Tuesday 28 June 2022

ወይ ነገር መፈለግ፣ ወይ ዱቢ! ወይ ዱቢ!

ከወንድሙ መኰንን፣ ኢንግላንድ 26 June 2022

መግቢያ

ከአራት ዓመት በፊት የመጣው ለውጥ የተሻለ ነገር ይዞ ቢመጣ ብለን፣ ብዎቻችን ጓጉተን ነበር። ነገሩ ከድጡ ወደማጡ ሆነ። አሁንስ ግፉ በዛ! ማርም ሲበዛ ይመራል ይባላል። የኢትዮጵያ ጠላቶች ድሮም፣ ኢትዮጵያን የማጥፋት ጅማሮ፣ አማራን ከማጥፋት ቅዠታቸው ጋር ይያዛል። ኢትዮጵያን ለማጥፋት ሲባል ብቻ፣ የሌለ ምክንያት እየፈጠሩ፣ “አማራ” ተብሎ በተፈረጀ ምስኪን ብሔር ላይ ሲዘምቱበት ምዕት ዓመታት ነጎዱ። ያንን ለመገንዘብ፣ Abyssinia: The Powder Barrel  ተብሎ በBaron Roman Prochazka  የተጻፈውን መጽሐፍ ማንበብ ይበቃል። ጣሊያንም ያደረገው ያንኑ ነው። ደርግም ሲመጣ አቆርቋዥ በመባል ብዙ አማሮች ተፈናቅለዋል። ወያኔም ያንኑ ነበር ሥራ ላይ ያዋለው። አሁንም እያየነው ነው።

እስቲ እግዚአብሔር ያሳያቸው፣ “የኦሮሞ ደም ደሜ ነው” ብሎ ከወንድሙ ጎን ለቆመው አማራ ይኸ ይገባዋልግፍ ነው! የግፍ ዶፍ! የወያኔው ኢህአዴግም ሆነ፣ የኦህዴድ ብልጽግና ትኩረት፣ አሳምኖም ይሆን አወናብዶ፣ ያው የፈረደበትን አማራ የተባለ ብሔር ላይ መዝመት ሁኗል። አትኩሮ የ፣ ሦስት ነገሮችን ያስተውላል። ስልታቸው ተመሳሳይ ነው። ጠላቶቹ፣ አማራና ኦርቶዶክስ ሀማኖት ተከታይ ካገኙ፣ ሰኔና ሰኞ ገጠመላቸው ማለት ነው። የበደኖን፣ የአርባ ጉጉን፣ የወተርን ተውት ትንሽ ራቅ ብሏል። በቅርቡ የሆነውን እንይ! ከኬኛዎቹ አንዱ “ተከበብኩ” ብሎ ሲጣራ፣ ምክንያት ብቻ ይፈልግ የነበረው መንጋ፣ ብድግ ብሎ ስንቱን አማራ ነበር የጨፈጨው? ይኸ አንዱ ነው። ሌላው፣ አማራም ባይሆን፣ ኦሮሞም ይሁን ሌላ፣ ኦርቶዶክስ ሀይማኖት ተከታይ ከሆነ፣ እሱም አብቅቶለታል። ከአማራው ጋር ዕምነት ይጋራላ! ሰበብ ፈላጊዎቹ፣ ታዋቂ የኦሮሞ ዘፋኙን፣ ሀጫሉ ሁንዴሳን፣ ሰበብ ሲፈልጉ፣ ያልሆነ ነገር አናዘውት፣ እንሱው በግፍ ገድለውት፣ “ገደሉት” አሉና ግርር ብለው ተነስተው ስንቱን ጨፈጨፉት[1]። ያ ሰበብ ስንቱን አማራና ኦርቶዶክስ ሀይማኖት ተከታይ የሆነውን ለመጨፈጨፍ ዕድል ከፈተለተላቸው? በያለበት ማረድ አልበቃ ብሏቸው፣ ያወደሟት ሻሻማኔ እንደ ሰደሞና ገሞራ ስትታወስ ትኖራለች። ዝዋይ ከተማ ታርደው ደማቸው ደመከልብ የሆኑት ቤተሰብን ማን ይፋረድላቸው?  የሚገርመው፣ ወያኔ አሳዳቸው፣ ኢንግላንድ የደረሱ ጽንፈኞች፣ ለንደን ዘልቀው የንጉሥ ኃይለሥላሴን ሀውልት  አፍርሰዋል። ሶስተኛው፣ አንድ ሰው እስላምም ቢሆን በአማራነት ከተፈረጀ ለመጨፍጨፍ ተጋላጭ ሁኗል (ድሮ፣ ድሮ እንኳን፣ አማራ ማለት ክርስቲያን ማለት ነበር አሁን ግን ዘር አድርገውት አርፈውታል)። በዚህች ሳምንት እንኳን በድሮው ወለጋ፣ ጠቅላይ ግዛት/አስተዳደር ግምቢ ውስጥ የታረዱት 1,600 ንጹሀን ሰዎች የሚያረጋግጠው ያንኑ ነው። በሙሉ እስላሞች ነበሩ ማለት ይቻላል። ምን በድለው ነው አንደበግ አጋድመው ያረዷቸው? አይጥ በበላ ዳዋ ተመታ ይባላል። ጥላቸው ከመንግሥት ጋር ከሆነ፣ እንደጀግና ለምን ጦሩን አይፋለሙም? ሕጻናትንና ሴቶችን መጨፍጭፍ ቦቅቧቃ ፈሪነት ነው። የጥላቻ ጥግ በዛ! በዛ! በዛ!

