Tuesday, 11 July 2023

“ኩሽ!” እያላችሁ ምን ያንኮሻኩሻችኋል?

“ኩሽ! እያላችሁ ምን ያንኮሻኩሻችኋል?

ወንድሙ መኰንን
England: 11 July 2023

ሰው ሲበድላችሁ፣ እስቲ አትናደዱ፤
ጠላትን አትጥሉ፣ ክፉን ሰው ውደዱ።
የክፉ ሰው ክፋት፣ ጠቃሚ ነው ትርፉ፤
ያነቃቃችኋል፣ እንዳታንቀላፉ።
የልቦናው ስሜት፣ እየተራቀቀ፣
ሁልጉዜ ወደ ላይ፣ በጣም እየላቀ፤
በሥራ በጥበብ፣ ግሎ ለመነሳት
ቆስቋሽ የፈልጋል፣ የሰው ልጅ እንደ እሳት
                                                                        ከበደ ሚካኤል፣ የዕውቅት ብልጭታ ገጽ 163

1)   1)   መግቢያ

ዳማ የተባለ ዳንግላ ፈረስ፣ ዋርዲት የተባለች ሽቅርቅር በቅሎ ጋር ሜዳ ውስጥ ሣር ሲግጡ ይተዋወቃሉ። መሽቶ ሊለያዩ ሲሉ፣ ዳማ በጣም ስለወደዳት ዋርዲትን “አባትሽ ማናቸው” ብሎ፣ ጠየቃት። ዋርዲት እየተሽኮረመመች፣ “አጎቴ ጥሪኝ የሚባል ፈረስ ነው” ብላ መለሰችለት ይባላል። ፊየል ወዲህ፣ ቅዝምዝም ወዲያ። ምን ለመደበቅ ነው?

ድንቁርና፣ ያጀግናል። ደፋር ያደርጋል። አንድ ሰው ባነበበ፣ በተመራመረ፣ ባወቀ ቁጥር ነው፣ አለማወቁን እየተረዳ ሲመጣ ነው ቁጥብ የሚሆነው። ያልበሰለው ጥራዝ ነጠቅማ፣ ጫፍ ይዞ እንደባዶ ቆርቆሮ ሲንጣጣ ነው የሚውለው። ከሠርቪስ ኮሊጅ ይሁን፣ ወይም ከነጻ ገቢያ ድግሪ እየገዙ፣ ያልበሰሉ የእፍ እፍ ባለ ዶክትሬት ዲግሪዎች፣ ታሪክቱን በጭንቅላቷ እያቆሙ ሲደፏት እያየን፣ አንዳንዴም በዝምታ፣ ካልሆነም በፈገግታ እያሳለፍናቸው ነው። በዝምታችን ምክንያት ምድሪቱ አልበቃ እያለቻቸው ነው። እንደልባቸው ይቀባጥራሉ። ፕሮፌሰሩ ዓይኑን በጨው አጥቦ፣ አንዳችም ሳያመነታ፣ “የመጀመሪያው ሰው ኦሮሞ ይባላል፣ ከውሀ ነበር የወጣው፣ ጾታ አልነበረውም፣ ዋቃ እንዲህ በጎን አይቶት ለሁለት ሰነተጠቀው” [i] እያለ ሲያወጋን ስቀን ወደሌላ መመልከት ግድ ሆነብን። ምንጩ ደሞ የኦሮሞ አፈ-ታሪክ ነው። የትም ተጽፎ የማይገኝ! ይኸው ፕሮፌሰር፣ ለብዙ ሺ ዓመታት በግዕዝ ተጽፎ የተቀመጠውን ታሪክ፣ የደብተራዎች ፈጠራ ነው እያለ ሲያጣጥል ሰምተነዋል። አባቶቻችን ፊደል ቀርጸው፣ ቀለም በጥብጠው፣ ብራና ዳምጠው፣ ጽፈው ያስረከቡን ታሪክ፣ ተረት ሁኖ ከተገኘ፣ በነዚህ የዘረኞች ሊሂቃን ከተጣጣለ፣ የማይመስል አፈ-ታሪክ ዕውነትነት ሲኖረው ይታያችሁ! ወይ አለማፈር!

2)  2)  ሌሎች ምን ይላሉ፣ ስለኢትዮጵያ?

የኢትዮጵያን ታሪክ ብዙ የአውሮፓና የአሜሪካ ተመራማሪዎች ጽፈውታል። ከነዚህም ፐከንሀም (Thomas Francis Dermot Pakenham)፣ ኡላንዶርፍ (Edward Ullendorff) ፣ ክራሚ (Donald Crummey)ሳልቫዶሬ (Matteo Salvadore)፣ ፓንክረስት (Richard Keir Pethick Pankhurst)፣ ፓየዝ (Pedro Páez)፣ ማርኩስ (Harold Marcus) እና ብዙ ሌሎችም የጻፉትን የኛ ዘመናዮች ያጣጥሏቸዋል። “እኛን ኮሎኒ አድርገው ለመግዛት ስለሚፈልጉ፣ ኦሮሞን ዝቅ አድርገውና አንቋሸው ጽፈዋል” ይሉናል። እነ ፓየስ እኮ ያዩትን ነው የጻፉት። ፓይዝ የተባለው ፖርቱጋላዊ፣ የኢትዮጵያ ታርክ (História da Ethiópia) በተባለው በ1622 ዓ.ም በጻፈው መጽሐፉ፣ የኦሮሞ ተዋጊዎችን ጭካኔ በዓይኑ ያየውን መዝግቧል። እና እንዲደብቁላቸው ነው የሚመኙት? ኢትዮጵያን በጣም የሚጠላው ባውም (James Edwin Baum) እንኳን፡ “አረመኔዋ ኢትዮጵያ (Savage Abyssinia) ብሎ በጻፈው ዘረኛ መጽሐፉ፣ የኢትዮጵያን ህዝብ ኦሮሞውንም፣ አማራውንም ቢስድብም፣ ታሪኳን ግን እየመረረውንም ቢሆን እንዳለች እንዲህ ሲል ለማስቀመጥ ተገዷል።

Yemen, the Red Sea province of Arabia, was conquered by the Abyssinians who ruled that turbulent country until 570 A.D. About the year of Mohamet’s birth, they were defeated before Mecca and driven, bag and baggage for ever from the continent of Asia”[ii]

ወደ አማርኛ በቀላሉ ስናቀርበው፤ “አቢሲኒያ፣ የአረቢያ ጠቅላይ ግዛት የነበረችውን የተበጠበጠች፣ የመንን ወራ ከያዘች በኋላ፣ እስክ 570 ዓ.ም ድረስ አስተዳደረቻት። ሞሀመት በተወለደ ዘመን አካባቢ፣ ከመካ በፊት፣ ተሸነፈው፣ ጓዛቸውንና ጉዝጓዛቸው ሰብስበው ተባረሩ” ይለናል። የመን ድረስ ዘልቃ ያስተዳደረች ኃያል አገር መሆኗን መደበቅ አልቻለም።

የኛዎቹ የተማሩ መሀይማን ግን መኖሯንም ክደው ያልሆንቺውን “ኩሽ ነበርች” ይሉናል። ኩሽ እኮ ግብጾች ጥቁሮችን ለመስደብ የተጠቀሙበት ቃል ሆኑን እንኳን አያውቁም። መሀይምነት ጀግና ያደርጋል ያልኳችሁ ለዚህ ነው። ድፍረታቸው የሚገርም ነው። ሊያለያዩን፣ ሊበታትኑን፣ “ኩሽ! ኩሽ! ኩሽ ነን እኛ” ይሉናል። ማነው ኩሽ? “ከአቢሲኒያዎች የተለየን ህዝቦች ነን” እያሉ አንዳንድ በኢትዮጵያ ቆሽታቸው የደበነ ነጮች የጻፉትን አንጠልጥለው፣ ልባቸው ውልቅ እስኪል ድረስ ይንጣጣሉ። በዛ! እነሱስ እሺ ይንኮሻኮሹ፣ ሌሎቹን፣ እንደ ካፋ፣ ወላይታ ጋሞ፣ ሲዳማ፣ የመሳሰሉትን የደቡብ ብሔር ብሔርሰቦችን ምን በወጣቸው? ከጎናቸው ለማሰለፍ? ጅሎች እየመሰሏቸው ብዙ ርቀት ሂደዋል። እነዚህ ሰዎች፣ አንድ ቋሚ የታሪክ አሻራ ጥለው ያለፉት የሚታይ ነገር የላቸውም። የመጀመሪያውም ሀውልት ስለነሱ የተቀረጸው በኢትዮጵያ ጠላት የተጻፈ ልቦለድ ገጸ ባህርይ በአኖሌ ስም ነው። ቢሞቱ ይሻላቸዋል! ሲያሳፍሩ!

