ሰንደቅ ዓላማ የሚያውለበልበውን ሁሉ የጨቋኝ ሥርዐት አራማጆች እያለ ማሳደዱን ቀጥሏል። ወያኔ ታሪካችንን እያጎደፈ፣ ባሕላችንን እያቆሸሸ፣ አንድነታችንን እያፈረሰ፣ አገራችንን እየሸጠ ይኽ ምልክት ያለበትን ሰንደቅ ዓላማ ማውለብለብና “የባንዲራ ቀን እያለ” ማሾፍ ጅምሯል።

በቅርብ ቀን የወያኔ ቅልቦች ውጭ አገር ድረስ እጃቸውን አስረዝመው የተረገመችውን “ባንዲራቸውን” ስደተኛው እንዲቀበለው ማስገደድ ጅምረዋል። የወያኔ ተንኰል ያልገባቸው ወጣት ኢትዮጵያውን የስደተኛ ሊጆች ወያኔ በረሀብ ለሚፈጀው ሕዝባችን ገንዘብ ለማሰባሰብ፣ አባቶችን፣ እናቶችን፣ ወንድሞችን፣ እህቶችንና ጓደኞቻቸውን ለንዶን ውስጥ ለማሰባሰብ ሞክረው ነበር። የወያኔ ሰዎች በራሪ ወረቆቶቹ ላይ የነበረውን ሰንደቅ ዓላማ አይተው “ያ ትክክለኛ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ሳይሆን የቅንጅት ሰንደቅ ዓላም ነውና በኢትዮጵያ ስም ይኸን ሰንደቅ ዓላማ መጠቀም አትችሉምና ትክክለኛው ይኸ ነው” ብለው አስፈራርተው እንዳይስቀየሩአቸው ደርሰንበት በግነናል።
ስደተኛው ኢትዮጵያዊ ሕብረተሰብ ይኸን ድፍረት መመከት ይገባዋል። ወያኔ ለአረንጓዴ፣ ብጫ ቀዮ ሌጣ ቀለም ተገቢውን ክብርና ቦታ እስካልሰጠው ድረስ ማንም ይኸንን የዘረኝነት ዓላማ የተንጸባረቀበትን የግድ መቀበል የለበትም። ወጣቶቹስ ምንም አያውቁምና አይፈረድባቸውም። ለትላልቆቹ ግን ትልቅ መልዕክት ማስተላለፍ ይጠበቅብናል። እሱም፣ ይኸንንም “ባንዲራ” ይዞ የተገኘ አዋቂ፣ የሟቾቹ አባቶቹና እናቶቹ አጥንት ይውጋው ብለን መርገም አለብን። እርጉም የተረገመ ይኹን! አሜን።[2] ወያኔ መሠረታዊውን የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ እስካላከበረ ድረስ ከሱ ጋር ያበረ፣ ከሱ ጋር የተባበረ፣ ከሚተባበረውም ጋር የዋለ፣ የፕሮፌሰር ጌታቸውን ቃል ልዋስና፣ እሱም እራሱ ወያኔ ስለሆነ የተረገመ ይሁን። ይኸን የወያኔ የዘረኛ አርማ “ባንዲራ” የያዘ ሁሉ ጥቁር ውሻ ይውለድ በሉና ርግሙት። ዕውነተኛው ሰንደቅ ዓላማችን፣ ያልተበረዘች፣ ያልተለወጠች፣ በድል አድራጊነት ዛሬ ላይ የደረሰች አርንጓዴ ብጭ ቀይ አርማችንን ከፍ አድርገን እናውለብልባት።





[1] በቅንፍ ውስጥ የሚታዩት የአውሮፓ ወይም የግሪጎራውያንን አቆጣጠር ነው።
[2] ነሐሴ ፴ ቀን ፲፱፻፩ ዓ. ይኸንን በተመለክተ የተጻፈችውን የእንግሊዝኛ ግጥሜን ብሎጌ ላይ ማንበብ ይችላሉ። http://wondimumekonnen.blogspot.com/2010_06_01_archive.html

Friday 30 September 2011


ደቂቀ በሊላ
ወንድሙ መኰንን
THE BELILAS BROUGHT UP AND NURTURED TO DESTROY ETHIOPIA

ሌባ እንጂ በሊላ
የለዉም ስም ሌላ
በሊላ በሊላ
ያስሠበረ ኬላ
ቀፈቱን ሊሞላ
ኑን ያስበላ

Haile Selassie Gugsa Surendering himself to the service of The Fascists

ለናቱ ያልራራ
ኰል እያደራ
ሰላቶ እየመራ
ያስቃማት መከራ
የባንዳ ልጅ ባንዳ
ወገኑን የከዳ
ገር ያስደፈረ
ለሆዱ ያደረ
Hailselassie Gugsa - transformed soldato of the fascists

ምን መጣ አዲስ ነገር?
ድንብሩን ቢያስደፍር
ገር ቢቸረችር
ንብረት ቢመዝብር
ከአያት ቅመ አያቱ
ከዘር ምንዝራቱ
እስከ ምንጅላቱ
ከሥር መሠረቱ
ገና ከጠዋቱ
የበሊላ ነገር
ደሮም ባንዳ ነበር።

A great grand son of the Belilas


Thursday 29 September 2011


ደመራ 


(በሃይማኖታችን፥ በታሪካችንና በባሕላችን አንጻር)

ቀሲስ አስተርአየ ጽጌ

nigatuasteraye@yahoo.com

መስከረም ፳፻፬ ዓ.ም.



           ደመራ’ ደመረ ከሚለው የግዕዝ ቃል የተወሰደ ነው:: ትርጉሙ ጭመራ ማለት እንደሆነ ለማንም ግልጽ ነው:: ጥሪት (ካፒታል) እንዳይጎድል እንዳይቀነስ ይልቁንም እየበዛና እያደገ እንዲቀጥል ጠብቆ መያዝ የሚያስችል ደመራ ነው:: ስሙ እንደሚያመለክተው ማስታወሻነቱ ለተጠራቀመ፥ ለተሰበሰበና ለተጨመረ ነገር ነው::  በዓሉ አካቶ የያዛቸዉ ሥርዓቱ የሚከናወንባቸው ቁሳቁሶች፥ የደመራው እንጨቶች፥ ችቦዎች፥ አሽክቶችና፥ ሌሎችም በበዓሉ ዙሪያ የሚታዩት፥ የሕዝቡን ስሜት አንድ ላይ ሰብስቦ ስለያዘ ደመራ ተባለ:: የደመራ ተቃራኒው ቅነሳና ከፈላ ነው::

በአገራችን በተፈጠረው ታሪካዊ ክስተት ምክንያት፥ በነገረ መለኮት ከኛ ጋራ አንድ ከሆኑት አኀት አብያተ ክርስቲያናት በማይካፈሉት ሁኔታ በተለየና በደመቀ ሥርዓት በመላ ኢትዮጵያ ይከበራል:: ካህኑ የመጀመሪያዋን የደመራ መብራት “ደምረነ ምስለ እለ ይድኅኑ” በሚለው በሊጦኑ ቃለ ቡራኬ ባርኮ፥ ከደመራው እንጨት ጋራ እንዲደምራት ሕዝቡን በአስተዳደር ለሚመራው ሰው ያቀብለውና የደመራውን እንጨት ይለኩሰዋል:: ከዚያ በኋላ በተዋረድ ያገር ሽማግሌ ሁሉ ችቦውን እያቀጣጠለ በደመራው ላይ ይጨምረዋል:: በዚህ ሥርዓት የሚከበረውን የደመራ በዓል በሃይማኖታችን፥ በታሪካችንና በባህላችን አንጸር በመጠኑ እገልጻለሁ:: ዛሬ ባለንበት ዘመን ይህችን እሳት ባርኮ ሰጭው መንፈሳዊው ካህን ማነው? እሳቷን ከካህኑ ተቀብሎ በደመራው ላይ የሚለኩሳትስ ብቃት ያለው የአገር መሪ ማነው? ከዚያስ በተዋረድ እየለኮሰ ደመራውን የሚያቃጥል ሽማግሌ ማነው? በማለት ከሊቃውንት አበው የተማርኩትንና የሰማሁትን

·       በሃይማኖታችን፥

·        በታሪካችንና በባሕላችን

አንጻር በመዳሰስ ይሕችን ጦማር እደመድማለሁ:: በመጀመሪያ በሃይማኖታችን አንጻር እነሆ!