የመንግሥት የመጀመሪያው ኃላፊነት የዜጎችን ደኅንነት መጠበቅና ማስጠበቅ ነበር። ያንን የማያስፈጽም መንግሥት ፋይዳ የለውም! መንግሥት ተቀዳሚ ተግባሩን ለማስፈጸም በየክፍለ ሀገሩ ተልዕኮውን የሚያስፈጽሙ ታማኞችን ይሾማል። ልማቱም ብልጽግናውም ዚጎቹ በሰላ ወጥተው የመግባታቸው መብት ሲረጋገጥ ነው ትርጉም የሚኖረው። ዜጎቹን እኩል የማይንከባከብ መንግሥት ከፋፋይ ገዥ እንጂ ለአቅመ መንግሥት የበቃ አይደለም። አሁን ያለን መንግሥት “አፈናውንና፣ ግድያውን ታገሱኝ፣ ነገ ብሩህ ተስፋ መጣል” እያለ ያጃጅለናል ደረቅ የቃላት ፍትፍት ያጎርሰናል። ላም አለኝ በሰማይ ወቱቷን የማላይ! ይኽቺ “ዶር ማታ ዶሮ ማታ” የምትሏት ቀልድ ምንም እስኪመሽ አላደረሰችንም። የቻይናው ባምቡ (ቀርከሀ መሆኑ ነው መሰልኝ) የዛሬ 25 ዓመት እስኪ ደርስ የስንቱ ምስኪን አንገቱ መቀላት አለበት?

የመደመር ፍልስፍና ሲገመገም

የዛሬ አራት ዐመት ጨፍጫፊው ወያኔ በህዝብ ቁጣ ስንገላገለው እፍወይ ልንል አሰፍስፈን ነበር። ዶክተር ዐብይ አህመድ አሊ “በቲም ለማ” ታጅበው ወደ ሥልጣን ሲመጡ ብዙ የተስፋ ቃል ሰንቀውልን በደስታ አስፈንጥዘውን ነበር። የሞት ፍርድ የተፈረደባቸውንና ዕድሜ ልክ የታሠሩትን ጨምሮ ብዙ እሥረኞችን ፈተውልናል። አመሰገናቸው! ወያኔ ለሁለት የከፈለችውን የኦሮቶዶክስ ቤተክርስቲያንን አስታረቁ። ስደተኛውንም ፓትርያርክ በአውሮፕላናቸው ይዘዋቸው ተመለሱ። የተከፋፈለውንም የእስልምና ዕምነትን ተከታይ አስታርቀው አስማሟቸው። እነዚህንና የመሳሰሉትን ደግ ሥራዎች ስለፈጸሙ አለማምስገን ንፉግነት ነው። ለአሥርት ዓመታት በባድሜ ምክንያት ለጦርነት ተፋጥተው የኖሩትን፣ ሌላ አገር በሆነችው ኤርትራና ኢትዮጵያን አስታርቀው ሰላም አውርደዋል። ለዚህ ስኬታቸውም የመጀመሪያው የኖቤል ሽልማት ተቀባይ ኢትዮጵያዊ በመሆናቸው አኩረተውናል። 

ዳሩ ምን ያደርጋል፣ የተከተሉት መሥመር ጋት አላኬዳቸውም። አሮጌውን ስልቻ ይዘው ነበር ወደ አዲሱ የወይን ጠጅ የተጠጉት። የ”መደመር” ፍልስፍናቸው ወደፊት የሚያራምድ ሳይሆን “ባለህበት ርገጥ” ሁኗል። አንዳንዴም ፊትህን “ሳታዞር ወደ ኋላ ሂድ” ዓይነት ትዕዛዝ ሁኖባቸዋል። “መደመር” ጅብ አላምዶ የቤት እንስሳ አያደርግም። እንዲያውም መደመር ለወያኔ በሰላም ወደ መቀሌ የመመልስና፣ የመደራጀት ዕድል ፈጥሮ፣ ደንበር ይጠብቅ የነበረውን የኢትዮጵያን መከላከያ ቅርጥፍ አንድርጎ እንዲበላ ረድቶታል። መደመር ጦርነት አላስቀረም። ጦርነት አስክፍቶ ህዝብ አልቋል፣ ንብረት ወድሟል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ አሊ ያልተረዱት ነገር ቢኖር፣ ቃል የገቡልንን ራዕይ ተግባራዊ ለመድረግ፣ የወያኔን በዘር ከፋፍለህ ግዛ ሕገ-አራዊት ቀዳደው ሳይጥሉት፣ በመደመር እሳቤ በብታቸው እንዳቀፉ፣ ቋንቋን መሠረት ባደረገ የዘር የክልልን ሊያስተዳድሩን መሞከራቸው ነው! እባብ ለመደ ተብሎ በኪ ይያዛል እንዴ? መደመር አልሠራም። ጥጃና ጅብ አይደመርም!