በዚያም አልተወሰኑም። ሱማሌውንም፣ አፋሩንም “ኩሽ ናችሁ” ብለው፣ የኢትዮጵያን ፊደላት ሳይሆን፣ ላቲንን፣ እንዲጠቀሙ አስታቅፈዋቸዋል። ወደሰሜኑም ብቅ በለው፣ ቅማንቱን፣ አገውን እና ሸናሻውን፣ ኩሾች ናችሁ እያሉ የአንዳንዱን ግልብ፣ ጭንቅላት አዙረዋል።

የአዋቂዎች ዝምታ፣ መሀይሞች እንደፈነጩበት ሰፊ ቦታ ሰጣቸው። ይፈነጩብናል። የታሪክ ተመራማሪ ኢትዮጵያውያን አፍረው ይሆን ወይም ድፍርት አንሷቸው አይታውቅም ዝምታን መርጠዋል። ንጉሡን ራቁታቸውን መሆናቸውን የሚነግራቸው እብድ ያስፈሊጋል። ግፋ ቢል፣ እብድ ቢባል ነው። ራቁታቸውን ናቸው ብሎ በመሸበት ማደር ይመረጣል! እኔ እሱን መሆን መርጫለሁ።

ከላይ ያለው የደራሲ ከበደ ሚካኤልን ግጥም ያስቀመጥኩላችሁ፣ ዝም ብዬ አይደለም። ይነካኩን ይነካኩንና፣ አንድ ቦታ ላይ ስንደርስ፣ ይበቃናል። እነሱ፣ ለተንኮል ያጣመመቱን ለመቃናት ግድ ይለናል። ለመሆኑ፣ ኩሽ ብለው እንዲህ የሚሟሟቱበት አቶ ኩሽ ሆዬ ማን ነበር? እስቲ በሚቀጥለው እንይ።

3)3)  ትክክለኛው የኩሽ ታሪክ

ነገር ከሥሩ፣ ውሀ ከጥሩ ይባል የለ?  እስቲ ወደ መሠሩቱ እንሂድ። መሠረቱ፣ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። በከፊል፣ እስራኤላውያን የትውልድ አመጣጣቸውን ጥንታዊ ታሪክ ጽፈው አስቅምጠውልና። ሙሉ ግን አይደለም። የራሳችን ሊቃውንት እጀ የገቡ ብዙ በብራና ላይ የተጻፉ መጽሐፍት፣ መጽሐፈ ኼኖክ ሳይቀር እስከዘመናችን ዘልቀዋል። ኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ 10 ከቁጥር 1 ጀምሮ፣ ኖኅ 3 ልጆች እንደ ነበሩት ያወራል። እነሱም፣ ሴም፣ ካምና ያፌት ናቸው። ዣንሸዋ ተቀዳሚ የሚባለው ጥንታዊው መጽሐፈ ብሩክ የነዚህን ትውልዶች ከገጽ 261 እስከ 275 ዝንፍ ሳይል፣ የሴምንም፣ የካምንም፣ የያፌትንም ትውልድ ዘርዘሮ ያስቀምጥልናል። ሰረገላ ታቦር የተባለውም፣ በመሪ ራስ አማን በላይ የተተረጎመውም ከገጽ 290 ጀምሮ እስክ 306፣ ይኸንኑ ይተነትናል። ማንበብ የሚወድ፣ የታሪክም ተመራማሪ ሁኖ ከዩኒቨርሲቲ መመረቅ አያሻውም። ታሪኩን እንደወረደ አንብቦ ይረዳል። ማን የማን ልጅ እንደሆነ በተጻፈው መሠርት ማንበብ ነው። የሚያወሩት ስለካም ልጅ፣ ኩሽ ከሆነ፣ የሴም ልጆች ሴማውያን ከተባሉ፣ የያፊት ልጆች፣ ያፌታውያን ከተባሉ፣ የካም ልጆች ካማዊያን “አፍሪካ” ጋ ሲደርስ የማይባሉበት ምስጢር ከቶም አይገባኝም። አንድ መደበቅ ያለበት ታሪክ ከሌለ እንደ ዋርዲት ምን አጎት ድረስ ያወርዳል?

የኖኅ ልጆችን የትውልድ ሐረግ (Family Tree) ሲመዘዝ እንዴት ማመን ይቻላል? መልሱ ቀላል ነው።  ጥንታዊውያን ማንበብና መጽሐፍ የሚችሉ አባቶቻችን፣ ልጆች ሲወለዱላቸው፣ ቀኑና ዓመተ ዓለሙን/ምህረቱን ወይም በየአገሩ የዘመን አቆጣጠር ባህል መዝግቦ ማስቀመጥ ልማዳቸው ነው። ያልተማሩት ይኸ ዕድል የላቸውም። ለምሳሌ፣ ወላጅ አባቴ፣ አቶ መኰንን አየነው፣ ነፍሳቸውን ፈጣሪ በገነት ያኑርልኝና፣ ሲወርድ ሲዋረድ በመጣው ውርስ ባህላቸው መሠረት፣  የኔን ልደት ከነ ሰዓቷ፣ ቀኗ፣ ወሯንና ዓመተ ምሕረቷን፣ ከደረታቸው በማትለየው ዳዊታቸው የውስጥ ሽፋኗ ላይ ጽፈው ቁጭ አድርጎልውኛል። ያ ብቻም አይደለም። የደብረ ኤሊያስ ካህናት ትውልድ በመሆናቸው ወደ ኋላ በትንሹ እስከ ሰባት ቤት አባቶቻችን እነማን እንደነበሩ፣ ተመዝግቦ ከተቀመጠው ስሞቻችውን በቃሌ ቆጥሬ እንድይዝ አስጠንተውኛል። ቁም-ነገሩ፣ በአፈ ታሪክ ሳይሆን፣ የሥነጽሑፍ ባህል ያዳበረ ሕብረተሰብ ነገሮችን በቅደም ተከተሉ፣ በጽሑፍ መዝግቦ መያዝ፣ የዕድገት ደረጃውን ያመለክታል። እስከነ ተረቱ፣ በአፍ የተነገረ ይረሳል፣ የተጻፈ ይወሳል ይባል የለ? በአፈ ታሪክ የሚወራው፣ ምንም ዓይነት ማረጋገጫ ስለማይገኝለት፣ ተረት ሁኖ ይቀራል። አንዳንዴም የጎደለውን ለማሸብረቅ ያልነበረው ገብቶበት ይቦካዋል።

በሴም በኩል፣ አንዷን ዘለላ መዘን እስክ አብርሃም ያለውን ትውልድ እንይ[iii]። ምክንያት አለን። ኖኅ ሴምን ወለደ፣ ሴም አርፍክስድን ወለደ። አርፍክስድ ሳላን ወለደ። ሳላ ኤቦርን ወልደ። ኤቦር ፋሌቅን ወለደ። ፋሌቅ ራግውን ወለደ። ራግው ሴሮሕን ወለደ። ሴሮሕ ናኮርን ወለደ። ናኮር ታራን ወለደ። ታራ አብርሃምን ወለደ። ይበቃል[1]። ከሴም እስክ አብርሀም 10 ትውልድ መሆኑን ልብ በሉልኝ።

አሁን ደሞ በሌላ በኩል፣ ከሴም ታናሽ ወንድም፣ ከካም እስከ ካህኑ አበመሌክ ያለውን የትውልድ የሐረግ ዘለላ መዘን ከመጽሐፍ ቅዱስና ከተለያዩ ምንጮች እንመልከት።  

ኖኅ ካምን ወልደ። ካም ኩሽን ወለደ። ኩሽ ሳባን ወለደ፣ ሳባ ኑባን ወለደ። ኑባ አጋናን ወለደ። አጋና ኤታን ወለደ። ኤታን ናምሩድን ወለደ። ናምሩድ አዳማን ወለደ። አዳማ ራፌልብን ወለደ። ራፌልብን ቄናን ወለደ። ቄና መልክጸዴቅን ወለደ[iv]ከካም እስከመልከጸዴቅ 11 ትውልድ ነው። ኩሽ የት እንደቀረ አያችሁ? ከከነዓን ምድር እግሩም አልተቃነቀም

ኩሽ ናምሩድን ወለደ የሚል የተሳሳተ  ነገር አንብቤ፡ “ታላቁ ዶቦ ሊጥ ሆነ ብያለሁ።” ኩሽ ለናምሩድ ቅማንቱ[2] ነበር። አምስተኛ ትውልድ መሆኑ ነው። የነገሮች ውል ሲጠፋ እንዲህ መሳሳት ያመጣል። እንዲያው ዝም ነው። ምነው ኢትዮጵያውያንን ሊቃውንትን በጠየቁ!

ችግሩ ከየት እንደመጣ ላስረዳችሁ። ቫን ሰተር (Van Seter)[v] የተባለው ጸሐፊ እንደዘገበው ከሆነ፣ ኦሪት ዘፍጥረት፣ ኦሪት ዘጸአት፣ ኦሪት ዘሌዋውያንና ኦሪት ዘኁልቁ የተጻፉት በ6ኛው እና በ5ኛው መቶ ዓመት ዓለም፣ ዕብራውያን ከግብጽ ባርነት ነጻ ከወጡ በኋላ ነበር። የራሳቸውን ታሪክ በአብዛኛው መዛግብቱ ቢኖራቸውም፣ በስደት ዘመን የካምን መዝገበ ታሪክ አልነበራቸውም። የናምሩድ ትውልድ ስሀተት ከዚህ ነው የተፈጠረው። እንዲህ ነው የሆነው። መጽሐፈ ኼኖክና፣ ሌሎች መጻፍትን፣ ኖኅ የሰጠው ለካም ነበር። ካም ደሞ ለታላቅ ልጁ፣ ለኩሽ ሰጠው። መጻፍቶቹ፣ ካህን ለሚሆኑት ለታላላቆቹ እየተወረሱ እስከ መልከጸዴክ ደረሱ። መልከጸዴቅ ለታላቅ ልጁ፣ ለኢትዮጵ (ሌላ ስሙ ኢትኤል) አወረሰው። ኢትዮጵ መጻሕፍቱን ይዞ፣ ዛሬ አፍሪካ ወደምትባለው መሬት ተሻገረ። እንዲህ እያለ ኢትዮጳውያን ሊቃውንት እጅ ገቡ። እስራኤላውያን፣ በዚያን ጊዜ የካምን ታሪክ የሚክታተሉበት መንገድ አልነበራቸውም። ታላቁን ናምሩድ የካም ዘር ቢሆንም፣ ውሉ ስለጠፋቸው የኩሽ ልጅ ብለውት አረፉ።