ደመራ በሃይማኖታችን አንጻር




የአምልኮታችንን ሥርዓት ተንተርሶ “The Wisdom Compass to Eternal Life” በሚል ርእስ አቤል ጋሼ ጌታችን ያስተማረውን ጸሎት መሠረት በማድረግ በቀመር መልክ ብቅርቡ ባቀረበው መጽሐፍ ብዙውን ዳሶታል:: አቤል ጋሼ በገጽ ምዕ 10  ገጽ 135 ላይ “While we keep reciting ‘Have mercy on us’ twelve times corresponding the name of the Father, the son and the Holy Spirit”  ብሎ የጠቆመውን ከደመራ ጋራ ያለንን መንፈሳዊና ባሕላዊ ግንዛቤ ለመግለጽ እሞክራለሁ::

አምልኮታችንን ጀምረን የምንፈጽመው ነቢዩ ኢሳይያስ በምዕራፍ ፮ ከቁጥር ፪-፭ እንደገለጸው፥ ቅዱስ ዮሐንስም በራዕዩ አይቶ እንደነገረን፥ (ምዕራፍ ፬ እና ፭) የእግዚአብሔርን ዙፋን በተሸከሙት ኪሩቤል የአምልኮት ዘይቤ ነው:: እነዚህ ኪሩቤሎች በላያቸው ላለው ፈጣሪ አምልኮት ሲያቀርቡ ሶስት ጊዜ “ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የነበርክ ያለህ፥ ወደፊትም የምትኖር” እያሉ ነው:: የቀደሙ ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንትም ይህን መሠረት በማድረግ “ንሕነሰ ነአምን ከመዝ እስመ ሥሉስ ቅዱስ እሩያን እሙንቱ በተዋሕዶተ መለኮት ወፍጹማን በ፫ቱ አካላት ዘውእቶሙ ፩ዱ አብ ቅዱስ፥ ወ፩ዱ ወልድ ቅዱስ፥ ወ፩ዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ” (ሃይ ምዕ፷፪፡፲፭):: እያሉ የነገረ መለኮቱን መሠረት አስተማሩ:: ማለትም፥ “እኛም እንደ ሱራፌልና ኪሩቤል፥ ኢሳይያስ ባየው፥ ዮሐንስም በገለጸው መንገድ በአካል ሶስት፥ በመለኮት አንድ እያልን እናምናለን፥ አምነንም እናመልከዋለን፥ እናስተምረዋለን”:: በኪዳን ተጀምሮ በቅዳሴው የሚፈጸመው አምልኮታችን የሚከናወነው በዚህ መሠረት አንድም ሶስትም እያልን ነው::

ቅዱስ ጳውሎስ “ሕጻን ሳለሁ፥ እንደ ሕጻን አስብ ነበር እንደ ሕጻንም እቆጥር ነበር” እንዳለው ሕጻናት ነገሮችን ማጤን የሚጀምሩት የራሳቸውን ጣቶች በማየት፥ የሚዳስሱትንም ለመቅመስ ጣቶቻቸውን በመጉረስ ነው:: ቁጥር መማር የምንጀምረው በጣቶቻችን ነው:: በጸሎታችን የሰማዩንና የምድሩን ሁኔታ ከዳሰስን በኋላ የምንደመድመው በጣቶቻችን ላይ ባሉት አጽቆች (phalanxes) ቀመር ነው:: Mutation (የተፈጥሮ ባሕርይን መቀየር) ከሚባለው አጋጣሚ በቀር ያንዱ እጅ ጣቶቻችን ከአምስት አይጎሉም፥ አይተርፉም::

አውራ ጣታችንን ቆጣሪ በማድረግ በአራቱ ጣቶቻችን ላይ ያሉትን አጽቆች እንቆጥራለን:: አራቱ ጣቶቻችን እያንዳንዳቸው ሶስት አጽቆች አሏቸው:: በያንዳንዷ ጣት ላይ ያሉት አጽቆች ስብስብ መጠን ለማግኘት ስንደምራቸው ፲፪ ቁጥር እናገኛለን:: እኒህ በጣቶቻችን ላይ ያሉት ፲፪ አዕጹቅ ቁጥሮች ለአምልኮታችን ሥርዓትና የባሕላችን መሠረቶች ናቸው:: ዛሬ በየብስ፥ በባሕርና በአየር ውስጥ ተቆልፎ የኖረበትን የፍጥረት ምሥጢር የሰው ልጅ እየበረገደ የገባውና በመግባት ላይ ያለው በደመራ በተጀመረ ቁጥር ነው::

12  ን አጽቆች ለ4 ጣቶቻችን ብናካፍላቸው የምናገኘው ውጤት ሥላሴ ማለትም 3 ነው:: 12 ን አጽቆች ባንዷ ጣት ላይ ላሉት ለ3 አጽቆች ብናካፍላቸው የምናገኘው ጸወርት መንበር የሚባሉትን 4ቱን ኪሩቤል ነው:: እንደገና 3 እና 4 ብንደምር የሳምንቱን ዕለታት ልክ ቁጥር 7 ን እናገኛለን:: ፊደሎቻችንም የተዋቀሩት በሳምንቱ ዕለታት ላይ ነው:: በግዕዝ (፩) ተጀምራው የሚያልቁት በሳብእ (፯) ቁጥር ነው:: ፩፥ ፫፥ ፬፥ ፯ ና ፲፪ ቁጥሮች ለብዙ ነገሮች ምልክቶች ናቸው::

በአራቱ ጣቶቻችን ያሉት ፲፪ አጽቆች፥ አንድ ቀን የተባለው ብርሃን የያዛቸውን አስራ ሁለት ሰዓቶች ያስታውሱናል:: አንድ አመት የሚሰጡንን የአስራ ሁለት ወራት ጥርቅም ይሰጡናል:: የክርስቶስን ምድራዊ አካል ምንጭ ለማግኘት የምንቆጥራቸውን የ፲፪ቱን ነገደ ፳ኤል ቁጥር ይሰጡናል:: በመቀጠልም ከክርስቶስ ቀጥለው ክርስትናን ያስፋፉትን የሐዋርያትን ፲፪ ቁጥር ይጠቁሙናል::

የቤተ ክርስቲያናችን የጸዋዕ ማኅበራት፥ በስላሴ፥ በመድኃኔዓለም፥ በእመቤታችን፥ በመላእክት በጻድቃንና በሰማእታት ስም የሚመሰረቱት በ ፲፪ ቁጥር ነው:: በራዕየ ዮሐንስ ላይ እንደተገለጸው፥ የያንዳድዱ አጥቢያ (ሰበካ) ቁጥር በአስራ ሁለቱ ነገደ እስራኤል፥ በ፲፪ ሐዋርያት፥ በ፲፪ ወራትና በ፲፪ ሰዓተ መአልት (ቀን) ልክ ነው:: አካለ መጠን የደረሰ ሁሉ በያለበት አጥቢያ (ሰበካ) በ ፲፪ እየተመደበ ይደመራል:: ሁሉም የጽዋዕ ማኅበራት ለያንዳንዳቸው መምሕር ይመደብላቸዋል:: እያንዳንዱ አባል ከዓመቱ ውስጥ ካሉት ወራት አንዱን ይወክላል:: ከነገዶች ውስጥ አንዱን፥ ከሐዋርያትም አንዱን ይወክላል:: በዚህ መንገድ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት አባል የሆነ ሁሉ በዚህ ቁጥር እየተካተተ (እየተደመረ) የጽዋው ተካፋይ ይሆናል::

እያንዳንዷ በ፲፪ ቁጥር የተዋቀረችው የጽዋዕ ማኅበር አባላት ከመካከላቸው በእምነትና በመንፈስ ላቅ ያለውን መርጠው ሙሴ የሚባል ለማኅበሩ መሪ ይሰይማሉ:: እያንዳንዷ የጽዋዕ ማኅበር የመረጠችው ሙሴ (መሪ) ደግሞ፥ የሚመራትን የጽዋዕ ማኅበር በመወከል አንድላይ ተሰብስበው ይደመሩና የራሳቸውን የጽዋዕ ማሕበር፦ ማሕበረ በኩር ብለው ይሰይማሉ:: ለማሕበረ በኩሩ መምሕር ሆኖ የሚሰየመው በሙያና በችሎታ ከሊቃውንቱ መካከል ተመርጦ የደብሩ አለቃ ነው:: የደብሩ አለቃ ዋና ኃላፊነት እየዞሩ የጽዋዕ ማኅበራቱን አባላት የሚያስተምሩትንና የማኅበረ በኩሩን አባላትና ሙሴዎች አንድላይ እየሰበሰበ ማስተማር ስለሆነ በጥንቃቄ ይመረጣል:: የመሳፍንቱ ሥርዓት ተጽእኖ ቤተ ክርስቲያኒቱን ባያዘናጋት ኖሮ የያንዳንዷን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መምራት የነበረበት ይህ ማኅበረ በኩር የተባለው ጉባዔ ነበር::

