Tuesday 13 March 2012

በአደባባይ መዘባረቅ መብት አይደለም! ቁልቁለቱን ለብቻ

ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም

ከአጼ ኃይለ ሥላሴ ወዲህ የመጡት ገዢዎች የታሪክ አዋቂዎች ለመምሰል የሚጥሩ ናቸው፤ ምክንያቱን በኋላ እናየዋለን፤ በቅርቡ ኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለ ማርያም ትግላችን የሚል ትልቅ መጽሐፍ አሳትሞአል፤ እዚህ ደሞ አቶ ስብሐት ነጋ አክሱም ለተንቤንና ለአጋሜ ምኑ ነው በማለት አዲስ የኢትዮጵያ ታሪክ ነግሮናል፤ የጎሠኛነት አስተሳሰብ እየጠበበና እያጠበበ መሄዱ የታወቀ ነው፤ እስቲ ስብሐት ተናገረ የተባለውን ፍሬ-ገለባነትን ትተን ያስተሳሰቡን አድማስ ቆንጠር አድርገን እንየው፡፡
‹‹ታሪክና የፖለቲካ አቋም ይለያያል፡፡ የተናገርኩት እኔ የማውቀውን ታሪክ ነው፡፡ ታሪክ አውቃለሁ የሚል ደግሞሊ ያጣራው ይችላል፡፡ ታሪክ የፖለቲካ አቋም ስላልሆነ ተነቦ ሊስተካከል ይችላል፡፡እኔ እንደሚመስለኝ የአክሱም መንግሥት በመጀመሪያ ደረጃ የ ከተማ   መንግሥት  ይመስለኛል፡፡እንደነ አቴንስ እንደነ እስፓርታ የከተማ መንግሥት ይመስለኛል፡፡›› ሰንደቅ የካቲት 14 2004

እነዚህ ስድስት ዓረፍተ ነገሮች አቶ ስብሐት ነጋ በተጠቀሰው ጋዜጣ ላይ የተናገራቸው ናቸው ተብለው የወጡ ናቸው፤ ዛሬ ሁለት ሳምንት ሊሆነው ነው፤ ስብሐት ነጋ አላስተባበለም፤ አንዳንዱን ዓረፍተ ነገር ለየብቻው እንየው፤--

1. ታሪክና የፖለቲካ አቋም ይለያያል፡ ፡ እስማማለሁ፤ ምንም ቅሬታ የለኝም፡፡


2. የተናገርኩት እኔ የማውቀውን ታሪክ ነው፡፡ ችግር አለ፤

ሀ)ስብሐት ነጋ የሚያውቀው ታሪክ ወላጆቹ ከሚያውቁትና እኛ ከምናውቀው ታሪክ እንዴት ተለየ? እኛ ተማሪ ቤት አልሄድንም፤ ወይ እሱ ተማሪ ቤት አልሄደም፤ ወይ የእኛ እውቀት በልፋት የተገኘ ሲሆን የእሱ በመንፈስ ኃይል የተገለጠለትና የታየው ነው፤ ወይ ስለጉዳዩ የተጻፉትን መጽሐፍት አላነበበም፤

ለ)የተናገርሁት እኔ የማውቀውን ነው ማለት ምን ማለት ነው? አንድ ሰው አራትና አራት ስድስት ነው ከአለ በኋላ የተናገርኩት እኔ የማውቀውን ሂሳብ ነው ቢለን ምን እንለዋለን? ድንጋይ ቢበሉት ያጠግባል ብሎ ከተናገረ በኋላ የተናገርኩት እኔ የማውቀውን ነው ቢለን ምን እንለዋለን?

3. ታሪክ አውቃለሁ የሚል ደግሞ ሊያጣራው ይችላል፤ አውቃለሁ ያለው ስብሐት ራሱን መጠራጠር የጀመረ ይመስላል፤ በታሪክ እውቀት ከስብሐት የሚበልጥ ሰው ከአለ ጉዳዩን እንዲያጣራው ፈቃድ ይሰጣል፤ በሌላ በኩል ደግሞ አንድ ሰው ከአነበበና ከተመራመረ ስብሐት ወደደረሰበት መደምደሚያ ሊያደርስ ይችላል ማለቱ ይሆናል፡፡