አንድ አባት “ቀኝህን ሲመቱህ፣ ግራህን አዙርለት” በሚል አርዕስት ሰበኩ። ከትምህርቱ በኋላ፣ አንድ ጋጠ ወጥ ጠጋ ብሎ በጥፊ አጮላቸው። በደመ ነፍስ የተመታውን ፊታቸው በእጃቸው እያሻሹ ደንግጠው ሳያስቡት ሌላውን ደገማቸው። ብድግ አድርገው ከመሬት አጣብቀው እስኪበቃው ወቁት። ደሙን እየዘራ፣ “አባ ግብዝ ነዎት። ያስተማሩትን ተግባር ላይ አላዋሉም” አላቸው። እሳቸውም፣ “ልጄ፣ ሁለቴ መተኸኝ የለ?” አሉት። “አዎን” አላቸው። ሦስተኛ ጉንጭ እኮ የለኝም አሉት። ወዳጄ ልቤ፣ በ“ጉንጭህን” አዙርለት” አገር አትተዳደርም። ባለጌ ከድክመት ይቆጠርብሀል። መደመር የነበረውን ክፉ አስተዳደርን ማስቀጠል ከሆነ ጉልቻው ተቀያየረ እንጂ ለውጡን አላጣፈጠም። እንዲያውም የህዝቡ ሕልውና ወደባሰው አዘቅት ወረደ። ሰው የራሱን ፊት ያለመስታወት ማየት አይችልም። መስታወት ደሞ፣ ነጻ ጋዜጠኞችና ተቺዎች ናቸው። ዛሬ እረኛ የለም! ድክመታቸው ሊነገራቸው ይገባል።

የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፓርላማ ጥያቄና መልስ

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሻሻ ይወለዱ እንጂ አራዳ ናቸው። ክ15 ዓመታቸው ጀምሮ፣ ወያኔ ስላሳደጋቸው ዘዴዋን በልተዋታል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፓራላማ ጥያቄና መልስ በጥሞና እየጎመዘዛም ቢሆን ማዳመጥ ጠቅማል። ፈገግ ካደረጉኝ ንግግራቸው አንዱ፣ ወደሥልጣን ሲመጡ በፍቅር ካከነፈንላቸው ከኢትዮጵያ ፍቅር ባሻገር አንዱ፣ “ከእንድግዲህ ሳናጣራ ማንንም አናስርም” ማለታቸው ነበረች። አሁን ግን ሽውድውድ ሲያደርጉን፡ ያለህግ ስለታፈኑት ሲጠየቁ፣ “እያጣራን እንፈታቸዋለን” ብለውን እርፍ! እ? ሌላው፣ አባባላቸው እስካሁን ኦሮሞ በኢትዮጵያ ውስጥ እንደሁለተኛ ዜጋ እራሱን ስለሚቆጥር፣ አሁን፣ አሁን ቀና ቀና ማለት ሲጀምር “አካም አካምን” አብዝቷል አሉን። ኧር ጉድ! እንዴ! ታሪክ አያውቁም ወይስ ሊሸውዱን እየሞከሩ ነው? ዕውን “አማራ” የግራኝ አህመድን ወረራ ተከትሎ፣ የኦሮሞ ወራሪ ጎንደርን ከያዛት በኋላ ሥልጣን ላይ ወጥቶ ኢትዮጵያን ብቻውን አስተዳድሯት ይታወቃል? የመንግሥቱ አንጋሽ አውራጅ ማን ሆነና! ነገሥታቱስ ቢሆኑ ማንኛቸው ነበሩ ንጹሀን አማሮች? የድሮውን አጼ ባካፋን ተዋቸው፣ የጉዲሳው የልጅ ልጅ ልጅ ኃይለሥላሴም ቢሆኑ፣12.5% ብቻ የአማራ ደም ቢገኝባቸው ነው። እናታቸውም፣ ወይዘሮ የሺመቤት አሊም ቢሆኑ፣ በእናታቸው በኩል ምናልባት ክንጉሥ ሳህለ ስላሴ የወረደች ከውሀ የቀጠነች ደም ብትኖርባቸው እንጂ፣ የወረኢሉው ኦሮሞ፣ የሼህ አሊ ልጅ ነበሩ። ከየት አመጣህ አትብሉኝ። የባልቤቴ አያትና ወይዘሮ የሺመቤት የእህትማማች ልጆች ነበሩ። የቤተሰቤን ታሪኬን ነው የማወራችሁ፣ ብትፈልጉ! እሱም ይቅር። ለመሆኑ፣ የትኛው አማራ ነው ከ50 ዓመታት ወዲህ ኢትዮጵያን አስተዳድሯት የሚያውቅ? የኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያም መንግሥት? አታስቁኝ? የአቶ የመለስ ዜናዊስ መንግሥት አማራ መሆኑ ነው? ኃይለማርያምን እንዝለል። ሚስቱ ያስኮረፈችው የኦሮሞ ወንድ ሁሉ፣ እንደ ሁለተኛ ዜጋ እራሱን ቆጥሮ ምስኪን አማራ መጨፈጨፍ መተከዣው ከሆነ ነገር ተበላሽቷል። መደመር ስህተቶችን አባባሳቸው እንጂ አላረማቸውም። 