በተራ በየቤቱ በሚደረገው ጉባዔ ተረኛው ቄጠማውን ጎዝጉዞ፥ ውሐውን ቀድቶ ይጠብቃል:: የአምልኮቱ ማዕከል ዮሐንስ የታረደው በግ እያለ የገለጸው ክርስቶስ ነው:: ሁሉም ነጭ ልብስ ለብሰው ስለታረደው በግ ፍቅር፥ ክብር ውዳሴና አምልኮ ለማቅረብ ይሰበሰባሉ:: በሙሴያቸው አስተናባሪነት ካህኑ በራዕየ ዮሐንስ ላይ የተመሠረተውን ሥርዓት በመጠበቅ ጉባዔውን ይመራል:: ከዚያም የማኅበሩ ሙሴ ባለወር፥ ባለሳምንት ብሎ ጉባዔው የተሰየመበትን ስም እየጠራ “የጉባዔው ወዳጅ ማነህ እኔነ ነኝ የምትል” ብሎ ያውጃል::ተረኛው ተዘጋጅቶ በመጠበቅ ላይ ነውና እኔ ነኝ ብሎ ወደ መሐል ይቀርብና ይቆማል:: “እኔ አለሁ ብለህ እንደቆምክ መድኃኔለም ይቁምልህ” ይለዋል:: ጽዋውን በመቀባበል በጽዋዕ ውስጥ ያለውን ጠበል ሁሉም ይካፈለዋል:: ከዚህ በኋላ ጽዋውን የተቀባበሉ አካላት በጉባዔው ፊት ይወድቃሉ:: መምሕሩ “እንደዚህ እንደወደቃችሁ ኃይለ አጋንንትን ያውደቅላችሁ” ብሎ አቤል ጓሼ እንደገለጸልን ሰዓታቱን፥ ወራቱን ነገደ እስራኤልን፥ ሐዋርያትን በመጨረሻም ስላሴን አራቱ ኪሩቤልን አጠቃሉ ደምሮ በያዘው ፲፪ ቁጥር “እግዚኦ መሐረነ ክርስቶስ” ይልና ያለፈውን ይቅር ይበለን ከሚመጣውም ጠብቆ በሚቀጥለው ጉባዔያችን ያገናኘን ብሎ የአምልኮቱን ሥርዓት ይዘጋዋል:: ነፍሳቸውን ይማርና ብፁዕ አቡነ ቴዎፍሎስ የሰበካ ጉባዔውን ሲነድፉት፥ በዚህ ቅዱስ ታሪክና ባሕል የቤተ ክርስቲያናችንን አስተዳደር ለማዋቀር ነበር፡፡







ደመራ በታሪክችንና በባህላችን አንጻር


         

ደመራውን የጀመረችው በሶስተኛው ክፍለ ዘመን አካባቢ እሌኒ የምትባለው የቆስጠንጢኖስ እናት ክርስቲያን ንግሥት ናት:: የጀመረችበት ምክንያትም የክርስቶስ ተቃራኒዎች፥ የክርስትና ንክኪ ያለውን  ፍንጭ ሁሉ ለማጥፋት ባደረጉት ጥረት፥ ከክርስትና ፍንጮች አንዱና ዋናው የክርስቶስ መስቀል ስለነበረ፥ በጉርጓድ ቀበረውት ነበረና፥ ፈልጋ ለማግኘት ነው::

እሌኒ ሕይወቷ የተመሠረተው በክርስትና ፍቅር ላይ ስለነበረ መስቀሉን ለማግኘት በብርቱ ጣረች:: መስቀሉን ለማግኘት የተጠቀመችበት ስልት፥ እሳት አንድዳ ጢሱ እንዲመራት በመጸለይ ነበር:: የሚቃጠል ነገር ሰብስባና ደምራ በማንደድ ጢሱን ተከትላ በመሄድ መስቀሉን አገኘችው:: የታሪኩ መነሻ እሌኒ እንደሆነች በያመቱ ስንናገረው የኖርነው ነውና፥ በዚህች ጦማርም መሸፈን ስለማልችል በእሌኒ ዙሪያ የሚነገረውን ታሪክ እዚህ ላይ ገትቼ፥ ከራሳችን ታሪክ ጋራ ወደተያያዘበት መስመር እሻገራለሁ::

የታሪኩ መሠረት ይህ ሆኖ ሳለ ንግሥት እሌኒ በጀመረችበት ቦታ፥ እኛ በምናደርገው ሥርዓት ዓይነት ሊከበር ቀርቶ የሚያስታውሰውም የለም:: ታዲያ ለምን እኛ ብቻ በዚህ መልክ እናከብረዋለን? የሚል ጥያቄ ማስከተሉ አይቀርም፥ ተገቢም ነው:: መልስ የሚጠበቀው ከዚያ ወዲህ በየዘመኑ ወደ አገራችን ከገቡት ባሕርያቸው ከደመራ ይልቅ ወደ ከፈላ ካዘነበሉት አብያተ ክርስቲያናት አይደለም:: የደመራውን ታሪክ የማስተማርና በደመራው ዙሪያ ለሚነሱት ጥያቄዎችም የመመለስ እዳ፥ ሸክምና ግዴታ ያለባት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብቻ ናት::

የጥምቀቱን በዓል ከዓለም ክርስቲያኖች ለየት ባለ መንገድ እንደምናስታውሰው፥ በንግሥት እሌኒ ሕሊና ውስጥ ይነድ የነበረውን የክርስቶስን ፍቅር በያመቱ ደመራ የሚል ስም ሰጥተን በዓለም ያሉ ክርስቲያኖች በማያስቡበት በተለየ መንገድ እናከብረዋለን:: በዓላት በምክንያት የሚጀመሩ፥ የታሪክ መነሻዎች ናቸው:: ባንድ ወቅት የተጀመሩት ሳይረሱ የሚታረመውን እያረሙ፥ የሚጨመረውን እየጨመሩ ዓለም እስክታልፍ የሚቀጥሉ ሕዝቦች፥ በቅኝ ገዥዎች አዕምሯቸው ሳይዝልና ሳይዘነጋ እስከ መጨረሻ ጠንክረው የሚጓዙ እንደ ኢትዮጵያውያን ያሉ ኅብረተ ሰቦች ናቸው::

ይህ በዓል ከተጀመረበት ጀምሮ እስከዚህ ዘመን ድረስ በገጠሙን ክፉ ቀናቶች ሁሉ ሳያቋርጥ ከኛ ደርሷል:: በዓላት ሁለት መንገዶች አሏቸው:: ከሁለቱ አንዱ ከጣዖትና ከባዕድ አምልኮት ጋራ የተያያዘ ቅዱስ መጽሐፍ የሚያወግዘው ነው:: ከሰይጣን አምልኮት በራቀ መንፈስ ባሕልን ታሪክን አዝለው በመመላለስ የሚታወሱ ሁሉ በዓላት፥ ይዘታቸው እየሰፋ የሚቀጥል መጻሕፍቶች ናቸው:: ይህ አይነት የSocial Memory መጽሐፍ የሌለው ሕብረተ ሰብ በኛ ግንዛቤ እንስሳት ብቻ ናቸው::

ከዚህ ቀደም ቅበላ (http://www.medhanialemeotcks.org/pdf/ISAT.pdf) በሚል ርእስ እንደገለጽኩት፥ በሐዘንና በደስታ፥ በልቅሶና በሳቅ፥ በመሸበርና በመረጋጋት በምትናወጠው ዓለም የሚኖር ሰው፥ በዓሉን የሚያከብረው በሚገጥመው ሁኔታ ነው:: አንድ ጊዜ የተዘጋጁ መጻሕፍት በውስጣቸው የያዙትን ምዕራፍ በሚገጥሟቸው ተመሳሳይ አዳዲስ ክስተቶች እያሰፉ በመደጋገም እንደሚታተሙ ሁሉ፥ በዓላትም እንደዚሁ በየአመቱ የሚገጥማቸውን እየጨመሩ ስለሚሄዱ የሕብረተ ሰቡ ትዝታ ወይም የ Social Memory መጻሕፍት ናቸው::

ለደመራው በዓል መነሻዋ እሌኒ ብትሆንም፥ እሌኒ ደመራ ብላ አልሰየመችውም:: ይህ በዓል ደመራ ተብሎ አሁን በምናከብረው ሁኔታና መንፈስ እጅግ ሰፍቶ ከመከበሩ በፊት፥ ወደ እኛ ተሻግሮ መጥቶ ሲከበርና ሲታወስ ቢኖርም፥ የመስቀል በዓል እንጅ ደመራ እየተባለ አልነበረም:: እሌኒ የሰራችውን ታሪክ በማስታወስ ሲከበር የቆየው የመስቀል በዓል፥ በአጼ ገላውዴዎስ ዘመን አዲስ ታሪካዊ ክስተት ገጠመውና ሊቃውንት አበው፥ ከታሪካችን ጋራ ደምረውና አስፍተው ደመራ ብለው ሰየሙት::

ከሊቃውንት አበው መምሕሮቼ እንደሰማሁት፥ ግራኝ መሐመድ ኢትዮጵያን በወረራት ዘመን፥ የአገሪቱ መሪ አጼ ልብነ ድንግል በዚያ ዘመን ገናና ይባል የነበረውን የፖርቹጋሉን መንግሥት እርዳታ ጠየቁ:: የፖርቹጋሉ መንግሥትም ይህን አጋጣሚ ተጠቅሞ፦