እነዚህን የሁለቱን የወንድማማቾችን ሐረጎች ምን አስመዘዘን? መክንያቱም የሴምና የካም 10ኛና 11ኛ ትውልድ በአንድ ጊዜ እንደኖሩና እንደሚገናኙም፣ ዝምድናቸውንም እንደሚያውቁ ለማመልከት ነው። መጽሕፍ ቅዱስ፣ ኦሪት ዘፍጥረት፣ ምዕራፍ 14 ከቁጥር 17 እስክ 21 እንዲህ ይላል።

“ኮሎዶጎምርና ከእርሱ ጋር የነበሩትን ነገሥታት ወግቶ ከተመልሰ በኋላም፣ የሰዶም ንጉሥ የንጉሥ ሸለቆ በሆነ በሊዊ ሸለቆ ሊቀበለው ወጣ። የሳሌም ንጉሥ መልከጽዴቅም እንጀራንና የወይን ጠጅን አወጣ። እርሱም የእግዚአብሔር ካህን ነበረ። ባረከውም፦ አብራም ሰማይንና ምድርን ለሚገዛ ለልዑል እግዚብሔር የተባረከ ነው። ጠላቶችህን በእጅህ ተጣለልህ ልዑል እግዚአብሔርም የተባረከ ነው አለውም። አብርሃምም ከሁሉ አሥራትን ሰጠው።”

አውሮፓውያንና አሜሪካውያን ተመራማሪዎች፣ ግዕዝን ለመማር የሚሟሟቱበት ምክንያት ብዙ የነገሮችን ግንኝነት ውል በፍጹም ሊያገኙት ባለመቻላቸው ነው ወደ ኢትዮጵያ የሚያንጋጥጡት። የአብርሃምንና የመልክጸዴቅን ግንኙነት (relationship) ጨርሶ ያልገባቸው፣ ፈረንጆች እንዲ ሲሉ ይናገራሉ።

Abraham encounters a mysterious figure named Melchizedek. So, who exactly is this mysterious Melchizedek? As Abraham is returning victorious from a risky battle, he passes by the city of Salem, and the king comes out to meet him. We're told that this king is also a priest who serves the same God as Abraham.[vi]

በቀላሉ ወደ አማርኛ ስንመልሰው፡ አብርሃም ምስጢራዊ የሆነ መልከጸዴቅ የተባለ ሰው ያጋጥመዋል። እና፣ ይኸ ምስጢራዊ የሆነ ሰው ማነው? አብርሃም አደገኛ (risky) የሆነ ጦርነት ተዋግቶ ድል ነስቶ በሳሌም ከተማ ውስጥ ሲመለስ ይኸን የሳሌምን ንጉሥ ያገኘዋል። እንደነገሩን ከሆነ፣ ይኸ ንጉሥ፣ አብርሃም የሚያመልከውን እግዚአብሔር የሚያገለግል ካህን ነው። 

እንደዚህ ዓይነት ብዙ ነገሮች ከኢትዮጵያ ምንጮች ካልሆነ በስተቀር ሌላ ቦታ ድርና ማጉን ማገናኘት የማይቻሉ ነገሮች አሉ።[3]

እንግዲህ ዕውነተኛው ኩሽ የኖረው ወደ 5,000 ዓመተ ዓለም አካባቢ ነው። ወዲያው ከታላቁ ውሀ መጥለቅለቅ በኋላ ብዙ ህዝብ አልነበረም። የከነዓን ምድር ሁሉ ለኖኅ ልጆች የምትበቃ ሰፊ ነበርች። ኩሽ ከከነዓንም ምድር ወጥቶ አያውቅም። አፍሪካ የት እንዳለችም አያውቅም። ይኸ ጥቁር ህዝብን በደፈናው ነጮቹ ኩሽ የሚሉት ከግብጽ ተውሰው በዘረኝነት ላይ የተመሠረተ ታሪካዊ ጭብጥ የሌለው መላ ምት ነው። ቀላ ቀላ ባሉት ወራሪ ዘሮች ድቅልቅል ያሉት ግብጾች ወደደቡብ የገፏቸውን፣ ጥቆርቆር ያሉትን ኑቢያዎች የሰደቧቸው መስላኡቸው ኩሽ አሉቸው። የድንቁርና ጥግ ይሉሀል ይኸ ነው።

በ440 ዓመተ ዓለም ገደማ የኖረው ታላቁ የግሪክ የታሪክ ሰው፣ ሔሮዶቱስ (Herodotus) ስለኩሽ ሳይሆን ስለ አእትዮጵያ ("Αἰθιοπία - Aethiopia") ነበር እንዲህ እያለ የተርከው።

“... this country produces great quantities of gold, has an abundance of elephants and all the woodland trees, and ebony; and its men are the tallest, the most handsome, and the longest lived."[vii]

ወደ አማርኛ ስንመልሰው፡ “አገሪቱ ብዙ ወርቅ የምታመርት፣ ብዙ ዝሆኖች የሚገኙባት፣ በጫካ የተከበበች፣ ብዙ ለአናጢ ሥራ የሚመቹ ግንዶች ያሏት፣ ህዝቧ በጣም ረጃጅም የሆኑ፣ በጣም የሚያማምሩ፣ እና በዙ ዓመታት መኖር የሚችሉ ናቸው” ይላል። ሔሮዶቱስ ማለት የዓለም ታሪክ አባት ተብሎ የተሰየመ ነው። የተቃጠለ ፊት የሚለው ትርክት ሰዎች እንደልማዳቸው የግሪክ ቃል ፈልገው አጠጋግተው ካልሆነ እንጂ፣ በሔሮዶቱስ ገለጻ አንድም ቦታ የተቃጠለ ፊት የሚል አናገኝም። ከየት ፈበረኩት? እንዲያው የተቃጠለ ፊት በግሪክኛ Kaméno Prósopo (Καμένο πρόσωπο) ነው። ምኑን ከምን አገናኙት?

ከ9ኛው እስከ 8ኛው ዓመተ ዓለም የኖረው ሆሜርም፣ ኤሊያድ ( Iliad)  በተባለው ድርሰቱ ሁለት ጊዜ፣ በኦዲሰይ (Odyssey) 3 ጊዜ ኢትዮጵያን በስሟ ጠርቶ ያሽሞነሙናታል። ግሪኮች በነበረው ስሟ፣ ኢትዮጵያ ብለው ጠሯት እንጂ፣ አዲስ ስም አላውጡላትም። ኢትዮጵያ ስለምትባለውና ስለህዝቧ ነው የተናገሩት። እነሱ ማን ናቸውና ነው ለኢትዮጵያ ስም የሚያወጡላት? በስሟ ጠርተው ነው ያደነቋት። የዘመኑ ታርክ አጥኚ ነን ባዮች እንዴት “የተቃጠለ ፊት” ሊሉት ቻሉ? እንዴት አጠጋጉት? ምናልባት፣ አዲግራትን “አዳ ጋራ” እንዳሉት አጠጋግተው ይሆን? ግሪኮች የሚያወሩት ስላጋጠመቻቸው “ኢትዮጵያ” ነበር እንጂ ስም አላወጡላትም። እነሱ በግልጽ ሲናገሩ የነበሩት፣ ስለ ኢትዮጵያን ልብ የሚሠርቅ ውበታቸው ነው እንጂ ስለተቃጠለው ፊታቸው አልንበረም። እስቲ ይታያችው፣ የግሪክ አፈታሪክ (mythology) ክዋክብትን በኢትዮጵያ ንግሥት ካሶፒያ (Cassiopeia) እና ንጉሥ ሲፊየስ (Cepheus) እያሉ ሲሰይሙ ስለተቃጠለው ፊት፣ ወይም ስለ ኩሽ እያወሩ ነበር? ስለ ልዕልቲቱ የካሶፒያና የሲፍየስ ልጅ፣ ስለ አንድሮሜዳ ሲያወሩ፣ ስለኩሽ ነበር ያወሩት? ከየት ነው ኩሽ መጥቶ በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ የተደነቀረው? ኩሽ መጥፎ ስም ሁኖ ሳይሆን፣ የታሪክ መሠረት ስለሌለው ነው። ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ ይሉሀል ይኸ ነው። “ኢትዮጵያ” የሚለው መጠሪያ ስም ግን የተረጋገጠ የታሪክ መሠረት አለው። ለመሆኑ ይኽቺን ኩሽ የምትለዋን ቃል ማን ነበር መጀመሪያ አምጥቶ የደነቀራት? ከላይ እንደተገለጸው ግብጾች ነበሩ። ጢሞቲዎስ ኬንዳል (Timothy Kendal) የተባለ ሰው፣ እንዲህ ጉዱን ይነግረናል።

Kush, the Egyptian name for ancient Nubia, was the site of a highly advanced, ancient black African civilization that rivaled ancient Egypt in wealth, power and cultural development. The first capital of Kush lay at Kerma just south of the Third Cataract of the Nile.[viii]

“ኩሽ፡ ግምጾች፣ ለጥንታዊ ኑቢያውያን የሰጡት ስም ነው። አካባቢውም በጣም በሥልጣኔ የመጠቀና ከግብጽ ሥስልጣኔ፣ ሀብትና ኃያለነት ያላነሰ የጥቁር አፍሪካውያን አገር ነበር። የመጀመሪያው ዋና ከተማቸው ኬርማ ይባል ነበር። የሚገኛውም ከሦስተኛው የአባይ ካታራክት (ዓባይን እንደ የዓይን ሞራ የሸፈነ መሬት) ትንሽ ወደ ደቡብ ወረድ ብሎ ነው”። ግብጽን ከኢትዮጵ ዘሮች ከቀሟት በኋላ ማን ያልተፈራረቀባት አለ? ግሪክ፣ ሮማዎች፣ ቱርኮች፣ አረቦች ... ወዘተርፈ።

የአውሮፓ ቅኝ ግዥ ነጮች፣ ያቺን ከግብጽ ተዋሱና ትርጉሙን አጣመው ጥቁሩን ህዝብ በሙሉ ኩሽ አሉት። ኢትዮጵያውያን ለአገራቸው ስም ማውጣት አቅቷቸው ነው፣ ነጮቹ ግሪኮች አዲስ ስም የሚያወጡላቸው? ለነገሩ፣ አልተሳካላቸውም እንጂ፣ አቢሲናያስ ሊሉን ምን ያልፈነቀሉት ድንጋይ ነበር?