ኢትዮጵያ ውስጥ ኦሮሞ ሁለተኛ ዜጋ ሁኖም አያውቅ? ይህቺ ናት ጨዋታ! ኧረ ተው ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር! ለመሆኑ፣ ጽንፈኛ የኦሮሞ ሊህቃን የሚኮንኗቸው የዳግማዊ ምኒልክ በነማን ዕርዳታ ነበር ለንግሥና የበቁት? የወሎዋ ኦሮሞ ንግስት ወርቃይትም አልነበርች እንዴ ከአጼ ቴዎድሮ ቤተመንግሥት ጠፍተው ሲኮበልሉ፣ አቅፋ ደግፋ ወደ ሸዋ ያሻገረቻቸው? እንዲያው ምኒሊክ አባታቸው ኃይለመለኮት ይሁኑ እንጂ፣ እናታቸውስ ማን ነበሩ? እሱም ይቅር፣ የጦር አበጋዞቻቸው እነማን ሆኑና ነው ኦሮሞ ሁለተኛ ዜጋ የሆነው? ጠቅላላ ኦሮሞዎች አልነበሩም እንዴ የምኒሊክ ቤተመንግሥት አራጊ ፈጣሪዎች? እንዲያው የአድዋን ጦርነትና ድል ልተውና እነማን ነበሩ፣ እምቦቦ ላይ በተደረገው ጦርነት ለምኒልክ ተዋግተው ጎጃምን የመቱላቸው? መቶ በመቶ በራስ ጎበና ዳጬ የሚመራ የኦሮም ፈረሰኞች አልነበር እንዴ ምድሪቱን ቀውጢ ያደረጉት? ንጉሥ ተክለሀይማኖትን አሸንፈው ማርከው ለአጼ ምኒልክ አላስረከቡም[2]? ለመሆኑ ጎጃምን አስገብረው፣ ቤጌምድርን አስገብረው እስክ ትግራይ ድርስ ዘልቀው ሰጥ ለጥ አድርገው ያስገዙት የኦሮሞ ጦረኞች አልነበሩም? ኦቦ ሌንጮ ለታ እንኳን ዛሬ ላይ ሰከን ብለው ከሚኒሊክ ሚኒስትሮች አራት ኦሮሞ፣ ሁለት ከጉራጌ፣ ሶስት ከደቡብ፣ ሁለት ከአማራ መሆናቸውን ነግረውናል[3] ምኒልክ የተረፋቸው ንሥ መባሉ ብቻ ነበር ልቀጥል? ለመሆኑ ተወዳጇ፣ የምኒልክ ባለቤት፣ እቴጌ ጣይቱስ ቢሆኑ፣ ጎንደር ይወለዱ እንጂ የየጁ ኦሮሞስ ባላባት ትውልድ አልነበሩም?  እንዲ ወይ እንደ 15ው ክፍለ ዘመን ተመልሰን በገዳ ሥራዓት እናስተዳራችሁ ካላሉን በስተቀር፣ ሁለተኛ ዜጋም ሁነውም አያውቁም። ሁሌም አንደኛ ናቸው ።

እንዲያው ደፈር ልበለና፣ አማራ የተባለ ብሔር ምናልባት የአማርኛ ቋንቋ የኢትዮጵያ የሥራ ቋንቋ ከመሆኑ በስተቀር ለጎጃሜው፣ ለጎንደሬው፣ ለወሎዬው እንዲሁም ለሸዌው፣ ከድህነት ወጭ አንዳችም ነገር ጠብ ያለለት ነገር የለም። ቁንቋው ደሞ አገር አስተዳደሩ ላይ ከግዕዝ ቀጥሎ የመንግሥት ቋንቋ በመሆኑ፣ ከግዕዝ በወረሰው የግዕዝ ሥነጽሑፍ ስለዳበረ እንጂ በሌላ ጉዳይ አልነበረም። ወደሥልጣን የመጣው ሁሉ አማርኛ የሚቀለው ቋንቋ በመሆኑ፣ እስከወያኔ ዘመን ድረስ ዘለቀ። እንዳዛሬ የላቲን ፊደሎች ሾርባ ቀርጾ መጻፍ ሳይችል፣ አማርኛ እየተጠቀመ ሲገዛን የኖረው የኦሮሞ ሊህቅ ነው። በቀደማዊ ኃይለሥላሴም ዘመን ቁልፍ ቁልፍ ቦታዎችን የያዙ ኦሮሞዎች ነበሩ። የክብር ዘበኛ ጄኔራሎቹ በአባዛኛው ኦሮሞዎች ነበሩ። አየር ኃይሉን ተቆጣጥረውት የነበሩት፣ የወለጋ ኦሮሞዎች ነበሩ።