·       ፩ኛ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሮማ ካቶሊክ ሥር፥

·       ፪ኛ ኢትዮጵያንም በራሱ ቅኝ አገዛዝ ሥር ለማድረግ ከሮማው ፓፓ ጋራ ሲሸርብ ዘገየ::

ከዚህም ጋራ የዘመኑ የጉዞ ሁኔታ ለመዘግየታቸው ተጨማሪ ችግር ነበር ይላሉ:: በዚያም ሆነ በዚህ፥ አጼ ልብነድንግል ከጠየቁበት ወቅት እጅግ ዘግይተው፥ ጦርነቱ ከበረደ በኋላ መልእክተኞቹ ደረሱ:: አጼ ልብነ ድንግል ሞተው፥ በጦርነቱ የደቀቀው ሕዝብ በአጼ ገላውዴዎስ መሪነት በመቋቋም ላይ ሳለ፥ በሸርና ሸፍጥ የተላኩት የፖርቹጋል ሰዎች ዘግይተው ከኢትዮጵያ ደረሱ:: ጦርነቱ እንዳለቀና የነሱም እርዳታ እንደማያስፈልግ ሲረዱ ወደ አገራቸው በመመለስ ፈንታ፥ በኢትዮጵያ ውስጥ በመኖር በሕዝቡ መካከል እየገቡ፥ አሁን ቻይናዎች በአገራችን ላይ እንደሚያደርጉት ማለት ነው፥ ኢትዮጵያውያን ሴቶችን እየተጋቡ በመዋለድ ኑሯቸውን ማስፋፋት ጀመሩ::

በአገሪቱ ባሕል ሃይማኖትና ፖለቲካ እየገቡ የሕዝቡን አንድነት የሚፈታተን ሸርና ደባ መሥራት ጀመሩ:: በዚያን ጊዜ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ የተፈጠረው ሁኔታ በዘመናችን የተደገመ ይመስላል:: ከአጼ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት መወገድ ጀምሮ ደርግ እስኪፈርስ ድረስ በውጭ ጠላት ባይሆንም እርስ በርስ በተካሄደው እልቂት ያለቀው ሕዝብ አገሪቷ ያመረተችው ምርጥ ዜጋ ነበር:: አገሪቱ እነዚህን ሁሉ አጥታ፥ ህዝቡም ተዳክሞ ባለበት ወቅት፥ ዘረኛው ያቶ መለሰ መንግስት አገሪቱን በግላጭ ተቆጣጠራት:: እንደዚሁ ሁሉ በግራኝ መሐመድ ካለቀው የተረፈው ሕዝብ ከግራኝ መከራ በኋላ ሳያርፍ እንደገና ፖርቹጋሎች ከፈጡሩበት መከራ ውስጥ ገባ:: ከኤርትራ ጋራ በንጉሡና በደርግ ዘመን በተደረገው ግጭት ካለቀው ሕዝብ ይልቅ በአቶ መለሰ መንግሥት ያለቀው ወገን ይበዛል እንደሚባለው መሆኑ ነው::

በፖርቹጋሎችና በኢትዮጵያውያን መካከል ጥላቸውና መናናቁ እጅግ በማየሉ በቅጽል ስምና በተረብ መዘላለፍ ተጀመረ:: ኢትዮጵያውያን ለፖርቱጋሎች ትኋን የሚል ስም ሰጧቸው:: ፖርቱጋሎች ደግሞ ለኢትዮጵያውያን ቁንጫ የሚል ስም ሰጧቸው:: በመናናቅ እርስ በርስ የተሰጣጧቸው የቅጽል መግለጫዎች ትርጉም አላቸው:: ኢትዮጵያውያን ፖርቹጋሎችን በትኋን ጠባይ የገለጿቸው፥ ትኋን የሰው ደም መምጠጥ የምትጀምረው ጨለማ ተንተርሳ፥ ቀስ ብላ እየተጠራራች ከየስርቻ በመውጣት ነው:: ደሙን የመጠጠችው ሰው ካያት ሮጣ አታመልጥም:: የመጠጠችውን ደም ተሸክማ ስትንገዳደገድ ትደፈጠጣላች:: ጥላው የምትሔደው ክርፋት በቶሎ የሚለቅ አይደለም:: ፖርቹጋሎችን እንዲህ ናችሁ ለማለት ኢትዮጵያውያን ትኋኖች ብለዋቸዋል::

ቁንጫ ለመባላት ቀንም ሌትም አትመርጥም:: ይዞ ለመግደልም የማትጨበጥ ፈጣን ናት:: የሚሸት ነገር የላትም:: ኢትዮጵያውያኖችንም አይያዙም፥ አይጨበጡም፥ ጠላታቸውን ለማጥቃት ቀንና ሌሊት አይመርጡም ለማለት ፖርቹጋሎቹ ኢትዮጵያውያንን ቁንጫዎች ብለዋቸዋል:: በዚህ መልክ መሰዳደቡና መተራረቡ አድጎ ጸቡና ጥላቻው እየከረረ ሄደ:: እንዲያውም አድዋ አካባቢ የነበሩት ፖርቹጋሎች ድርጅታቸውን የበለጠ አጠናክረው “መንግሥታችሁ በፖርቹጋል ምንግሥት ሥር ካልሆነ ተቆርጣችሁ የቀራችሁ ናችሁ” እያሉ በመስበክ በሌላው ክፍለ አገር ሕዝብ ላይ ከፈጸሙት የመከፋፈልና እርስ በርሱ የማገዳደል ደባ በአድዋ ሕዝብ ላይ የፈጸሙት እጅግ የከፋ ነበር ይባላል:: ይህንም ለማስታወስ በአድዋ አካባቢ ያሉ ኢትዮጵያውያን እስካሁን ድረስ “ዓኾ ዓኾኋይ ሆይ ሆያዬ ንጎናይ በርሆ” በማለት ደመራውን በመዞር በያመቱ ያስታውሱታል:: ይህም ማለት፥ “እናንተ ተቆርጣችሁ የቀራችሁ እያሉ ይዘልፏቸው ስለነበረ፥ እኛ ኢትዮጵያውያን የተቆረጣችሁ እየተባልን በገዛ አገራችን ስንሰደብ ብንኖርም፥ ዛሬ በዚህ ችቦ የነጻነት ብርሃን በራለን” እንደ ማለት ነው ብለው ሲናገሩ ሰምቻለሁ:: የትግርኛውን ቋንቋ ስለማላውቀው አበላሽቼ እጽፈውና እተረጉመው ይሆናል:: ይቅርታ እየጠየቁ የማቃናቱን ኃላፊነት ባካባቢው ለተወለዳችሁ ወገኖቼ እተወዋለሁ:: ንጎናይ ማለት ቆራጣ ማለት ነው ሲሉ ሰምቻለሁ:: ከዚህም ጋራ ለአገራቸውና ላንድነታቸው ጸንተው የቆሙ የትግራይ ሰዎች በአማረኛ አሽከት በትግርኛ ጸጎጎት የምትባለውን የመጣበቅ ባሕርይ ያላትን ሐርግ በራሳቸው ላይ ያስራሉ:: ሐረጓን ያንድነታቸውና የጽኑ መተማመናቸው ምልክት አርገው ተጠቅመውባትል:: በአሽክቷ የተጠቀሙበትን ምሥጢር መስከረም ፲፮ በያመቱ ጽንዒ እያሉ ያስታውሱታል::

የፖርቹጋሎች ሁኔታና አዝማሚያ ኢትዮጵያውያንን እያሳሰባቸው መጣ:: ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ይህን ነገር ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሕዝባቸው ሳይጎዳ እነዚህን ትኋኖች እንዴት እንደሚገላገሏቸው አጠኑና የመስቀሉን በዓል እንዴት እንደሚጠቀሙበት ዘዴ አመነጩ:: ምሥጢር ማደላደል በሚባለው ጉባዔ ላይ በየኔታ ፍስሐ መሪነት፥ ነፍሶቻቸውን ይማርና የኔታ አንዳርጌና የኔታ አምዴ የቅኔ መምሕራን ሲነጋገሩ እንደሰማሁት፥ በዚያ ዘመን የነበሩ ሊቃውንት እንዴትና በምን መንገድ ፖርጋሎችን ላንድ ጊዜና ለመጨረሻ ጠራርገው ለማጥፋት ሲያስቡ፤ በመጽሐፈ መሳፍንት ምዕ ፱ ከቁጥር ፳ ላይ ተመዝግቦ እንደምናነበው “ለትጻዕ እሳት እምቤተ አቤሜሌክ፥ ከመ ትብላእ አብያተ ሴኬም፡ ወትሜሎም:: ወለእመ አኮ እሳት ትጻእ እምቤተ ሴኬም ወትሜሎም ከመ ትብላዕ ቤተ አቤሜሌክ” የሚለው ንባብ ትዝ አላቸው:: ይህም ማለት “እኛ ኢትዮጵያውያን በገዛ አገራችን የተደጋገመ ግፍ እየተፈጸመብን ነው:: ይህች ከኢትዮጵያውያን ቤት እየተጫረች የምትወጣ የዘንድሮው የመስቀል በዓል እሳት፥ በሸርና በሸፍጥ በእርዳታ ስም መጥተው የወረሩንን ፖርጋሎችን ትብላ፥ ለአገራችን ለነጻነታችን መታገላችን በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት አጥቶ ረድኤቱን ከነፈገንም፥ ለዘላለም በፖርጋሎች ሥር ተጠቅተን ከመኖርና ለልጆቻችንም የተገዥነትን ውርስ ከማውረስ ይሕች ከየቤታችን የጫርናት እሳት እኛኑ ትብላን” ብለው ቆርጠው ተነሱ::