4)  ኢትዮጵያ - ምድረ ኢትዮጵ

የካምን ትውልድ ሀረግ ስንመዝ፣ 11ኛው ትውልድ ላይ ነበር የቆምነው። እሱም ካህኑ መልከጸዴቅ ነበር። ካህኑ መልክጸዴቅ ምሥጢራዊ ሰው ሳይሆን በቀጥታ ዘር ሐረጉ ሳይዛነፍ ከካም፣ የወረደ 11ኛ ትውልድ ነው። አብርሃምና መልከጸዴቅ ፈረንጆቹ distance cousin (የሩቅ የአጎት ልጆች) የሚሏቸው ናቸው።

መጽሐፈ ብሩክ ዣንሸዋ ቀዳማዊና ቀጥሎ ሰረገላ ታቦርን ስናነብ፣ ካህኑ መልከጸዴቅ ሦስት ወንዶችና አራት ሴቶች ልጆች እንደነበሩት እናገኛለን። ከሦስቱ ወንዶች፣ አንዱ ኢትኤል፣ በኋላ፣ ኢትዮጵዮ የተባለ የበኩር ልጁ እንዳለ እንገነዘበለን። በዚህን ጊዜ የከነዓን ምድር በሰው ተጨናንቃ ነበር። የሴም ልጆችም በዝተው ነበር። የካም ልጆችም እንደ የምድር አሸዋ በዝተው ነበር። በየጊዜው ለከብቶቻቸው ግጦሽና ውሀ፣ ለሚያርሱት መሬት፣ ከሴም፣ ከያፌትና ከወንድሞቻቸው ጋርም እየተጋፉ ይጣሉ ነበር። በዚህ የተነሳ፣ ኢትዮጵ ከብቶቹንና ቤተሰቡን ይዞ ወደ ሲን (Sinai) በረሀ ወረደ ይለናል ሰረገላ ታቦር ገጽ 307። ከሲና ተንስቶ ወደ ደቡብ የዓባይን ወንዝ ተከትሎ እንደሰፈረ እንረዳለን። በዚህ መሠረት፣ ኢትዮጵ ግብጽን፣ ሱዳንን እና የዓባይ ምንጭ የሚፈልቅባትን መሬት የራሱ ርስት አድርጎ በራሱና በልጅ፣ በልጅልጆቹ ማንም ሳይጋፋው ማስተዳደር ቀጠለ። የያዛቸውም መሬቶች እንዳሉ የኢትዮጵ ምድር ወይም ግዛት እንደተባለ ጥንታዊ መዛግብት ላይ ተጽፏል። ሌላም ቦታ፣ የያፌትም ልጆቹ ሆኑ የሴም ልጆች በሄዱበት በራሳቸው አባቶች ስም የያዙትን መሬት መሰየም የተለመደ ነው። ለመሳሌ እንግላንድ የኢንተርኔት ምድር ናት። ስኮትላንድ፣ የስኮቲሾች ምድር ግዛት ናት። አየርላንድ፣ የአይሪሽች ምድር ናት። ምድርን ወይም ግዛትን አንዳንድ ቦታ በ..”ያ” (..ia) ተቀጽላ ይተኩታል። አረቢያ የአረብ ምድር ናት። ኢንዲያ የህንዶች የሚኖሩባት ምድር ናት። ዩጎስላቪያ፣ የዩግስላቮች አገር ነበርች። ራሺያ የሩስኪዎች አገር ናት። ሶማሊያ፣ የሶማሌዎች ምድር ናት። እንደዚሁም የኢትዮጵ ግዛት የነበረችው ጠቅላላ አህጉር ኢትዮጵያ ትባል ነበረ። ውቂያኖሷም፣ የኢትዮጵያ ውቂያኖስ ነበረ። 



በኋላ ላይ ግሪኮችም፣ ሮማውያንም፣ ሌሎችም ቅኝ ገዢዎች ኢትዮጵያን ወይም የኢትዮጵ ምድር ወረሯት። የአህጉሩንም ስም 17ኛ መቶ አጋማሽ ክፍለዘመን ላይ ሮማውያን “አፍሪካ” ብለው እንደሰየሟት ከተለያዩ ምንጮች እንረዳለን[ix] የጥንት ነባር ካርታዎችን ስናይ፣ የትም ቦታ ኢትዮጵያ የሚል እንጂ ኩሽ የሚል አገር አታገኙም። የሆኑ፣ የኋላ ታሪክ ተመራማሪዎች ነን የሚሉ ሰዎች ናቸው ጥቁሮቹን አፍሪካውያንን ግብጽን ተከትለው “ኩሽ” ብለው ያረፉት። ከየት አመጡት? የኛዎቹ ጉዶች ያንን ይዘው ይንኮሻኮሻሉ። እግዚአብሔር ይማራቸው።

የሆነ ሁኖ፣ የኢትዮጵ 10 ትውልድ ዛሬ አፍሪካ የተባለችውን፣ የኢትዮጵን ምድር እስከዮቶር ድረስ ተራ በተራ እንዳስተዳደሯት እናገኛለን። ዮቶር ማለት፣ የሲጳራ አባት፣ የግብጻዊው ሙሴ አማት ነበር። ስማቸውን ስንዘረዝር፣ ኢትዮጵ አዜብን ይወልዳል። አዜብ ሞሪን ይወልዳል። ሞሪ ልብናን ይወልዳል። ልብናም መላክን ይወልዳል። መላክም ጋቢናን ይወልዳል። ጋቢናም አዲያምን ይወልዳል። አዲያምም ኖርኑስን ይወልዳል። ኖርኑስም ዮቶርን ይወልዳል። አንባቢን ላለማሰልቸት፣ እዚህ ላይ ቆም እንበልና ትውልዱ፣ እያለ እስከ ንጉሥ አክሱም ይኸዳል። አክሱም ማለት፣ የኛ ዘመናዮች ያለ ምንም ተጨባጭ መረጃ፣ “አካሱማ” ከሚለው የኦሮሚኛ ቋንቋ የመጣ ሳይሆን፣ ነግሥተ ሳባ የተባለችው ንግሥት አያት ነበር። አክሱምን አካሱማ ያሉን “ሁንዱማ ኬኛዎች” ነገ ሚኒስቶታ የተባለ የአሚሪካ ከተማ ውስጥ እየበዙ መጥቷልና፣ “ማና ሶታ” ነበር እንዳይሉን፣ ምን ይገድባቸዋል?

ስለዚህ ኩሽ ብሎ ነገር አፍሪካ ውስጥ አልነበረም። ባይሆን እንኳን የካም ልጆች ነን ቢሉ ያምርባቸዋል። ከሴምና ከያፌት እኩል ሚዛናዊነቱን የጠበቀ ነዋ። የሴም ልጆች ሴማውያን ናቸው። የያፌት ልጆች እነ ጋሜር፣ ማጎግ፣ ማዴ፣ ያዋን፣ ይልሳ፣ ቶቤል፣ ሞሳሕ፣  ቴራስና የልጅ ልጆቻቸው በሙሉ ያፌታውያን ነው የሚባሉት። የካም ልጆች ካማውያን (Hamites) እንዳይባሉ ጥራዝ ነጠቅ የኦሮሞ ልሂቃን ያንኮሻኮሹት ምን ተአምር ተፈጥሮ ነው? ምን ለመደበቅ ታስቦ ነው ከጊዜ በኋላ ኩሽ የተባሉበት ምክንያት?

ታዲያ እኛ ኢትዮጵያውያን ማን ነን? የሚቀጥለው ክፍል ያብራራዋል።

5)   ማጠቃለያ - እኛ ማን ነን?

እኛማ ዓለም ያወቀን ጸሐይ የሞቀን ከጥንታዊቷ ኢትዮጵያ ስንቀነስ፣ ስንቆረጥ የተረፍን፣ የአባታችንን፣ የኢትዮጵን ስም ወርስን የቀረን ኢትዮጵያውያን ነን። እየቆረሱን አናልቅ ብለን ያስቸገርናቸው ህዝብና አገር ነን። አጼ ዘርዓ ያቆብ እንኳን 15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከዛሬው በእጅጉ የሰፋች አገርን ሲያስተዳድሯት ነበር። ትላንት፣ ዓይናችን እያየ ጂቡቲና ኤርትራ ሌላ አገር ሁነዋል። ዛሬ፣ ዘረኞች 83 ቦታ በቋንቋ ሸንሽነውን፣ የፈለገ መገንጠል ይችላል የሚል “ሕገ መንግሥት” ቀርጸው፣ ሊለያዩንና የኢትዮጵያን ስም ከምድረ ገጽ አጥፍተው በኩሽ ሊቀይሩ ሲታትሩ እናያለን። በተለይ ኩሽ ኩሽ እያሉ የሚጮኹ የኦሮሞ ልሂቃን በሚያስፍር ሁኔታ ህዝቡን በሴምና በኩሽ ከፍለው ደም ለማፋሰስ ሌት ተቀን ይጥራሉ። ነገሩ፣ ጸረ ሴማዊነት (antisemitic)(x) ፕሮፌሰር ግርማ ብርሀኑ ቢጠቁምንም፣ ቦታውን የሳተ ነው። እዚህ ሴማውያን የሉም። እስራኤልና፣ አንዳንድ የተሰደዱብት አገር ነው የሚኖሩት። እዚህ የነበሩትም ሂደዋል። "ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ" ይሉሀል ይኸ ነው።