4. ታሪክ የፖለቲካ አቋም ስላልሆነ ተነቦ ሊስተካከል ይችላል፤ የአስተሳሰብ ችግሩ ምንጭ እዚህ ላይ ነው፤ ይህ ዓረፍተ ነገር በቅርጹም በይዘቱም ፉርሽ ነው፤ ሊስተካከል የሚችለው ታሪክ ነው? ወይስ የፖለቲካ አቋም? በስብሐታዊ አስተሳሰብ የፖለቲካ አቋም አይነቃነቅም፤ አይለወጥም፤ ታሪክ ግን ሊለወጥ ይችላል፤ በስብሐታዊ አስተሳሰብ የፖለቲካ አቋም ሃይማኖት መሆኑ ነው፤ ስለዚህ አይለወጥም፤ ይችላል፤ ለስብሐት ከራራንለት ስለታሪክ የሚያነብ ሰው የበለጠ ሲያውቅ ራሱን ያስተካክላል ብለን እንተረጉምለታለን፤ ለስብሐት ካልራራንለት ደግሞ ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት የሆነውን ታሪክ እናስተካክለዋለን ማለቱ ስለሆነ ልክ አይደለም እንላለን፤ በሌላ አነጋገር ታሪክ በስብሐት አስተሳሰብ ይስተካከላል፤ በጣም ግልጽ ለማድረግ፣ ስብሐታዊ አስተሳሰብ የሚለው ያለፈውን፣ ያላየነውንና በቀጥታ የማናውቀውን መለወጥ እንችላለን፤ የወደፊቱን፣ ያልደረስንበትን፣ እኛ ራሳችን እየሰራን ያለነውን ግን ልንለውጠው አንችልም!

5. እኔ እንደሚመስለኝ የአክሱም መንግሥት በመጀመሪያ ደረጃ የከተማ መንግሥት (City state) ይመስለኛል፤ እዚህ ላይ ታሪክን ወደተረት የመለወጥ ዝንባሌ መጣ፤ አክሱምን እንደነገሩ እንኳን የማያውቅ ሰው ባሕር ተሻግሮ ስለአቴንስና ስለስፓርታ እንደነገሩ እንኳን የማያውቀውን ቢጨምርበት ወደታች እንጂ ወደላይ የሚወስድ መንገድ አያገኝም፤ የየጁ ደብተራ ቅኔ ቢጎድልበት ቀረርቶ ሞላበት እንደሚባለው የማይገናኙ ነገሮችን ማገናኘት ነው፤ ወይም በአፈር ቡኮ ቂጣ ለመጋገር አይቻልም፡፡)

አንድ ሰው እንኳን ሳይገደድ ተገዶስ ቢሆን የማያውቀውን ነገር ለምን ይናገራል? አንድ ጊዜ ግቢ በአስቸኳይ ድረስ ተብዬ ሄድኩና ጃንሆይ ፊት እጅ ነሥቼ ስቆም፣ ‹‹የት›› ስለሚባል ኦጋዴን ውስጥ ያለ መንደር ጠየቁኝና እንደማውቀው ከተናገርሁ በኋላ በ‹‹የት›› የሚገኘው የውሃ ጉድጓድ በቀን ስንት በርሜል ውሃ ይወጣዋል? ብለው ጠየቁኝ፤ ‹‹ጃንሆይ አላውቅም፤›› አልሁ ደጋግመው ግምት ጠየቁኝ መልሴ ያው አላውቅም ሲሆንባቸው ‹‹ሂድ ውጣ!›› አሉኝ፤ የማላውቀውን ለምን ልዘባርቅ የኢትዮጵያን ታሪክ አጥርቶ ሳያውቅ ጭራሹኑ ወደማያውቀው ወደ ጥንቱ የግሪክ ታሪክ ምን አስኬደው!

ታሪክ በአጥንትና በደም የተገነባ መቅደስ ነው፤ ታሪክ የስንትና የስንት ትውልዶች የተጋድሎ፣ የፍቅርና የቃል ኪዳን፣ የኩራትና የክብር፣ የመብትና የግዴታ ገድል ነው፤ ታሪክ መዝገብ ነው፤ ምስክር ነው፤ ታሪክ የህልውና መሠረት ነው፤ ማንነት ነው፡፡

በአለፉት አርባ ዓመታት ውስጥ የኢትዮጵያ ታሪክ ከፋሺስት ኢጣልያ ዘመን ያላነሰ ውርደት ደርሶበታል፤ አምባ-ገነኖች ታሪክን የሚያነሡት የወደቀውን ለመቅበርና ሁልጊዜም በግልጽ እንደሚሉት ‹‹በመቃብሩ ላይ ለመቆም›› ነው፤ ከዛሬ በፊት የነበረውን ሁሉ በማራከስ፣ በማጥላላት፣ በማናናቅ፣ በማፍረስ ታሪክ ነገ እንደሚጀምር የተስፋ ዳቦ መጋገር ለአለፉት አርባ ዓመታት የተለመደ ሆኖ እያሰለቸን ነው፤ የትናንቱ ታሪክ በትንንሽ ሰዎች እንደማይደመሰስ ሁሉ የነገውም ታሪክ በትንንሽ ሰዎች አይገነባም፡ ፡