“የመስቀል በዓል ፖርጋሎችን የማይደምር የግላችን ነው:: የምናከብረው ሌሊት ነው:: በበዓላችን የማይደመሩት ፖርጋሎች እንቅልፍ ላይ ይሆናሉ:: እናንተ ቱኋኖች ከአገራችን ውጡ፥ እያልን በምናበራው ችቦ ቤታቸውን እያቃጠልን በኛ ላይ የሚያደርጉትን ግፍና፥ በቅኝ ግዛት ለመቀጠል ያላቸውን ረዥም እቅድ ይህችን የመስቀል በዓል በመጠቀም ላንድና ለመጨረሻ ጊዜ መግታት አለብን” ብለው ያቀዱትን በየደብሩ ለሚኖረው አካለ መጠን ለደረሰ ወንድ ልጅ ሁሉ ትድረስ ብለው ካህናቱ በቆራጥ መንፈስ አሰራጩት:: መልእክቱ የደረሳቸው ኢትዮጵያውያን ሁሉም በመተባበርም ተግባራዊ አድርገውት አደሩ:: ካህናቱ ለወገን መጎሳቆል ተቆርቁረው ወስነው ባንድ ልብ እንሙት ብለው መነሳታቸው ያስደነቀው አንድ ሰው፥

“ካህን ሞተ ተብሎ አይነግሩም አዋጂ

እንዲህ በየደብሩ መላክ ነበር እንጂ” ብሎ እንደገጠመ ይነገራል::

በነገራችን ላይ የኔታ አንዳርጌ ከላይ የጠቀስኩትን ታሪክ መሠረት በማድረግ በደመራ ሌሊት መወድስ ዘርፈውበት፥ እኛ ተማሪዎችም የሳቸውን ቅኔ እንደ ምሳሌ (ሞዴል) በመጠቀም የሳምንቱ የቅኔ መቁጠሪያችን ሆኖ መሰንበቱን አስታውሳለሁ::

ኢትዮጵያውያን ከወገኖቻቸው አንድ ሰው ሳይጎዳ በመስቀሉ የችቦ እሳት አገራቸውንና ነጻነታቸውን ከፖርቱጋሎች ነጥቀው መለሱ:: ይህንም ለማስታወስ በደመራው በዓል “ትኋን ውጪ ቁንጫ ግቢ” ይባላል:: ኢትዮጵያውያን የፖርቹጋሉን መሪና የሮማውን ፓፓ ሸፍጥ አከርካሪውን የሰበሩበት ጥበብና ጀግንነት ፖርቹጋሎችንና ሮማውያን አሳፍሯል፥ አስቆጥቷል፥ ቂምም አትርፏል::

ትኋኗ አለማምለጥና ስትደፈጠጥም የምታስከትለው ክርፋት፥ ለኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ቅኔ ሰምና ወርቅ ሆኗል:: የማይለቅ ክርፋት የተባለው የትኋኗ ሽታ፥ በዚያን ጊዜ የደረሰባቸው ጉዳት፥ በሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን መሪዎች ልብ የቀረጸው ቂምና በቀል ነው ይላሉ:: “ጥንተ አብሶ” ይሉሐል ይህ ነው::

እያንዳንዱ ዜጋ ለወገንና ለጋራ ጥቅም ለሰባዊ ልዕልና ቅድሚያ በመስጠት የሚቀርብለትን ጊዜያዊ ጥቅም ንቆና ተጸይፎ በመተው ፍላጎቱን ካልገታ፥ አገር እየበደለ ሕዝቡን እያስለቀሰ ለመኖር ከውጭም ይምጣ ከውስጥም ይፈጠር በጥቃቅን ነገር በሹመት በገንዘብ መፈተኑ አይቀርም:: ይህ አይነት ፈተና ሁለት ሰዎች [አዳምና ሔዋን] ብቻ በሚኖሩባት ገነት ከተከሰተ፥ በየተለያዩ የጎሳ ስሞችና ቋንቋዎች በምንኖርበት ባሁኑ ወቅትማ፥ እንደ ፖርቹጋሎች ለሚከፋፍል ለሚለያይ መንግሥት፤ ድኅረ ገጾችን፥ የመገናኛ መስመሮችን እያፈነ በጨለማ ዘግቶና አፍኖ ለመግዛት ምን ያህል ምቹ እንደሚሆንለት በአጼ ገላውዴወስ ዘመን ከነበሩት ወገኖቻችን የበለጠ መገንዘብ ይኖርብናል::

ኢትዮጵያውያን ካህናት ከፖርቹጋሎች ጋራ ወግነው ያስቸግሩ ስለነበሩ ወገኖች “ስማዕ እግዚኦ እለ ኪያከ ይስእሉ:: እግዚኦ እለ ዘንስእለከ ኢንሰተት አላ በስክየት ዲበ ጸላኢነ ነሀሉ:: ሀበነ ዘወትር ጸሎተነ እምኂጠተ ጸላኢ ንትአቀብ:: . . . . ተወከፍ ሲሩያነ በምሕረትከ አንጽሕ አብዳነ አጥብብ ወኅጉላነ”(ዘነግሕ):: በማለት ጸለዩ:: ማለትም፥ “አቤቱ በቅን ሕሊና የሚለምኑህ ስማ፥ የምንለምንህ እኛም ተሸንፈን እንዳንወድቅ እርዳን:: በወቀሳም በከሰሳም የምንከሰስበት እንዳይኖር ብንከሰስም እንድንረታ እርዳን:: ከጠላት ሸፍጥና ማታለል ነቅተን እንድንጸልይ እርዳን:: በስሕተታቸው ተጸጽተው የተመለሱትን ወገኖች ተቀበላቸው:: አርቆ የማሰብ ችሎታ ያጠራቸውንም ወገኖች ሕሊናቸውን ብሩህ አርግላቸው:: ወደ ጠላት ጎራ በመግባት ከመካከላችን የጠፉትንም ወገኖች ንቃቱንና ማስተዋሉን ስጣቸው” በሚለው ላይ አስምረውበታል::

ሊቃውንቱ ሰዓቱንና ወቅቱን ከታሪኩ ጋራ በማገናኘትም “መዝገበ ጽልመት እንተ ብነ በሥምረተ አቡከ አብራህከ ለነ ዘአውጻእከነ እማዕምቅ ውስተ ብርሃን:: ወወሀብከነ ሕይወተ እሞት:: ወጸጎከነ እምግብርናት ግዕዛነ:: ዘበመስቀልከ አቅረብከነ አምላክ:: አላ ብርሃነ ሀበነ”(መንፈቀ ሌሊት):: እያሉ አምላካቸውን አመሰገኑ:: ማለትም፥ “በጨለማ ውስጥ ለነበርን ለኛ ባባትህ በጎ ፈቃድ የደኅንነት ብርሃን አበራሕልን:: ከጨለማ አዘቅት አውጥተህ ወደ ብርሃን አፋፍ አወጣህን:: ከሞት አድነህ ሕይወትን ሰጠኸን:: ከመገዛትም ነጻ አወጠሀን:: በመሰቀልህ ያቀረብከን አምላክ ሆይ ብርሃንህን ስጠን”::

በግራኝ መሐመድ የተጎዳውና የተጎሳቆለው ወገን፥ እንደገና ከፖርቹጋሎች ጋራ ፊት ለፊት በመጋፈጥ እንዳይሞትባቸው፥ “ዕቀብ ኩልነ ዘእንበለ ጻሕብ ወዘእንበለ ተመውዖ ወዘእንበለ ማዕቀፍ:: አድኅን አእጋሪነ እምዳህጽ ወአዕይንቲነ እምአንብእ ወነፍስተነ እሞተ ኃጢአት ወደምረነ ምስለ እለ ድኅኑ ብከ በጸሎተ ኩሎሙ እለ እምዓለም አሥመሩከ” የሚለውን ንባብ ያቀፈውን ሊጦን ጸለዩ:: (ሊጦን ዘሠርክ) ይህም ማለት፥ “አምላካችን ሆይ! በፍልሚያ ውስጥ ገብተን ስንዋጋ ተደናቅፈን ከመሸነፍ ጠብቀን:: ጠላቶቻችንን ስናሳድድ አንዳልጦን ከመውደቅ አድነን:: እንባ ከማፍሰስም ተዋርዶ ከመሞት አድነን:: ባንተ ታምነው ባንተ መከላከል ከሚድኑት ጋራ ደምረን