እንዲያ የሚገርመኝ፣ የኦሮሞ ጽንፈኛ አማራው ጨቆነኝ እያለ ያማያላዝነው ከምን ተነስቶ እንደሆነ አይገባኝም። ኦሮሞ መሀል ተወልጄ በማደጌ፣ አብሮ አደጎቼና እኔ መሀል የተለየ ነገር አልነበርም። ሁላችንም ከድሀ ገበሬ የወጣን ልጆች ነበርን። የለበሳትን ልብስ እንኳን ሳይቀይር አፈር ገፍቶ የሚኖረው አማራው ነው። ጃንሆይም የጎጃም አማጺ አፍነውት፣ ኢትዮጵያን አልከዳትም። የወሎም ህዝብ ቦሩ ሜዳ ላይ ተዋግቶ ተሸንፎ ምንም ያለው የለም። ረሀቡን እየተመላለሰበት የሚያጠቃው ያንን ሕዝብ ነው። ወያኔም “ደመኛ ጠላቴ ብላ” የተነሳችው አማራው ላይ ነው። ኦሮሞ በኢትዮጵያው ውስጥ በመሆኑ ምን የቀረብት ነገር አለ? በግድ አይደል እንዴ ጃንሆይ ልጁን አስገድደው አስተምረውለት ዛሬ በሊቀ ሊቃውንት መንበሽበሽ የቻለው? የታወቀ ሀቅ እኮ ነው።

ሌላው ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ካሉት ውስጥ የገረመኝ፣ አዲስ አበባ ውስጥ ኦሮሞ ጠሊታ የሆን ህዝብ አለ አሉን። አይባልም፣ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴር! አማካሪ አድርገው ያስቅመጧቸው ምን እየሠሩ ነው ደሞዝ የሚከፈላቸው? ወይስ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምክር አይሰሙም? የአዲስ አበባ ብሔር የላትም። ህዝቡ አንድ ወጥ አይደለም። አዲስ አበባ ከማንኛውም የኢትዮጵያ ግዛቶች ተሰብስበው የሚኖርባት ከተማቸው ነች። አንድ ብሔር ረግጬ ልግዛችሁ የሚል ከመጣ ግን “ወጊድልኝ” ሊል ይችላል እንጂ፣ ለይቶ የሚጠላው ብሔር የለም። እርግጥ ዘቅዝቆ የሚሰቅልና፣ አጋድሞ እንደበግ የሚያርድ ይወደዳል ብዬ አልመጻደቅም። ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንድምሳሌም ሲያቀርቡ፣ “ለምን የኦሮሚኛ ብሔራዊ መዝሙር በትምህርት ቤት ተዘመረ” ብሎ የሚንጨርጨር እንዳለ ነገሩን። ሁለት ነገር ልበል። አንዱ ለመሆኑ፣ የአማራ ህዝብ ብሔራው መዝምር ነው ወይስ የጉራጌ ህዝብ ብሔራዊ መዘሙር ነው አዲስ አበባ ላይ በየትምህርት ቤቶች ሲዘመር የሰሙት? ሌላ ጥያቄ! በዚህ መዝሙር ውስጥ “የመቶ ዓመት ግፍን በደም አጠብንልሽ” የሚል ህዝብን ከሕዝብ የሚያፋጅ ስንኝ አንዳለበት እያወቁ! አዲስ አበባን ካልቀማሁ እያለ የሚውተረተረው የኦሮሞው ፓርቲያቸው ነገር ሲፈልግ ነው እንጂ፣ አሁን የኦሮሞን ብሔራዊ መዝሙር ትምህርት ቤቶች ተዘመረ ብለው ገና ለገና “ሳይጠሉን አይቀሩም” ብሎ ያዙኝ ልቀቁኝ ማለት አስፈላጊ ነበር? ወይ ነገር መፈለግ፣ ወይ ዱቢ ወይ ዱቢ! ይኸ ሰሞኑን አንድ ወጣት ጓደኛዬ ላከልኝ ፎቶ ነው የኦሮሞ ሊሒቃንን ነገር ፍለጋ አስታወሰኝ። 