ኩሽ ኩሽ ባዮችን እረፉ እንላለን! አታንኮሻኩሹብን! ኩሽ ብሎ ነገር የለም። ካምና ሴም የሚባል የተከፈለ ህዝብ የለንም። የዘመናችን ታልቁ የቤተክርስቲያናችን በሕይወት የሚገኙ ሊቅ፣ አባታችን ቀሲስ አስተራዬ ጽጌ፣ “ሕብረ ሐመልሚል” በሚል ርዕስ “የአቶ መላኩ አስፋ የሕይወት” በሚል ርዕስ በሚያዝያ 1 ቀን 2006  ዓ.ም. ባበረከቱት ጽሑፍ እንዲህ ብለው ነበር።

የመላኩ ሰውነት   አርአያ ኮሰኮስ ዘብሩር የተባለውን  የሁላችንን ሰውነት  የምንመለከትበት መስተዋታችን ነው።   በሌላ  አገላለጽኢትዮጵያዊነታችን በለመለመ መስክ በቅለው፤ አብበው፤  በሩቅ የሚታዩ  የጽጌ ረዳ፤ የአደይ አበባ፤ የሶሪት አበባ፤ የሱፍ አበባ መሳይ ይህ ቀረሽ የማይባል የውበት ውጥንቅጥ ማለት ነው። ከዚህ ውጭ ነኝ የሚል ኢትዮጵያዊ ካለ፤ ወፍ ዘራሽነትህን ተቀብለህ ቦታህን ፈልግ ሊባል ይገባዋልእያሉ ሊቃውንት አበው አስተምረውናል።

ይኸ አባባል ዝም ብሎ ነገር ለማሳመር የተነገረ፣ ሳይሆን ሀቅ ላይ ተመሥርቶ የተነገረን፣ ዕውንተን ያዘለ ጥልቅ መልዕክት ነበር። ምሑራዊ ትንተና ነው። አባታችንን “ቃለ ሕይወት ያሰማልን” እያልኩ፣ ወደሌላው የመጨረሻ የኩሽ ትርክት የቀብር ሳጥን ላይ የሚመታ 12 ቁጥር ሚስማር ልለፍ። ይኸውም ኩሽ ወይም ሴም የምባል ዘር አለመኖሩን የሚነግረን ሳይናስዊ ቀመር ነው። አረቦች ሐባሽ ያሉን ምክንያት ነበራቸው።

በአገራችን፣ ጥርት ያለ ኩሽ የለም፣ ሴምም የለም ስንል በታሪክ በሳይንሱም ላይ ተመርኩዘን ነው። ኢትዮጵያዊያን ነን። የምንናገረው ቁንቋ፣ የማን ልጆች መሆናችንን፣ ማንነታችንን ሊያሳየን አይችልም። ቋንቋ የሕብረሰብ መግባቢያ እንጂ፣ የዘር ሀረግ መምዘዢያ አይደለም። ዕረፉ አትንኩሻኮሹብን! በታሪካችን፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በ20ኛው መቶ መጨረሻ ክፍለ ዘመንና በ21ኛ መቶ መጀመሪያ ኢትይጵያውያን በዓለም በስደት እንደጉድ ተዘርተናል። ልጆቻችን እንግሊዝኛ፣ ፈረንሳይኛ፣ ስዊዲሽኛ፣ ኖርዊይጅኛ፣ ጀርመኒኛ፣ ግሪክኛ ጣሊያንኛ፣ ስፓኒሽ፣ ... ወላጆቻቸው እንደተሰደዱብት አገር አፍ መፍቻ ቋንቋቸው አድርገው ያድጉበታል። ታዲያ ያ አይደለም ማንነታቸውን የሚውስነው። ኢትዮጵያውያን ከአገራቸው ሲሰደዱ፣ ኢትዮጵያን በልባቸው ይዘው ነው በዓለም የተዘሩት። በሂዱበት፣ የራሳቸውን ባህልና አኗኗር ይዘው ነው የሚንከራተቱት። እንዲያውም፣ የኢትዮጵያዊነት ስሜት የሚብስባቸው፣ አገራቸው እየኖሩ ሳይሆን ከአገር ሲወጡ ነው ብል ማጋነን አይሆንብኝም። ምግባቸው እንኳን በተቻለ መጠን አትለውጥም። የኢትዮጵያ በረበሬ ጣዕም ሌላ ቦታ የለችም። ምጥን ሽሮአቸው እንኳን አትለያቸውም። በሔዱብት ሬስቶራንታቸው፣ ትከተላቸዋለች። በዓላቶቻቸውን ልክ እንደ ኢትዮጵያ ነው የሚያክበሩት። ቤተ ዕምነታቸውም፣ አብራቸው ተሰዳለች። ልጆቻቸውንም፣ በኢትዮጵያዊ ጨዋነት ለማሳደግ ነው የሚጥሩት። ሕጻናቱ፣ ኢንደሌላው ሕብረተሰብ፣ የማንነት ጥያቄ (identity crisis) ጭንቀት አይታይባቸውም። በኩራት ኢትዮጵያዊነታቸውን ይናገራሉ። ኤርሚያስ በትንቢቱ (13:23) በውኑ ኢትዮጵያዊ መልኩን፣ ወይስ ነበር ዝንጉርጉርነቱን ይለውጥ ይችላልን?” ያለበት ምክንያት ነበረው። ቂሲስ አስተራየን የሚሉትም ይኸንኑ ውበት ነው። አንድ የሚያደርግን፣ በውስጣችን የሚዘዋወረው የደማችን አንድነት ነው እንጂ፣ የምንናገረው 83 ቋንቋዎች አይደለም።

እስቲ አንድ ከዚህ በታች የአለውን የዘረመል (DNA) ምርመራ ውጤት ከልብ ተመልክቱ። ወደ ሌላ አትዩ! አትኩራችሁ ተመልከቱ፡ አጥኑ! አገናዝቡ! ምን ይታያችኋል?



አንድ ንጹህ ኦሮሞ ፈልጋችሁ አታገኙም። አንድ ንጽህ አማራም ፈልጋችሁ አታግኙም። ኩሽ እየተባለ የሚንኮሻኮሽበት ኦሮሞ የኦሮሞ ልሂቅ፣ ከአማራው፣ ከአፋሩ፣ ከትግሬው፣ ከወላይታው ተደባልቋል። ለመድኃኒት እንኳን ንጹህ ኦሮሞ አይገኝም። እምኑ ጋ ነው ኩሽነቱ? እንድገመው! ቋንቋው? ቋንቋንማ ማንም ሊናገረው ይችላል። ስንት ኦሮሚያ ውስጥ የተወለዱ አማሮች ተብለው የተፈረጁ ኦሮሚኛ የመጀመሪያ ቋንቋቸው እንደሆነ እነዚህ የተማሩ መሀይማን ይረዱ ይሆን?

አማራውም ቢሆን፣ ከኦሮሞው፣ ከአፋሩ፣ ከትግሬው፣ ተደበላልቋል። ደሙ ሲመረመር አንድ ንጹህ አማራ በአጉሊ መነጽርም (microscope) ተፈልጎ አይገኝም። እምኑ ጋ ነው ሴማዊነቱ? ቋንቋውን ስለተናገረ? እንዳልነው ቋንቋማ መግባቢያ ነው። ስንቱ አማራ ያልሆነ ይራቀቅበታል።

እናንተ የተማራችሁ መሀይማን! ኩሽ አገራችንን ረግጦም አያውቅም። የኖረው ክ7023 ዓመት በፊት በከነዓን ምድር ነው። ወደዚህ የመጣው ከኩሽ 12ኛው ትውልድ ኢትዮጵና ቤተሰቡ ነበሩ። በዝተው ተባዝተው አህጉሯን ስለሞሏት ግዛቱም ኢትዮጵያ ይባል ነበር። ኢትዮጵያ በታሪኳ ስደተኞችን ስትቀበል የኖረች ናት። በተለያየ መንገድ በአረቢያም ይሁን በሱዳን በኩል በተለያየ ጊዜ የሴም ልጆች ወደ ኢትዮጵያ ቢመጡም ከካም ልጆች ጋር ተጋብተው ተዋልደው ቀሲስ አስተራየ እንዳሉት “ህብረ ሐመልሚል” ፈጥረዋል። የተለየ ሴም ወይም ኩሽ የምትሉት ነገር የለም። እኛ ኢትዮጵያውያን ነን። አትንኮሻኮሹብን።

ትላንት ያልነበራችሁትን፣ ዛሬም ያልሆናችሁትን፣ ነገም ልትሆኑ የማትችሉትን ኩሽ እያላችሁ አታንኮሻኩሽብን! በሀሰት ተርክት ህዝባችንን አታምሱት። ስላም ስጡን።

አበቃሁ።




End Note - የመጨረሻ ግርጌ ማስታውሻ


[1] ከሴም እስከ አብርሀም ያለው ትውልድ በደረገጹ ላይ ክ10ኛው ተራ ቁጥር ጀምሮ ተደርድሯል። የተወሰደውም፣ ከዘፍጥረት ምዕራፍ 11 ነው።

[2] ትውልድ ሲተነተን እንዲህ ነው፡ ልጅ አባት አያት ቅድመ-አያት ቅም-አያት ቅማንት፣ ሽማት ፣ምንዥላት አንጅላት፣ ፍናጅ፣ ቅናጅ ፣አስልጥ አምስጥ ማንትቤ፣ ደርባቴ