ትናንትን ያላግባብ እያራከሰ ለመቅበር የሚጥር ሁሉ ዛሬን ትናንት ያደርገዋል፤ ትናንትንና የትናንትን ኃይል ከነድካሙ በትክክል ያልተገነዘበ የሚቆምበት መሬት አያገኝም፤ የሚንደረደርበትም ሆነ የሚንደረደርለት ዓላማ የለውም፤ ከሆዱ በቀር የሚሞትለት ወይም የሚሞትበት ዕዳ የለውም፤ እንደእውነቱ ከሆነ ግን ሁላችንም የታሪክ ዕዳ አለብን፤ ጥንት ከተለያዩ ቄሣራውያን ኃይሎች ጋር አባቶቻችንና እናቶቻችን የፈጸሙትን ተጋድሎ እንርሳው፤ ከሰባ አምስት ዓመት በፊት ከፋሺስት ኢጣልያ ጋር ለተደረገው ትግል የተከፈለውን መስዋዕትነት እንርሳው፤ ለመቋቋም የተከፈለውን መስዋእት እንርሳው፤ የቅርቡን የባድመን እንዴት ልንረሳው እንችላለን? በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች የጅብና የአሞራ ምግብ ሆነው የቀሩት በእውነት ለቁራጭ መሬት ብቻ ነው? የአድዋ ክብርና ኩራት፣ የማይጨው ውርደት የለበትም? እንደስብሐት ነጋ ያለ በትልቅ የኃላፊነት ቦታ ላይ ያለው ሰው ይህንን ይስታል ለማለት ያስቸግራል፤ ስሕተት ካልሆነ ታሪክን በጎሣ ማጥበብ ዓላማው ምንድን ነው? አደጋ ሲመጣ እንኳን ከተምቤንና ከአጋሜ ጋር ከቦረናና ከኦጋዴንም ጋር የታሪክ ዝምድና መቁጠር አስፈላጊ ይሆናል፡፡
በወላጆቻችን የምናፍርበት ምክንያት ቢኖርም መንፈሳዊ ወኔያችንን አጠንክረን ህመማችንን ልንጋፈጠው ይገባል እንጂ ታሪካችንን በሙሉ በማራከስ ከሐፍረታችን አንድም፤ የአንድ ሰው ታሪክ የአንድ ሰው ታሪክ ነው፤ የአንድ ቤተሰብ ታሪክ የአንድ ቤተሰብ ታሪክ ነው፤ የአንድ አገር ታሪክ ደግሞ የተለየ ነው፤ የሁሉም ነው፤ ኩራትና ክብሩ የጋራ ነው፤ ውርደትና ሐፍረቱም የጋራ ነው፤ የግል ቁስልን አክካለሁ ብሎ አገርን ማቁሰል ተገቢ አይደለም፡፡

ትናንት ለዛሬው ሕይወት የሕይወት ዋጋ የተከፈለበት ነው፤ ዛሬ የትናንትን ውለታ ተሸክሞ የቆመ ነው፤ ይህ ሸክምና ውለታ ለእንደ ስብሐት ነጋና መሰሎቹ አይሰማቸውም፤ እነሱ የሚያውቁት የዛሬውን ምቾትና ጉልበተኛነት ነው፤ እነሱ የሚያውቁት የዛሬውን ማናለብኝነት ነው፤ አቶ ስብሐት ስለአክሱም ታሪክ የተናገረው (መናገሩን የማውቀው ባለማስተባበሉ ነው፤) በትምህርትም ሆነ በንባብ ያገኘው ነው ለማለት ይከብዳል፤ አለማወቁን የነገረን ስለአክሱም ብቻ ሳይሆን ስለከተማ ሀገረ-መንግሥቶችም (City state) ነው፤ በእርግጥ ለስብሐት አዲስ የሚባል ነገር ተናግሮአል፤ የተለየ ነገር የሚያውቁ ካሉ ያስተምሩ፤ ይናገሩ፤ በማለት ፈቅዶአል! ስለዚህ ልንጨክንበት አይገባም፤ ነገር ግን አንድ ጥያቄ ለመጠየቅ እንገደዳለን፤ ከመጠምጠም ትምህርት ይቅደም፤ የሚባለውን ስብሐት ሳይሰማ አይቀርም፤ ስለዚህ የማያውቀውንና እርግጠኛ ያልሆነበትን ዓቢይ የአገር ታሪክ ሞሽልቆ ራቁቱን አስቀርቶ በአደባባይ በጋዜጣ ለመናገር እንዴት ደፈረ? የማያውቁትን ነገር ለማወቅ መድኃኒቱ መጠየቅ ነው፤ ጥያቄ በመጠየቅ የሚወቀስ የለም፤ የማያውቁትን በአደባባይ መዘባረቅ ግን ከማስወቀስ አልፎ ያስንቃል፡፡