 ከዚያ በኋላ ከነቢዩ ዳውት ድርሰት (መዝ ፶፱፡፩-፭) ላይ ያለውን

“እግዚኦ ገደፍከነ ወነሠትከነ፥
ቀሰፍከነሂ ወተሣሀልከነ
አድለቅለቃ ለምድር ወሆካ
ወፈወስካ ቁስላ እስመ አንቀልቀለት
አርአይኮሙ ዕጹባተ ለሕዝብከ

ወአስተይከነ ወይነ መደንግጸ” የሚለውን በክስተት መልክ ከተቀባበሉ በኋላ ከዚያ ቀጥሎ ያለው ንባብ 

          “ወወሐብኮመ ትእምርተ ለእለ ይፈርሁከ
          ከመ ያምሥጡ እምገጸ ቅስት
          ወይድኀኑ ፍቁራኒከ” የሚለውን ዲያቆኑ መስቀሉን ይዞ ከፍ ባለ ድምጽ አሰምቶ እንዲያዜም አደረጉ:: ይህም ማለት የችቦውን ዘዴ እንደመከላክያ ጋሻ አርገን እንድንጠቀምበት አስተማርከን:: ከጣላቶቻችንም ጋራ ፊት ለፊት ተጋጥመን ጠላት ከሚወረወርብን ጦር እናመልጥ ዘንድ የችቦውን መብራትና የምንጠቀምበት ሰአት ገለጽክልን የሚለውን መንፈስ የያዘ ነው:: የታሪኩ መነሻ በተብራራ ሁኔታ ለሕዝብ አልተነገረም እንጅ ይህ እስከ ዚህ የገለጽኩት ሁሉ በያመቱ በየደመራው በዓል ላይ አመታዊ ሥርዓት ሆኖ ይካሄዳል::
አምና ለዘመነ ሉቃስ “የተወደደችውን የጌታን ዓመት እንስበክ” በሚል ርዕስ ባቀረብኳት ጦማር (http://www.medhanialemeotcks.org/pdf/ethiopian_new_year_zemene_lukas.pdf) ስለ መንፈሳዊው አባት ሚና ስገልጽ፥ “አምላኩን ወዶ ለማስወደድ፥ ሃይማኖቱን አክብሮ ለማስከበር፡ በህዝባዊ ፍቅር ልቡ የነደደ፥ ቅዱስ ተብሎ የተሰየመ አባት፡ የምሕረት ምንጭ በሆነው አምላክ ስም፡ በሚያቀርበው የምሥራች ቃል:: ዘመኑን ባርኮ ለሥጋውያን መሪዎች አውደ ምህረቱ ይለቅ ነበር” እንዳልኩት፥ በደመራው በዓልም፥ የሚቃጠልበት የእሳት ምንጭ በካህኑ እጅ ያለው ችቦ ነው:: መጀመሪያ “ደምረነ ምስለ እለ ይድኅኑ” ብሎ የሚጸልየው ያካባቢው ካህን የመጀመሪያዋን እሳት በእጁ ባለው ችቦ ላይ ይጭራታል:: ካህኑ ካቃጣላት ችቦ ላይ የአገሪቱ ሥጋዊ መሪ በራሱ ችቦ እሳቱን እንዲለኩስ ይፈቅድለታል:: የአገሪቱ መሪም እሳቱን በካህኑ እጅ ላይ ካለው ችቦ በችቦው ለኩሶ በደመራው ላይ መለኮሱን ይመራል:: በተዋረድ የተከበሩ የአገር ሽማግሌዎች ይቀጥላሉ:: ከዚያ ጎረምሳው፥ ኮበሌው ወጣቱ እሳቱን በችቦው እየተቀባበለ ወደ ደመራው እየወረወረ የጀግንነት ምልክቱን ብትር ከፍ አድርጎ ይዞ ሆ! እያለ ደመራውን ይዞራል::
ቁርጥ የሚባል ስም ተሰጥቶት ጥሬ ሥጋ መብላት የተጀመረውም በዚሁ ዘመን ነው:: በሌሎች ክፍላተ ሐገሮች የሚደረገው ተመሳሳይ መሆኑንና አለመሆኑን ባላውቅም፥ ባደግኩበት አካባቢ ቁርጥ ሥጋ ወንዶች ብቻ ሲበሉ እንዳየሁ ሁሉ፥ በደመራው በዓልም ዳቦት(ችቦ) አብርተው ከቤት የሚወጡት ወንዶች ብቻ ናቸው:: ወንዶች ብቻ የሆኑበትን አባቶች ሲናገሩ እንደሰማሁት፥ “ብርሃን ዘበ አማን ዘያበርህ ለኩሉ ሰብዕ” የተባለው በጨለማ ለነበረው ዓለም ያበራው፥ ያለ ወንድ ዘር ወንድ ሆኖ የተወለደው ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው::
እመቤታችንእመ ብርሃን (የብርሃን እናት) ምሥራቅ (መውጫ)” እንጅ ብርሃን አይደለችም:: ይሁን እንጅ በማሕጸኗ አድሮ ወልዳው በሄደችበት ሁሉ ታቅፋ ያቋረጠችውን ዘመን በደመራው በዓል ይታወሳል:: በደመራ በዓል አጋጣሚ ሆኖ የቤቱ ባለቤት በሞት ወይም በሆነ ነገር በቤት ውስጥ ከሌለ፥ በእናቱ እቅፍ ያለ ወንድ ሕጻን በእናቱ እጅ ችቦውን (ዳቦቱን) እያበራ ከቤት ይወጣል:: ሴት ብቻ ከሚኖሩበት ቤትም፥ ከጎረቤት ወንዶች ልጆች አንዱ አብርቶ እንዲወጣ የሚደረገውም ይህን ለማስታወስ ነው::
ከፖርቹጋሎች ጋራ በተፈጠረው ታሪካዊ ክስተት ላይ፥ በዚያች ሌሊት ችቦ እያበራ ወጥቶ ፖርቱጋሎችን የደመሰሱት ወንዶች ብቻ ስለሆኑ፥ የመታሰቢያነቱ ገጽታ ተለጥጦ መልኩን እንዳይለውጥ ሴቶች ችቦ አብርተው ከመውጣት ተቆጥበዋል:: ይህ በእሌኒ የተጀመረ በዓል፥ በኢትዮጵያውያን ከትውልድ ወደ ትውልድ እንደሐረግ እየዘመተ በቅኝ ገዥዎች ሳይቆራረጥ በደማችን በምግባችን በስሜታችን ሳይቀር ተቀርጾ ለረዥም ዘመን በመቀጠሉ፥ የታሪክና የባሕላችንን  ምዕራፍ እያሰፋ እስከኛ ዘመን ደርሷል::
ትውልድ በውጭም ሆነ ባገር በቀል ወራሪዎች ተወሮ፥ ተበታትኖና ቋንቋውን ታሪኩንና ባሕሉን እንዲረሳው ካልተደረገ፥ ታሪኩ በግልጽ እየተነገረው በያመቱ የደመራው ሥርዓት ከቀጠለ፥ እየተፈራረቀ የሚገጥመውን ሁሉ እያባዛእየደመረ ባህሉንና ታሪኩ እየሰፋ ይሄዳል:: ይህ የደመራው በዓል ይዘቱን ሳይለቅ፥ ከታሪካችን ጋራ ያለው ጥምረት ለትውልዱ በግልጽ እየተነገረ እንዲቀጥል፥ ጠንካራ መመሪያ የመስጠቱ ኃላፊነት የመንፈሳዊና የፖለቲካ መሪዎች ቢሆንም፥ ከመንግሥት ይልቅ በላቀ ሁኔታ ኃላፊነቱ የሚመለከታቸው ወላጆችንና፥ ሽማጎሌዎችን ነው::

የመጀመሪያዋን የደመራውን እሳት የሚለኩሳት ማነው?