[3] ለምሳሌ፤ የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 26 ቁጥር 18 ላይ “እርሱም ፦ ወደ ከተማ እገሌ ዘንድ ሂዳችሁ ፦ መምህር፦ ጊዜዬ ተቃርባል። ከደቀ መዛሙርቴ ጋር ከአንተ ዘንድ ፋሲካን አደርጋለሁ ይላል በሉት።” ማነው እገሌ? መልሱን ከሐሙሱ ሰይፈ ሥላሴ፣ ተአምሩ ላይ 318ቱ ሊቃውንት ከአሪዮስ ጋር በኒቅያ ጉባኤ ሲከራከሩ፣ በቁጥር 18 ላይ፣ ይኽ እገሌ፣ ወዳጁ አልዓዛር መሆኑን እንረዳለን።



[ii] Baum, James E.: Savage Abyssinia, J.H Sears & Company, Inc. Publishers, New York, 1928, P. XVii

[iv] መጽሐፈ ብሩክ፣ ዣንሸዋ ቀዳማዊ ገጽ 269 እና ሰረገላ ታቦር ገጽ 290 (ትርጉም፣ መሪ ራስ በላይ አማን)።

[v] Van Seters, John (2004). The Pentateuch: A Social-science Commentary. Continuum International Publishing Group. ISBN 978-0567080882

[vii] https://stockton.edu/hellenic-studies/documents/chs-summaries/kantzios96.pd

[viii]f

[viii]https://www.pbs.org/wonders/Episodes/Epi1/1_wondr2.htm#:~:text=Kush%2C%20the%20Egyptian%20name%20for,Third%20Cataract%20of%20the%20Nile.

[ix] https://youtube.com/shorts/kdMNA-szyKk?feature=share

x Girma Berhanu: The New Frontier Of Antisemitism: Racial Discourse And Oromo Extremism In Ethiopia – Analysis, https://www.eurasiareview.com/29062023-the-new-frontier-of-antisemitism-racial-discourse-and-oromo-extremism-in-ethiopia-analysis/?fbclid=IwAR2qRe-3GyGWSQgqMLmaeKkaFJLltxbr7LTFOEkDiqO5m5GNtMDHcFZ_RTc

Monday, 19 June 2023

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሲኖዶስ ዉሳኔ ቀሳውስቱንና ምእመናንን በተግዳሮት ላይ ጣለን!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሲኖዶስ ዉሳኔ ቀሳውስቱንና ምእመናንን በተግዳሮት ላይ ጣለን!

ቀሲስ አስተርአየ ጽጌ nigatuasteraye@gmail.com


        የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሲኖዶሳችን ቀሳውስቱንና ምእመናንን ከተግዳሮት (ፈተና ) ላይ ጥሎናል፡፡  “ሀሉ አንተ እንበለ ሐሜት ከመ ኢይትዐቀፍ በእንቲአከ አሐዱሂ ወህዝባዊ ያስተሐምም በነፍሱ አንተሰ ጾርከ ጾረ ክቡደ . .. .. . ብከ ዐቢይ ኩነኔ ለእመ ተሐከይከ በእንቲአሁ”( አ ፍ 5፡120)፡፡ ማለትም፦ “በትዳር ውስጥ ያለ ህዝብ ለትዳሩ ለልጁ በሚያስበው ተጽእኖ ለጥፋት የሚመጣበትን መከራ አርቆ የማያት ትኩረት ሊያጥረው ይችላል፡፡ አንተ ግን በህዝብ ላይ የሚያከሰትለውን መከራ አስቀድመህ ማየት እንድትችል ከትዳር፣ ከልጅ ሸክም ተላቀሀል፡፡ ያንዣበበውን መከራ አስቀድመህ የማየት እጽፍ ድርብ ግዴታና ሐላፊነት አለብህ” የሚለው ቃል የሚያተኩረው በመነኮሳት፣ ይልቁንም መንኩሰው ወደ ጵጵስና በመጡ በሲኖዶሱ አባላት ላይ ነው፡፡

        በዚህ ቃልኪዳን ውስጥ የገቡት በሲኖዶሱ ውስጥ የተሰበሰቡት ከትዳር የተገለሉ፣ ለሚስት፣ ለልጅ የማይጨነቁ ለዕለት ጉርስ፣ ለዓመት ልብስና ለመጠልያ፣ ለሞተው ሥጋቸው የማያስቡ ናቸው፡፡ የዘወትር ትኩረታቸውና ጭንቀታቸው በፈቃደ እግዚአብሔር እና በህዝብ ሁለንተና ደህንነት ላይ ብቻ እንዲሆን ለዕለት ጉርሳቸው ለዓመት ልብሳቸው አያርሱም፣ አይቆፍሩም፣ አይነግዱም፡፡ ከምድራዊ ሀሳብ ተላቀው መንፈሳዊ ልዕለ አዕምሮ እርክን ላይ በመድረሳቸው “ይትረኀዋ አዕዛነ ልብ ወይትከሰታ አዕይንተ ልብ ዘውስት ወአኮ እለ ትኩላት ብአፍአ” (አ ቁ 14)፡፡ ይህም ማለት “በሸፍጠኛ አደንቋሪ አንደበተኛ ጩኸትና ጫጫታ አትታለሉ፤ መከራ እየመጣባችሁ ነው፤ ንቁ ራሳችሁን ለመከላከል ተዘጋጁ፤ እያሉ ለሚመሩት ሕዝባቸው መመሪያ የመስጠት ብቃት ያላቸው ብጹዐን ናቸው ተብሎ ይታመንባቸዋል፡፡”

        በመንግሥትነት የተሰለፉ ቡድኖች በአፈሰፊ ካድሬወቻቸው ድንፋታና የቃላት ጋጋት ህዝቡን ባቀረቡለት የተሳሳተ ሐሳብ እንዲወሰን እያደረጉ፤ በስህተት የወሰነውን ወደ ተግባር ለማምጣት ህዝብ ወስኗል እያሉ የሚያደርጉትን ሽንገላ የሲኖዶስ አባል በብጽዕና ብቃቱ የማክሸፍ ሀለፊነትና ግዴታ ነበረበት፡፡ ሲኖዱሱ የሐሰት ፕሮፓጋንዳውን በማጋለጥ፣ መግሥትን ማሸማቀቅና ማሳፈር፣ ሕዝቡን የማንቃት ግዴታ ነበረበት፡፡ ሲኖዶሱ “ዓለሙም ምኞቱም ያልፋል የእግዚ ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘላለም ይኖራል” (1ኛ ዮሐ 2፡16) የሚለውን ቃል በመከተል የቅዱስ እስጢፋኖስንና የሐዋርያትን ትውፊታዊ ምሳሌነት መከተል ነበረበት፡፡ ግን ሲኖዶሱ ሠረዘው፡፡ የተሰረዘውን ሐዋርያዊ ምስሌ ከዚህ በታች እንመልከት፡፡

እስጢፋኖስ የተመረጠለት ሥራ ለእለታዊ ምግብ አከፋፋይነት ነበር፡፡ ከተሰለፈለት አገልጎሎት ይልቅ ባካባቢው በነጻ አውጭነት ስም እየተሰበሰቡ የሚተበትቡት ሸፍጥ በሕዝብ ላይ የሚያስከትለውን አደጋ አርቆ ተመለከተና ወደ ጉባኤያቸው ጥሶ ገባ፡፡ “እናንት አንገተ ደንዳኖች አረመኔወች ልባችሁና ጆሯችሁ ያልተገረዘ ሁልጊዜ እንደ አረማውያን ፖለቲከኞች አባቶቻችሁ ሊቃውንቱን የምትገሉ የሚገስጿችሁን የምታሳድዱ ንጹሐንን ለሞት አሳልፋችሁ የምትሰጡ” (የሐዋ 7፡51_53) ብሎ በሙሉ ልብና ድፍረት ፖለቲከኞችን ገሰጻቸው፡፡

        ሲኖዶሱ- የእስጢፋኖስን ምሳሌ በመከተል በጠ/ሚ ዓቢይና በአቶ ጌታቸው ረዳ ቡድኖች ወደተሰበሰቡበት ጉባዔያት ገብቶ “እናንት አንገተ ደንዳኖች የአረመኔ ልብ ያላችሁ፣ ጆሯችሁ ያልተገረዘ እናቶችንና ሕጻናቱን የምትገሉ፣የሚገስጿችሁን የምታሳድዱ፣ ንጹሐንን ለሞት አሳልፋችሁ የምትሰጡ፣ ባጠመቅናቸው ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ሥጋና ደም የኢትዮጵያን ገጸ ምድር እንዲጨቀይ ያደረጋችሁ፤ ከወገን ደም ጋራ የተቀላቀለውን ውሀ እንድጠጣ፤ ያደረጋችሁ፣ በኢትዮጵያ የሚነፍሰው ነፋስ ትቢያ የሆነውን የወገንን ሥጋ ባፍንጫችን እየጋታችሁ እንዲያስነጥሰን ያደረጋችሁ፤ የወገን አካል ከመሬት እየጠራረገ በላያችን ላይ በመበተን በቁማችን እንድንቀበር ያደረጋችሁ" በማለት በድፍረትና በቁጣ መናገር ነበረበት፡፡ አላደረውም፡፡ እንዲያውም ፊደል ቆጣሪ ሆኖ በፖለቲከኞች እግር ስር ተቀመጠ፡፡