ዕውነትም ነገር ፍለጋ ነው እንጂ፣ አዲስ አበባ ትምህርት ቤት ውስጥ የኦሮሞ ብሔራዊ መዝሙርን በጉልብት ማስዘመርን ምን አመጣው? ለዚያውም የኦሮሞን ህዝብ ባልነበረ ትርክት ቁጭት እንዲነሳሳ፣”የመቶ ዓመት ግፍን፣ በደም አጥበንልሽ” ይሉናል። የአኖሌው ሀውልት ዓይነት ልቦለድ መሆኑ ነው። ይኸው ግምቢ ውስጥ የኦሮሚያን መሬት በአማራ ደም አጥበውላታል። ኦሮሚያ አለፈላት? ያን መዝሙር ነው እንግዲህ የአዲስ አባባ ሕዝብ እንዲጋትላቸው የሚያስገድዱት

ኧረ “ባህሩን የሚያሻግረን ሙሴ መጣልን” ያልናቸው ጠቅላይ ሚንስትር፣ የአዲስ አበባ ህዝብ እንዲሸማቀቅ ምን ያላሉት አለ? “የአዲስ አባባ ህዝብ ቆሻሻውን እየደፋበት” ብለውናል። ወገናዊ ቁጭት እንዲህ ነው እንጂ! ቆሻሻ በተገቢዉ መልክ ማስወገድ እኮ እሳቸው የሚመሩት የመንግሥት ሥራ ነው። መንግሥት ካልቻለ፣ ግለሰቦች እንዲሰማሩብት ሁኔታዎችን ማመቻችት የማዘጋጃ ቤቱ ግዴታ ነው። መንግሥት ደሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመሩት የማዘጋጃ ቤት ተቋም አለው። ወደ አዲስ አበባ ገብሬው ቀረብ እያለ የሰፈረው፣ ምርቱን እያመረተ ለመሸጥ መሆኑን ረስተውታል መሰለኝ። አዲስ አበባ፣ ለኦሮሞ ከእግዚአብሔር የተሰጠው መሬት አልነበረም። የንጉሥ ዳዊት ከተማ ነበረች።

ወይ ፊንፊኔ!

ብልጽግና ውስጥ የተሰገሰጉት፣ እንደነ ኦቦ ሺመልስ አብዲሳ፣ ታየ ደንደአ ... ያሉት ጽንፈኛ የኦሮሞ ሊሒቃን አዲስ አበባን “ፊንፊኔ” ካላላችኋት እያሉ ልባቸው ውልቅ ብሎ የኛንም ልብ ሊያወልቁት ይሞክራሉ። በነገራንችን ላይ፣ የልቡን የሚናገረው ሽመልስ አብዲሳ፣ ህወሀት ለትግሬ ኢህአዴግን እንደፈጠረው ኦህዴድም ለኦሮሞዎች ብልጽግናን ፈጥረናል[4] ብሎ ዕቅጯን ነግሮናል። ዕውነቱን ስለተናገረ፣ ጫፉንም ንክች ያደረገ የለም። ድንገት ሲያልፉ! “አዲስ አበባ” ስትል ከሰሙህ “ናፍጣኛ” እየመሰልካቸው የጎሪጥ ያዩሀል።  ነፍጡ ግን ያለው በነሱ እጅ ነው። አሁን ጋሞዎች ምን አድርገዋቸው ነው በቡራዩ የጨፈጨፏቸው? የአንደኛ ዜግነትን ቦታ ይዘውባቸው መሆኑ ነው? ምስኪኖች!

ድንቁርና ወጥ ያስረግጣል። “ፊንፊኔ” ቃሉ እራሱ አማርኛ መሆኑን ማን በነገራቸው! የኩሸት አባት እንደ ዓይናቸው የሚንከባከቡት ሊቃቸው ኤዝቂኤል ገቢሳ፣ “የመጀመሪያው ሰው ኦሮሞ ነው[5]” ዋቃም በጎን አይቶት ኦሮማ አለው ሲል ተሰምቷል። የመጀመሪያው የሰው ቋንቋም ኦሮሚኛ ነው ብሎናል። ግን እኮ፣ በኦሮሚኛ የተቀረጸ አንድም ሀውልት ከጥንት አልደረሰንም። እሺ ኦሮሞ የመጀመሪያ ሰው ነው እንበል። ጥሩ! አዳም ኦሮሞ ይን። ከሆነ ታዲያ አማራውም ኦሮሞ ነዋ። ስለዚህ ወንድም ወንድሙን መግደል ምን አመጣው? የቃየል ዝርያ መሆናቸው ይሆን? አሁን አሁን የምናያቸው የጽንፈኞች አጨካከናቸውም ያሰኛል። ለማንኛውም ፊንፊኔ አማርኛ ቃል እንጂ ኦሮሚኛ አይደለም። ፊን ፊን እያለች የምትፈልቀዋን ፍልውሀን የምትገልጽ ቃል ነበረች፣ ለአካባቢው ስም ሁና ስትወጣለት። እስቲ አዋቂ ነኝ የሚል ከቆቻቸው አንዱ ይምጣና “ፊንፊኔ” የሚለው ቃል በምን መልኩ ኦሮሚኛ/ኦሮሚፋ እንደሆነ ይንገረን። የቃሉን ሥነ-መሠረት ዕውቀት (Epistemology) ያስጨብጠን። የትም የለም!