                   

“ደምረነ ምስለ እለ ይድኅኑ” የሚለውን ሊጦን ጸልዮ ባርኮ የደመራዋን እሳት ለአገሪቱ መሪ የሚያቀብላት ካህን ማነው? ከካህኑ ተቀብሎስ የደመራውን እሳት በማቃጠል የሚመራው የአገሪቱ መሪስ የትኛው ነው? ሥርዓቱን ተከትለው በእጃቸው ያለውን የደመራ ችቦ እያቀጣጠሉ ወደ ደመራው መጨመር የሚችሉትስ ሽማግሌዎች የትኞቹ ናቸው?
          መተርጉማን አባቶች በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ፪ ቁጥር ፮ ላይ “ስድስቱ መሳብክት እለ እብን በዘ ያጥህሩ ቦቶን” ተብሎ በሚነበበው አረፍተ ነገር፥ ታሪክን ሃይማኖትንና ባህልን ይገልጹበታል:: ክርስቶስ የቃናውን ውሐ ወደ ወይን የለወጠባቸው ጋኖች የተሠሩት “ዕብነ አልማስ” በሚባል ማዕድን ከቀለጠ ድጋይ ነው:: ይህ የከበረ ማዕድን ድንጋዩን ሰብስበው ሲያቀርቡለት ያቀልጠዋል:: በሱም ድንጋዩን እያነጡጡ፥ እየላጉ፥ በፈለጉት ቅርጽ ይሠሩታል::
ሰውም ከምንቼትነትና፥ ከቶፋነት እየተላቀቀ ወደ ጋንነት ለመድረስ ማንጠጫ፥ መላጊያና መቅረጫ “ዕብነ አልማስ” አለው:: ለተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ የመጀመሪያውና ቀዳሚው “ዕብነ አልማስ”፥ መለኮቱን ከሥጋችን የደመረው ኢየሱስ ክርስቶስ ነው:: ተከታዮቹም ቅዱስ አትናቴዎስ “ቅትራተ ሐጺን ዘኢያንቀለቅል” ብሎ የገለጻቸው ሕዝቡ በእምነታቸው በሞራላቸው አምኖ የሚሰማቸው ካህናት ናቸው:: ቀጥሎም “በሃይማኖት በታሪክና ባባሕል ምስክርነታቸው በእውቀትና በሞራላቸው በቤተ ክርስቲያን ዙርያ የተሰለፉ ያገር ሽማግሌዎች ናቸው” ይላሉ ሊቃውንት አበው:: ሲያብራሩትም፥ ሕጻን ሃይማኖት ታሪክና ባህል ይዞ አውቆና ተምሮ ከናቱ ማህጸን አይወጣም:: ክርስቶስ እንዳለውም በሥጋ አልሚ ምግብ በዳቦ ብቻ ሰው አያድግም:: Fast Food Nation እንዳይሆን ማለት ነው:: ትውልድ ሃይማኖቱን፥ ታሪኩንና ባህሉን ለይተው በተረዱ ባባትና እናት፥ በሐገር ሽማግሌዎችና በመንፈሳዊውያን መሪዎች እየተነጠጠ፥ እየተላገና እየተቀረጸ ማደግ አለበት::
ከካህናትና ከፖለቲካ መሪዎች በመቀጠለ የነ አብርሃምን የነ ይስሐቅንና የነ ያዕቆብን ምሳሌ የያዙ ዕብነ አልማሶች የሚባሉት ያገር ሽማግሌዎች ነበሩ:: በፖርቹጋሎች ምክንያት ምዕራፉን አስፍቶ ከኛ ዘንድ የደረሰው የመስቀሉ በዓል፥ እምነትና ሞራል ተንተርሰው፥ እውነትን እየፈለጉ ያለፉትን ከእሌኒ በፊት የነበሩትንና በዓለም ያሉትን ሁሉ አርበኞች ዕብነ አልማሶች እያልን እንድናስታውሳቸው አድርጎናል:: ለምሳሌ “ተዘከሮሙ እግዚኦ ለኩሎሙ አበዊነ ወአኀዊነ ወአኃቲነ እለ ኖሙ ወአዕረፉ በርትዕት ሃይማኖት ወደምር ነፍሳቲሆሙ ውስተ ሕጽነ አብርሃም ይስሐቅ ወያዕቆብ” ማለትም፥ “ሳይወላውሉ በቀናች እምነት ጸንተው ለወገናቸው ለነጻነታቸው መስዋዕት እየከፈሉ ያለፉትን አባቶቻችንን፥ ወንድሞቻችንን እናቶቻችንና እኅቶቻችንን በአብርሃም በይስሐቅና በያዕቆብ ሕጽን አንድ ላይ ሰብስብልን” እያልን በቅዳሴያችን እንጸልያለን::
እነ አብርሃምን ዕብነ አልማሶች የምንልበትን ምክንያት፥ በኢትዮጵያ መንበር ላይ ቆሞ የሚቀድስ ካህን ሁሉ ክህነቱን ከመቀበሉ በፊት ከሊቃውንት ሊማረውና ጠልቆ ሊረዳው ይገባዋል:: “በአንተ አሕዛብ ሁሉ ይባረካሉ” ተብሎ ለአብርሃም ወንጌል የተሰበከለት፥ “ወበጽሖሙ ሌሊተ ምስለ ደቂቁ ወቀተሎሙ ወዴገኖሙ እስከ ባኮር እንተ እምጸጋማ ለደማስቆ”( ዘፍ ፲፬፡ ፲፭) ማለትም፥ “አብርሃም አርበኞቹን አሰልፎ በእምነት ተሰልፎ ድልን ከተጎናጸፈ በኋላ ነው:: እነ ያዕቆብንም ቅዳሴው የሚያነሳሳቸው “ወለዛቲ ምድር እንተ ወሀብኩ ለአብርሃም ወለይስሐቅ ለከ እሁበከ ወለዘርእከ እምድኅሬከ” (ዘፍ ፴፭፡፲፪-፲፬):: ከሚለው ባሻገር “ወአቀመ ያዕቆብ ሐውልተ ውስተ ውእቱ ብሔር ኀበ ተናገሮ”(፴፭፡፲፬) ማለትም፥ “ያዕቆብ እግዚአብሔርን ባናገረበት ቦታ ላይ የድንጋይ ሐውልት አቆመ” የሚለውን ገጸ ንባብ መሠረት በማድረግ ነው::
ያዕቆብ እግዚአብሔርን ባናገረበት ቦታ ሐውልት ያቆመበት ምክንያት፥ ቦታውን ቤተ-ኤል (የእግዚአብሔር ቤት) ለማለት እንጅ፥ እንደ ዘመናችን ፓትርያርክ፥ እንደ ማክዶናል ፋስት ፉድ እየተገላበጡ ትላንት ሌላ ዛሬ ሌላ  ከሚናገሩትና ከሚያደርጉት ጋራ በመገለባበጥ የራስን ቅርጽና ዝና በህዝቡ ልቡና ለማስረጽ አይደለም:: ያዕቆብ የተከለው ድንጋይ ያነበበውን ሁሉ እስከኛ ዘመን ድረስ እየናጠጠና እየላገ ያለና የሚቀጥል ነው:: በዚህ ታሪካዊ ባሕርያቸው እነ ያዕቆብን መጽሐፈ ቅዳሴያችን ይጠቃቅሳቸዋል:: ቅዳሴያችን “ወለነኒ አድኅነነ እምኩሉ አበሳ ወመርገም ወእምኩሉ ጌጋይ ወእምኩሉ ክሕደት ወእምኩሉ መሐላ በሐሰት ወእምኩሉ ግዘት ወእምተደምሮ በዕልወት ወርኩስ ምስለ ዓላውያን ወአረማውያን በማለት ከከሐዲዎች ከሸፍጠኞችና ከአስመሳዮች ጋራ ከመደመር እራሳችንን እንድንጠብቅም በጽኑዕ ያሳስበናል::
ይሁን እንጅ ያገር ሽማግሌዎች በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት እራሳቸው እየተነጠጡ ካላደጉ፥ የሰውነታቸው እርጅና የጸጉራቸው መሸበት ብቻ የአገር ዕብነ አልማስ ሊያደርጋቸው አይችልም:: ይልቁንም በእርጅናቸውና በሽበታቸው ጎጠኝነትን፣መንደርተኛነትንና፣ ሸፍጠኛነትን በመስበክ የሚከተላቸውን ትውልድ ፈጣን ምግብ (Fast Food Nation) የሚያደርጉ የሕብረተሰብ ነቀርሳዎች ስለሆኑ፥ ትውልዱ የሚያደርጉትንና የሚናገሩትን በጥንቃቄ ሊያጤነው ይገባል:: “ፍልሰታ” በሚል ርዕስ ያቀረብኳት ጦማር ይመልከቱ::(http://www.medhanialemeotcks.org/pdf/Filseta%20Final.pdf)
 ጊዜ ሲበላሽ የሀገር ሽማግሌዎች ከደመራ ሆታ ባሻገር የደመራውን ምሥጢር ለመረዳት የተሳናቸው ሕጻናት ይሆናሉ:: ይህን ሳያስተውሉ ስለደመራው በዓል የሚሰብኩ፤ የደመራውን ችቦ ባርከው እሳቱን የሚለኩሱ ካህናትም፥ ከሆታው ባሻገር ያለውን የደመራውን ምሥጢር ከሊቃውንት አበው ሰምተውት ካላወቁ፥ ከሕጻነ አዕምሮ ገና ያልተላቀቁ ይሆናሉ::ደመራው ምሥጢር ተቃራኒ የሆኑትን ቅነሳንከፈላን ለሚያርምዱ አጫፋሪ በመሆንም ሆባዮች ይሆናሉ:: (በግዕዝ ሆባይ ማለት ዝንጀሮ ማለት ነው)
ችቦ አብርቶ ትኋንን ውጪ፥ ቁንጫን ግቢ ለማለት መጀመሪያ በደመራው እንጨት ውስጥ መወከልን ይጠይቃል:: ቀጥሎም የሚያበራው ችቦና የሚያቃጥለው የደመራው እሳት፥ ተቃራኒ በመሆን ለመክፈልና ለመቀነስ የመጣውን የፖርቱጋሎች ስሜት የተሸከመውን የሚያቃጥል፥ ከሰልና አመድ የሚያደር፥ በእምነታቸው በሞራላቸው ጸንተው ለቆሙት ኢትዮጵያውያ ግን የሚያበራ፥ የሚያሞቅና የሚያደምቅ እሳት መሆኑንም መረዳት ያስፈልጋል::
ከችቦውና ከደመራው ጋራ አብራ የገባች በአጥርና በዛፍ ስር የምትበቅል በአማርኛ አሽክት (ትድምርት ዘእንበለ ፍልጠት) ትግርኛ ጸጎጎት የምትባል ጥልቅ ትርጉም ያላት ሐረግ አለች:: ይሕች ሐረግ መረሳት የሌለባት በዚያ ዘመን ትልቅ ሚና የተጫወተች ናት:: ፓርቹጋሎች አንድነታችንን አፍርሰው ሊለያዩን አይችሉም በሚል ጽኑዕ ውሳኔ የተስስማማ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ዘመቻው ከመጀመሩ በፊት እንደ ልዩ መግባቢያ ሆና አገልግላለች:: እኔ ካገር ቤት የመጨረሻውን ደመራ አክብሬ ወደ ደብረ ሊባኖስ እስከሄድኩበት ዘመን ድረስ ልጆች ሆነነ በራሳችን እናደርጋት ነበር:: እናቶችና ሽማግሌዎች ደግሞ ለቁርጥማት መድኃኒትነት አላት እያሉ በደመራው አመድ ላይ  ጎዝጉዘው ይቆሙባት ነበር:: የደመራው እንጨት እርጥብና ደረቅ ነው:: “በርጡብ እጽ ለእመ ኮነ ከመዝ እፎ በይቡስ” እንዳለው ክርስቶስ፥ ርጥቡ እንጨት ባሕርዩን፥ እሱነቱን ያልቀየረ፥ በቀላሉ ለእሳት ያልተጋለጠ ወገን ነው:: ቢጎዳም ለወገን ነው:: የሚወክለው ቁርጠኛውን ዜጋ ነው:: ደረቁ እንጨት ባሕርዩን የቀየረውን፥ እራሱን ከወገኑና ከታሪኩ አግልሎ አድር ባይና ወላዋይ የሆነውን፥ በአስመሳይና በሸፍጠኛ ባሕርዩ ከፖርቹጋሎች ጋራ የወገነውን ዜጋ ይወክላል::