        ከሲኖዶሱ አባላቱ አንዱ አቡነ ሳዊሮስ ርሰዎ ባይርቁን ኖሮ ቤተክርስቲያናችን ከዚህ ላይ አትወድቅም ነበር በማለት ሲኖዶሱ በጠቅላይ ሚ. ዐቢይ አመራር እንዲቀጥል ተማጸኑ፡፡ ዓቢይም ሳዊሮስ በከፈቱላቸው በር ወደ ሲኖዶሱ ሰምጠው በመግባት የመለመሏቸውን ካድሬወች በሐምሌው ስብሰባ እንዲሰየሙ ትእዛዝ ሰጡ፡፡ ሲኖዶሱም ትእዛዙን ተቀብሎ በትህትና (በውርደት) ተሰናበተ፡፡ ሐዋርያት በሕዝቡ ላይ ያንዣበበውን መቅሰፍት እንዳያዩና የሚወገድበትን ዘላቂ መፍትሄ እንዳይፈልጉ ፈሪሳውያን ከወቅታዊ ችግር የራቀና፤ ችግር ባልሆነው በግዝረት ላይ እንዲያተኮሩ በማድረግ ትኩረታችውን ለመጥለፍ በሞከሩ ጊዜ፤ መንፈስ ቅዱስ በቃኘው አዕምሯቸው ለወቅታዊ አደጋ አጋላጭ ያልሆነውን ግዝረትን ገለል አድርገው ሕዝቡን ለከፍተኛ አዳጋ ባጋለጡት በሚቀጠሉት ነገሮች ላይ ብቻ አተኮሩ፡፡

1ኛ፦ ለጣዖት የተሰዋ መብላት

2ኛ፦ ሳይባረክ ወድቆ የተገኘ የእንስሳ ሥጋ መብላት፤

3ኛ፦ደም መጠጣት

4ኛ፦ዝሙት

        ህዝቡን ለእልቂት በሚዳረጉት በነዚህ በአራቱ አደገኞች ላይ ተነጋግረው ወሰኑ፡፡ “በመንፈስ ቅዱስ ምሪት ተመርተን የወቅቱን ችግር ከሚፈታ ውሳኔ በቀር ሌላ ጫና እንዳንጭንባችሁም ተጠነቀቅን፤ ሁላችን ባንድ ልብ ባንድ ሐሳብ የወሰነውን ወደናንተ እንዲያደርሱላችሁ ራሳቸውን ለእውነት ያሰለፉ ሰወች ከመካከላችን መረጥን ላክንላችሁ” (የሐው 15፡28)፡፡ ሐዋርያት ከውጭ የቀረበላቸውን ሐሳብ ወርውረው የመፍትሔውን ውሳኔ መወሰናቸው ብቻ ሳይሆን ውሳኔውን የሚያደርሱት ልዑካን ለተልእኳቸው ታማኞችና እስከሞት ድረስ የሚዘልቁ መሆናቸውን መረዳታቸው የሚያስገርም ምሳሌ ነው፡፡

        የዘመናችን ሲኖዶስ የሐዋርያትን ምሳሌ በመከተል፦ መንግሥት ከፋፋይ እቅዱን የሚያስፈጽሙለትን በጎሳ በቋኗና በክልል እንዲሾሙ መልምሎ ያቀረበለትን አጀንዳ ገሸሽ አርጎ፦

1ኛ፦የግድያውን እቅድ ዘርግቶ እርስ በርሱ ያዋጋው፡ ያገዳደለውና አሁንም በማገዳደል ላይ ያለው ባስቸኳይ ለፍርድ እንዲቀርብ

2ኛ፦እርስ በርስ በሚጋደለው ሕዝብ መካከል ገብቶ እኔን ገድላችሁ ተጋደሉ በማለት መገዳደሉን እንዲያቆም ማድረግ

3ኛ፦ለመከፋፈልና ለእርስ በርስ ግዳያ ምክንያት የሆነውን ሕግ ባስቸኳይ እንዲታረም ለማስደረግ ተጽእኖ መፍጠር ነበር፡፡ አላደረገውም፡፡

        የገደሉ ያስገደሉ ወንጀለኞች በሕዝብ ስም ራሳቸውን ለራሳቸው ይቅርታ እየጠቁ ራሳቸው ለራሳቸው ይቅርታ እየሰጡና ራሳቸውንም ይቅርታ ተቀባዮች በማድረግ እንደገና ከቀድሞው ይልቅ በተጠናከረ ጭካኔ ግድያውን ለመቀጠል ያለ ሐፍረት በድፍረት ራሳቸውን ሰይመው ሲቀርቡ ሲኖዶሱ ባለመቃወሙ ቀሳውስቱንና ምእመናኑ በተግዳሮት ላይ እንዲወድቁ አደርጓል፡፡ በተግዳሮት ላይ የወደቁት ቀሳውስት ቀድሞ የማየትና የመስማት ተላልፎም የመሞት ሐላፊነት የሲኖዶሱ ቢሆንም፡ ቀሳውስት በልጆቻቸው፣ በሚስቶቻቸው፣ በራሳቸው በሁለንተናቸው ከሲኖዶሱ ይልቅ ለህዝቡ የሚቀርቡ ሕዝባውያን ናቸው፡፡ በህዝቡ መካከል የሚካሄደውን የሚፈጸመውን ከጳጳሳት ይልቅ ቀድሞ የሚደርሰው ለቀሳውስቱ ነው፡፡ በህዝቡ ላይ የሚደርሰው ሞቱ፣ ስደቱ፣ ረሀቡ፣ ጽማቱ፣ እርዛቱ፣ ግርፋቱ በቀሳውስቱና በልጆቻቸውም ላይ እኩል ይደርሳል፡፡

        በህዝቡ ላይ እየመጣ ያለውን መከራ ቀሳውስቱ ለሲኖዶሱ የማሳወቅ ግዴታ አለባቸው፡፡ ሲኖዶሱ ቀሳውስቱን የማይሰማቸውና የማይቀበላቸው ከሆነ አትናቴወስ ”እስመ አኅለቁ ሥጋሆሙ በዝሙት” (አት ቁ 82) ሲል እንደተናገረው በሥጋዊ ፈቃድ መሸነፉን መንፈሳዊ ኃይሉ መገፈፉን በዝሙት በመብላትና በመጠጣት መደንዘዙን ቀሳውስት መረዳት አለባቸው፡፡

        የደነዘዙ ጳጳሳት ክምችት የሆነው ሲኖዶስ ለድንዛዜው ምክንያት “ኢታብአን ውስተ መንሱት” የሚለው ነው፡፡ ይህ ቃል በፈተና ስንገባ በሰላም ጊዜ የሚጸለይ ነው፡፡ ከፈተና ከተገባ በኋል እጅን አጣጥፎ በመቀመጥ “ኢታብአን ውስተ መንሱት” እያሉ መጸለይ ብቻ ተፈጥሮንና ፈጣሪውን መካድ ነው፡፡

        ጠቢቡ ሲራክ “እንዘ ይጻላሀው መፍቅደ ሀገሮሙ ወጽሎቶሙኒ ከመ ይጠበቡ በውስተ ኪኖሙ”(ሲራ 38፡34)፡፡ በሚለው ቃሉ ሀገራቸው ከሚሻው ውጭ እንጸልያለን የሚሉ ሰዎች ከመፋለሙ መስክ የማምለጫ ደካማ ዘዴ ነው ብሎ ይህን የመሰለ የላሸቀ ሐሳብ ያላቸውን ደካሞች እንዳጋለጣቸው ቀሳውስት መገንዘብ አለባቸው፡፡

        በዚህ ዓይነት እንቅልፍ ላይ ያሉት ጳጳሳት “ወሎሙኒ ኖሙ ረሲ አክናፈ መላእክት ይክድኖሙ ክበደ ንዋም ኢያስጥሞሙ ዘውእቱ አምሳሊሁ ለሞት” ( ዘሥሩ ቁ 86) እንዲል ከምንግሥት በሚያገኙት ድፍጋፍ ከህዝብ በሚዘርፉት ገንዘብ በሥጋ ፈቃዳቸው ተውጠዋል፡፡ በቁማቸው ሞተዋልና አንቃቸው ቀስቅሳቸው እያሉ በህዝብ ፊት የሚያነቡትን ቀሳውስት ተገንዝበው ሲኖዶሱ በተግዳሮት ውስጥ እንደጣላቸው መገንዘብና በገጽ ለሚያገለግሉት ሕዝብም መግለጽ አለባቸው፡፡

በተግዳሮት ላይ የወደቁት ምእመናን

        ኢትዮጵያ ተጠብቃ የኖረችው በዳዊት ደጋሚ አርበኞች እንጅ በሲኖዶስ አልነበረም፡፡ ምእመናን በዘመኑ ሲኖዶስ ድክመት ወደ ተግዳሮት የገቡት የቀደሙ አባቶቻቸውን ፈለግ በመርሳታቸው ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በፓትርያርክ በሚመራ ሲኖዶስ ከመመራቷ በፊት በእጨጌና በሊቃውንቷ በዳዊት ደጋሚ አርበኞቿ ትመራ በየነበረችበት ጊዜ የነበራትን ንቃትና ትጋት የውጭ ሰዎች ይመኙት ነበር፡፡

        ይህን አጉልተው ከጻፉት ውስጥ፦“The majlis, perhaps the first manifestation of modern Cptic life, was the embodiment of the educated youth’s desire to be accepted by modern Egyptian society. In time this modern waing of the Coptic community would develop its own Ethiopian ideas, quite different from those of the patriarchate, the Holy Synod, and the Coptic Church establishment” (The Cross and the Riverpage page 68) በማለት የነበረውን እያደነቁ ከብዙ ጸሐፊወች Haggai Erlich የተባሉት አንዱ ናቸው፡፡ 