አዲስ አበባን “ፊንፊኔ” ብለን ተቀብለንላቸው እንጥራትና ቀናቸውን እናብራላቸው ማለት እየዳዳኝ ነበር። ምክያቱም ሁለቱም አጠራር፣ ማለት፣ አዲስ አበባም፣ ፊንፊኔም፣ ከሚያወግዟቸው ከዳግማዊ ምኒልክ ባለቤት፣ ከእቴጌ ጣይቱ አንደበት የወጡ ቃላት ነበሩና። ችግሩ፣ የአዲስ አበባ ክፍለ ከተሞች በተለምዶ የራሳቸው አጠራር ነበራቸው። ለምሳሌ፣ አራዳ፣ አዲሱ ገበያ፣ አባ ኮራን ሰፈር፣ ሰንጋ ተራ፣ ውሀ ስንቁ፣ ጌጃ ሰፈር፣ ባልደራስ፣ በቅሎ ቤት፣ አራት ኪሎ፣ ስድስት ኪሎ፣ ውቤ በረሀ፣ ነፋስ ስልክ፣ ጉለሌ፣ ሾሮ ሚዳ፣ አቧሬ፣ መሿልኪያ፣ ቀበና፣ ነፋስ ስልክ፣ ፊንፊኔ/ፍልውሀ፣ ሾላ፣ ልደታ ... እያለ ይቀጥላል። ታዲያ የአንዷን ክፍለ ከተማ መጠሪያ ወስዶ ለኦሮሞዎች እንዲመች በአዲስ አበባ መቀየር ተገቢ ነው? እሱን እንተወው አንድ ነገር እንይ! ካላወቁ፣ መርዶ ድግመን እንንገራቸው፣ ዕርማቸውን ያውጡ!! ፊንፊኔ ቃሉ እራሱ አማርኛ ነው። አለቀ ደቀቀ! የቃሉ ሥነመሠረትም ፊን-ፊን ለምትለው የፍልውሀ አካባቢ የተሰጠ ስም ነው። ዛሬም ፊን ፊን የምትለዋ ፍልወሀ አካባቢ ለስሙ መጠሪያ ማስታውሻ ይሆን ዘንድ ለብዙ ዓመታት የቆመ “ፊንፊኔ አዳራሽ” የተባለው ሆቴል/ሬስቶራንት አለ። ሆቴሉ ሌላ ቦታ ሳይሆን ለምን እዚያ ሆነ ብሎ መጠየቅም የአባት ነው? ያንን ሆቴል ስወደው!

እንዳልኩት፣ አዲስ አበባን ፊንፊኔ ብንለው ባልከፋም ነበር። ሌሎች የአዲስ አበባ ክፍለ ከተሞች ይቀየማሉ እንጂ፣ ፊንፊኔ ብለንላቸው ባሳረፍናቸው ጥሩ ነበር። በዚያ የሚቆሙ ከሆኑ ምናለበት! ዳሩ ግን ነገራቸው ሁሉ ኬኛ ሆነና ተቸገርን ። ስንዝር ብትሰጣቸው ለክንድ ይመጡልሀል። ትዝ ይለኛል፣ በወያኔ ጊዜ አንዱ የኦነግ ታክሲ ነጂ አክቲቪስት ሎንደን ላይ አበሻ ሬስቶራንት ቁጭ ብሎ ሲያወጋ፣ አንዱ ጓደኛው “ለምን በቡድን ተደራጅተን ፊንፊኔ ቦታ ተመርተን ቤት በማኅበር አንሠራም?” ሲለው ምን መለሰለት መሰላችሁ። "ነገ ፊንፊኔ ከአማራውና ከምናምኑ ጸድታ የኦሮሚያ ዋና ከተማ ስትሆን፣ ከዚያ ሁሉ ከተሠራው ቤት መርጠን እንገባበት የለ? ምን አደከመህ!” አለው ደረቱን ገልብጦ! ለማንኛውም፣ መላውን አዲስ አባባ ፊንፊኔ ካልነውማ፣ ጉለሌስ ምን ጎደለው?