“አጓጉረውና እርጥቡን ከደረቅ፥
           እዚያው ጤሶ ጤሶ እዚያው ነዶ ይለቅ” የሚለው ሽለላ (ቅራርቶ) የመነጨውም ከዚህ ነው

ይባላል::
          የደመራው በዓል ይህን አስደናቂ ምሥጢር ያዘለ ከሆነ፥ “ደምረነ ምስለ እለ ይድኅኑ” ብሎ ይህን ምሥጢር በቃሉ ያስተማረ፥ በተግባሩ ያከናወነ የደመራዋን እሳት ችቦ የሚባርካት በዘመናችን የትኛው ካህን ነው? ከካህኑ ለኩሶ ደመራውን በመጀመሪያ የሚያቀጣጥለው መሪስ የትኛው ነው? ወጣቱንስ በየመንደሩና በየቤቱ በዚህ ኢትዮጵያዊ እምነት ታሪክና ባሕል የሚቀርጽ፥ የሚልግና የሚያስተካከል የትኘው ያገር ሽማግሌና የቤተ ሰብ ሐላፊ ነው?
ዛሬ ከመቸውም ዘመን በከፋ ሁኔታ የተዋሕዶውን ሃይማኖት አፍርሰው፥ በፖርቹጋላዊ ከፈፋይ መንፈስ ለመተካት የሚታገሉ አስመሳዮች ደፍረው ወደ ቤተ መቅደሳችን የገቡበት ዘመን አይደለምን? ከሃይማኖቱ፥ ከታሪኩና ከባሕሉ ይልቅ ለመንደርተኝነት ቅድሚያ በመስጠት ከሀዲዎች መሆናቸውን እያወቁ ድጋፍ ለመስጠት ሽንጣቸውን ገትረው የተነሱ ሽማግሌዎች የተከሰቱበት ዘመን አይደለምን? በአገሩቱ ላይ የሚካሄደውንስ የፖለቲካ ዘይቤ ስንመለከተው በአድዋ ላይ ሥር ሰዶ የነበረው “ዓኾ ዓኾኋይ ሆይ ሆያዬ ንጎናይ በርሆ” በማለት ኢትዮጵያውያን ያባረሩት ፖርቹጋላዊ የፖለቲካ መርሆ፥ ዛሬ መልኩን ለውጦ በነ አቶ መለሰ አማካይነት ኢትዮጵያን የተቆጣጠረበት ዘምን አይደለምን?
እነዚህ ካላይ በጥያቄ ያቀረብኳቸው መጠይቆች፥ እውነትም የወቅቱ መጠይቆች ናቸው ብለን ተስማምተን ከተቀበልናቸው:: የቀደሙ ሊቃውንት አበው በመጽሐፈ መሳፍንት ምዕ ፱ ከቁጥር ፳ ላይ የሰፈረውን “ለትጻዕ እሳት እምቤተ አቤሜሌክ፥ ከመ ትብላእ አብያተ ሴኬም፡ ወትሜሎም:: ወለእመ አኮ እሳት ትጻእ እምቤተ ሴኬም ወትሜሎም ከመ ትብላዕ ቤተ አቤሜሌክ” የሚለውን ተመርኩዘው፥ ማለትም “እኛ ኢትዮጵያውያን በገዛ አገራችን የተደጋገመ ግፍ እየተፈጸመብን ነው:: ይህች ከኢትዮጵያውያን ቤት እየተጫረች የምትወጣ የዘንድሮው መስቀሉ በዓል እሳት፥ በሸርና በሸፍጥ በእርዳታ ስም መጥተው የወረሩንን ፖርቱጋሎችን ትብላ፥ ለአገራችን ለነጻነታችን መታገላችን በአምላክ ዘንድ ተቀባይነት አጥቶ ረድኤቱን ከነፈገንም፥ ለዘላለም በፖርቱጋሎች ሥር ተጠቅተን ከመኖርና ለልጆቻችንም የተገዥነትን ውርስ ከማውረስ ይሕች ከየቤታችን የጫርናት እሳት እኛኑ ትብላን” ብለው ቆርጠው የተነሱበትን ያባቶችን መንፈስ ልንቃኘው ይገባናል::
የጥንት ኢትዮጵያውን ችቦውን አንድ ላይ አስረው፥ እንጨቱን አንድ ላይ ደምረው ያቃጠሉት፥ ዛሬ እኛ እንደምናደርገው በጎሳ በቋንቋ፥ በሃይማኖት፥ ከውጭ ሠርሥሮ በገባ ሃይማኖትና በተለያዩ የፖለቲካ ትርጓሜ በመለያየት አልነበረም:: ደመራውን ችቦውን ትንሿን አሽክት እንኳ ሳይቀር ላንድነታቸው ምልክት በመጠቀም ነበር:: እግዚአብሔር “ደምረነ ምስለ እለ ይድኅኑ” እያሉ የደመራውን እሳት የሚያበሩ ካህነት፥ “ትኋን ውጭ፡ ቁንጫ ግቢ” እያሉ የደመራውን ችቦ የሚያበሩ ሽማግሌዎች፥ የካህኑንና የሽማግሌዎችን ምኞት በሆታ የሚያስተጋባ ትውልድ እንዲፈጠር እንጸልይ::
ለዚህ ዓመት የደመራ በዓል ያደረሰን አምላክ፥ ለከርሞውም በሰላምና በጤና ጠብቆ  ያድረሰን::

ለሌሎች ቀሲስ አስተርአየ ጽጌ ጦማሮች የሚከተለዉን ድህረ-ገጽ ይመልከቱ::