የአክሱምን ሀገረ-መንግሥት የአረብ፣ የኢጣሊያ፣ የፈረንሳይ፣ የእንግሊዝ፣ የሩስያ… ሊቃውንት ለረጅም ጊዜ አጥንተው ጽፈውበታል፤ እኔ በእጄ ስላሉ የጥናት ውጤቶች ለመናገር ነው እንጂ በጀርመንና በሌሎችም ቋንቋዎች ጥናቶች ይኖሩ ይሆናል፡፡

ታሪክ የቡና ቤት ወሬ አይደለም፤ ማን ጠያቂ አለብኝ በማለት አፍ እንዳመጣ እየተናገሩ ታሪክን ማወላገድ ለወጣቶችና ለትንንሾቹ ልጆች አለማሰብ ነው፤ አንድ ሰው ስለአክሱም ሀገረ- መንግሥት የምን ያህል ጊዜ ጥናት አድርጎ፣ የእነማንን ጥናት አንብቦ የአክሱምን ታሪክ በድፍረት ለመናገር ቻለ የሚለውን ጥያቄ ማንሣቱ ዋጋ የለውም፤ ምክንያቱም አንድ ነገር ወይም አንድ ሰው ከባሕርዩ ውጭ ሌላ ሊሆን አይችልም፤ ታሪክ ሰዎችን ለማስደሰት ወይም ለማዝናናት የሚነገር ተረት አይደለም፤ ምን ዓይነት ጥላቻና ጎሠኛነት ነው በድንጋይ ላይ የተጻፈውን ታሪክ ለመካድ የሚያስገድድ? እንደስብሐት ሥልጣንን እውቀት አድርገው ለሚገምቱ ሰዎች በ1996 በታተመው የክህደት ቁልቁለት መጽሐፍ ውስጥ የተለያዩ ሊቆች፣ የፈረንሳይና የአረብ፣ የኢጣልያም ሆነ የእንግልጣር ሳይቀር፣ ስለአክሱም የጻፉትን ጠቅሼ በአራት ገጾች ላይ ጽፌ ነበር፤ ሌላው ሁሉ ቀርቶ ያንን እንኳን ያላነበበ ሰው አንብቦ ስለማጣራት ይነግረናል፤ በተለያዩ ምክንያቶች የተጠቀሱትን መጽሐፍት ለማንበብ የማይችል ሰው ባይሆን ጥቅሶቹን አንብቦ ሌላውን ከማሳሳት መዳን ይችል ነበር፤ ሥልጣን አለኝ ተብሎ አለማወቅን በአደባባይ ማወጅ፣ ሕዝብን፣ በተለይም ወጣቱን ከጥንት ታሪኩ ጋር ለማቆራረጥ መሞከርና ማሳሳት ሊያሳፍር ይገባል፡፡

በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ውስጥ ሥልጣን በእውቀት ላይ ያለውን የበላይነት በግልጽ የሚያሳየን ከሠላሳ ሁለት ዩኒቨርስቲዎች (ዶር. ዳኛቸው እንዳለው ይህንን ያህል ካሉ) ውስጥ አንድም የታሪክ ሊቅ ለሙግት ብቅ አላለም፤ ሌላው ቀርቶ የኢትዮጵያ መካነ ጥናትም ትንፍሽ ሲል አልሰማሁም! ሁሉም በሆዱ ተሰንጎአል! እዚህ ላይ የስብሐት ድፍረት ይጠቅማል፤ ስብሐት ቢጠየቅ ስለጳጳሳቱ ያለውን ስለሊቃውንቱ ይደግመው ነበር፤ በመሀከላቸው አንድ ሰውም የለባቸውም እንደሚል አልጠራጠርም!

No comments:

Post a Comment