ፊንፊኔ አማርኛ ለመሆኑ፣ አንድ ጋጠ ወጥ እምቡር እምቡር እያለ ሲያስቸግር፣ አሁንም “ፊን ፊን! አትበል” እየተባለ አደብ ያስገዙታል። ፊን ፊን እያላችሁ የምታስቸገሩን ጽንፈኛ የኦሮሞ ልሒቃን፣ ፊንፊኔ ተብሎላችሁ ምንም ለውጥ ላታመጡ ተውት። ፊንፊኔ ኦሮሚኛ ስላልሆነች አታፈናፍናችሁምና ለአዲስ አበባ ባይሆን ሌላ ስም ፍጠሩለት። ታሪክ የመፍጠር ችግር መቼም የላባችሁም። በዛ! አበዛችሁት!

ማጠቃለያ!

አዲስ አበባ፣ አዲስ አበባ ከመባሏ በፊት፣ ሌሎች ስሞች ነበሯት። አንዱ ሸገር ነበር። እሱም ኦርሚኛ ይሁን አይሆን አላውቅም። “ሻጋር ጉሉፋኒ” (SHAGGAR GALUUFANII) የተባለ በቦሀራ ብርሀኑ ( Bohaara Birahaanu)[6] የሚዘፈን ዘፈን አለ አይደል? ወደሸገር ግልቢያ መሰለኝ ትርጉሙ! እና ሌሎችም አሉ። ሸገር ሬዲዮስ አለ አይደል? በጥናት የተረጋገጠ፣ የጥንት ስሟም አለ። በረራ! እሱም ኦሮሚኛ አይመስለኝም። ነው እንዴ? እንጃ! አዲሳ አበባ የኦሮሞ ስም ካልነበራት፣ እንግዲህ አዲስ አበባ ኦሮሚያ ሁናም አታውቅም ማለት ነው። ምን ይሻላል?

እንግዲህ፣ ፊንፊኔ፣ ካላፈናፈነቻቸው፣ አዲስ ስም ያውጡና እንደልማዳቸው የጥንት ስሟ ነው ይበሉን። ለምን “ዳራራ ሀራ” (Haaraa) አይሏትም? “እቴጌ ጣይቱ እንደ የምኒልኳ ፈረስ ከዚያ ሰርቀው ነው” ማለት ይችላሉ። አይችሉም? ማን አባቱ ከልክሏቸው! “አባቦ ሀራ” በሉት እንዳልላችሁ፣ አባቦ የተንሻፈፈ የአማርኛው አበባ ስም ስለሆነ ነው።

“ፊንፊኔ የቀድ ስሟ ነበር እያሉ የኦሮሞ ልሒቃን ዊኪፒዲያ ላይ እየቀየሩ ይገኛሉ። ዳሩ ግን ስሟ ለመሆኗ አንዲት ምንጭ እንኳን አይጠቅሱም። ከየት አምጥተው! የለማ! ሲፈልጉ በኦሮሞ አፈታሪክ አለ ይሉሀል። ኤዲያ! ልክ የመጀመሪያው ሰው ኦሮሞ ነበር እንዳሉን መሆኑ ነው። በመጀመሪያ ደረጃ ያ ቦታ እልም ያለ ጫካና አውሬ የሚታደንበት አካባቢ ነበር። ዛሬም አዲስ አበባን ከቦ የሚኖረው ጅብ፣ ከዚያ የተረፈ የዱር አራዊት ነው። አዲስ አበባን ጣይቱ ናቸው የሰየሟት። ቦታውን ያዩዋትም፣ አጼ ምኒልክ ሐረር ሂደው፣ እቲጌይቱ ፊን ፊን ከምትለው ጸብል ሊታጠቡ ከንጦጦ ወርደው ነበር። ያቺን ፊን ፊን የምትል ፍልውሀ ጥለው መሄድ አልፈጉም። ንጉሡን አሳምነው ከተማ ቆረቆሩ። በዚህ ምክንያት የኢትዮጵያ ዋና ከተማ የመሆን ዕድል ገጥማት፣ የአፍሪካም ዋና መዲና ሆነች። ያ የሁሉ ኩራታችንና የሁላችን ውርስ ነው። አንዱ ቀማኛ ብሔር ዓይኑን የሚያሳርፍባት መሆን የለባትም። የአዲስ አበባ ሕዝብ እንዴት ጊዜው ቢከፋበት ነው፣ በወያኔ ጊዜ እንኳን የነበረውን የክልልነት ደረጃ አጥቶ በብልጽግና ጊዜ የኦሮሞ እንዲሆን ዲሞግራፊውን ለመቀየር እነ ሺመልስ አብዲሳ የሚሯሯጡት? ሀይ ሊባሉ ይገባል። ኢትዮጵያን ወክሎ የፌዴራል መንግሥቱን ሥልጣን የጨበጠው ክፍል፣ ሕዝቡን ማሸማቀቅ ትቶ መብቱን ማስመልስና ማስጠበቅ የግድ ይሏል። 

ኬኛዎች ሰላም ስጡን! ነገር አትፈልጉ! አብረን በሰላም እንደዱሯችን ተከባብረንና ተፋቅረን እንኑር! የአንድ እናት ልጆች ነን!

አበቃሁ!

No comments:

Post a Comment