        ጠቢቡ ሲራክ “እቀብ ተግሳጾሙ ለአዕሩግ እስመ እሙንቱሂ ተምሕሩ እም አበዊሆሙ”(ም 8፡9) ማለትም፦ እነሱም ማለትም አባቶቻችሁ ከቀደሙ አባቶቻቸው የተማሩት ነውና የአባቶቻችሁን ምክርና ተግሳጽ ጠብቁ፡፡ እያሉ ያብነቱ መምህራን አባቶቻችን በአጽንኦ ይንገሩን ክነበረው ምክራቸው ጋራ የ Erlich አባባል እጅግ የተቀራረበ ነው፡፡

        ቀሳውስቱም ሲኖዶሱም ድርሻቸውን ካልተወጡ በማለቅ ላይ ያለው ሕዝብ ራሱን ለመከላከል ዓይኑን ከጳጳሳቱ አንስቶ ቅዱስ አትናቴወስ እንዳለው በክርስቶስ ላይ ማተኮር አለበት፡፡ ቅዱስ አትናቴወስ “ኦ ኩልክሙ መሃይምናን እለ ትመስሉ ከዋክብተ ብሩሃነ ዕበይ ልክሙ ሶበ ትሬእይዎ ለእግዚእክሙ ይቀንት ወያንሶሱ ምስሌክሙ ወይሜጥወክሙ ዘዚአሁ ሀብታተ”(አ ት ቁ 99) ያለው በተመሳሳይ

ተግዳሮት ለወደቁት ምእመናን ነው፡፡ ይህም ማለት እናንት ሁላችሁ በጨለማው ዓለም እንደ ሰማይ ከዋክብት ደምቃችሁ የምትፈልቁ ምእመናን ሆይ እናንተን ለማዳን ከለሜዳ ታጥቆ በመስቀል ላይ የቆመውን ክርስቶስን ተመልከቱ፡፡

ይህ አባባል ክርስቶስ መስቀሉን በሥጋው ቢሸከመውም በመለኮቱ ውህደት ነው፡፡ ክርስቲያኖች ሸሽተው የማያመልጡ ተደብቀው የማያሳልፉት የሚመጣባቸውን መከራ የሚሸክመት ክርስቶስ “ዓለም እንዳሸንፍኩት እናንተም በጽኑእ እምነታችሁ በርቱ” ባለው ቃል ተደግፈው እንጅ ከቀቢጸ ተስፋ በራቀ ስሜት አይደለም፡፡ ሮጠው የማያመልጡት ሸሽተው የማያሳልፉት አንዣቦ የመጣ መከራ ሲገጥማቸው “ብሞትም በሕይወት ብኖርም በእግዚአብሄር እጅ ነኝ” ብለው እንዲገቡበት ይገደዳሉ፡፡ ቢሞቱም የማይቀረውን ሞት ነው፡፡ በህወት ቢኖሩም ድሉ የክርስቶስ ነው፡፡ ብለው በተጋድሎው ይገቡበታል፡፡

        ምእመናን አስቀድመው እንዲያዩ እንዲያስቡ እንዲከላከሉ እግዚአብሔር ያስታጠቃቸውን ትጥቅ በተስፋ ሳይጠቀሙ የሚሞቱትን ሞት “እግዚአብሔርሰ ኢገብረ ሞተ አላ ረሲአን ጸውዕዎ ወአርከ አምሰልዎ”(ጥ. ም 1፡18 ) ብሎ ገልጾታል፡፡ ማለትም ሸሽተው የማያመልጡትን በፍርሀትና በእምነት ጉድለት እየሸሹ መገደል ኃጢአት እንጅ ጽድቅ አይደለም፡፡ ምእመናን በሲኖዶሱና በቀሳውስቱ ቸልተኝነት የመጣባቸውን አረማዊ ገዳይ ለመከላከል ቆርጠው ከተሰለፉ፡ ዳዊት “ወአሰሰልኩ ጽዕለተ እምደቂቀ እስራኤል” እንዳለው ራሳቸውንና ቤተ ሰባቸውን አድነው ዘላለማዊ ውርደትን ከህዝባቸውና ከሀገራቸው እንዲያስወግዱ እግዚአብሔር ሊያግዛቸው የታመነ ነው፡

        ይቆየን

Sunday, 5 February 2023

ኦርቶዶክስ ተዋህዶን መናዱ፣ ከሦስቱ ግንዶች አንዱ!

 ኦርቶዶክስ ተዋህዶን መናዱ፣ ከሦስቱ ግንዶች አንዱ!



እንግዲህ ከወዴት እንደ ወደቅህ አስብ ንስሐም ግባ ...
ብሎ የጀምራል የዮሐንስ ራዕይ መዕራፍ 2 ቁጥር 5!

 ወንድሙ መኰንን፣ እንግላንድ 05/02/2023

መግቢያ

ዘረኞች ካሉ ማን በሰላም ተኝቶ ያድራል? ዘሮኞች ሥልጣን ላይ ከወጡማ፣ አያድርስ ነው። የጎጠኝነትን ጠንቅ በሩዋንዳ አይተናል። የአንድ አገር ልጆች በጎሳ ተከፋፍለው፣ ተጨፋጨፉ፣ ተገዳደሉ። ያሸነፈው አሸንፎ፣ ተሸናፊው በጄኖሳይድ ተክሶ እስከዛሬ ይወቀሳል። ከስህተቱ የተማረ የሩዋንዳ ህዝብ ዛሬ፣ ስለዘር ማውራት በሕግ የተከለከለ ነው። ዘረኝነት በዚያ አገር ዛሬ ዕርም (ታቡ) ቃል ነው። “የአበራሽን ጠባሳ ያየ በእሳት አይጫወትም” ይላል ያገሬ ሰው። ኢትዮጵያውያን ግን ከሩዋንዳ መማር አልቻልንም። ትላንት መጥፎ ጊዜ አሳልፈን ነበር። ዛሬም ህዝባችን አሣሩን እየበላ ነው። ሕዝባችን ተገፍቶ ከድጡ ወደማጡ ገብቷል። ነገስ?

የኢትዮጵያ ዘረኞች ጥምድ አድርገው የያዙትና በየጊዜው የሚያቆረቁዙ፣ የዘረኝነት ስሜት ያልነበረውን መንዜውን፣ ጅሩዬውን፣ መርሀቤቴውን፣ ቡልጌውን፣ ተጉለቴውን፣ ወሎዬውን፣ ጎጃሜውን፣ ጎንደሬውን “አማራ” እያሉ ነው። ይኸን አማራ፣ በምናባቸው ጭራቅ አድርገው ስለው ቀን ሲያናውዛቸው ውሎ ማታ ሲያቃዣቸው ያድራል። ይኸን ምስኪን ሕዝብ ያለጥፋቱ ጥፋት ፈጥረውለት፣ (ለምሳሌ የአኖሌ የሌሌ ታሪክ) ጠብ ያለሽ በዳቦ እያሉ ይጨፈጭፉታል። ዓላማቸው ኢትዮጵያን ማፍረስ ነው። ሌላው የኢትዮጵይዊነት ትልቁ ግንድ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ክርስትና ነው። የአንድነት ተምሳሌቱን ከሦስቱ አንዱን ግንድ መገንደስ ማለት የኦርቶዶክስ ሀይማኖትን ማጥፋት ነው። ለነገሩ ደግ የማይመኙልን እንድ ባሮን ሮማን ፕሮቻዝካ (Baron Roman Prochazka)[i] እና ጄምስ ኤድዊን ባውም (James Edwin Baum)[ii] የተባሉ የነጩ ዓለም ጸሐፊዎች፣ እንዲሁም የአሜሪካ ስቴትስ ዴፓርትመንት ዋና ጸሐፊ የነበሩት ሄነሪ ኪሲንጀር ኢትዮጵያ ከበለጸገች ለነጩ ዓለም አደጋ ስለምትደቅን ሦስቱን አምዶቿን ማፈራረስ እንደ ረዥም ዕቅዳቸው (ስትራተጂያቸው) ነድፈው ቁጭ ቁጭ አድርገውልናል። አንዱ አንድ የሚያደርጋትን የዘውድ ሥርዓቷን መገርሰስ ነው። ያንን የደርጉ ሥርዓት አሳክቶላቸዋል። ሀለተኛው የኦርቶዶክስ ሀይማኖቷን ማጥፋት ነው። ደርግ ሞክሮ ሳይሳካለት ለዘረኞቹ ትቶት ጠፍቷል። ሦስተኛው፣ አማራ የሚባለውን ህዝቧን ከሌሎች ጎሳዎች ጋር አጋጭቶ፣ ማስጨፍጨፍ ነው። የወያኔው ኢህአዴግ ለ27 ዓመታት ሂዶበት አሁን ደሞ የኦህዴዱ ብልጽግና ላለፉት አራት ዓመታት እያከናወነላቸው ነው። ፕሮጄክታቸው፣ ገና አላለቀም።

በከንቱ ልፉ ብሏቸው ነው እንጂ፣ ኢትዮጵያስ አትጠፋም። ኢትዮጵያ ምርጥ የእግዚአብሔር ርስት ናት።

የዘርኝነት ፖሊቲካ በኢትዮጵያ

ዘረኝነትን ሲያሰማምሯት የኢትዮጵያ ዘረኞች “ብሔር ብሔርሰቦች ህዝቦች” ብለው ጠሯት። የፖሊቲካ ቀለም ሲቀቧትም “ፌዲራሊዝም” አሏት። ድንቄም ፊዴራሊዝም! ዓላማቸውን ለማሳካት ህዝቡን በቋንቋ ከልለው፣ “በአፍ መፍቻህ ቋንቋህ ተማር” አሉት። እንዳይግባባ እኮ ነው! ትልቁ ከፋፍሎ የመግዛቱ ፍቱን ዘዴ የህዝቡን መግባቢያ በቋንቋ አጥፍቶ መደበላለቅ ነው። ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አገራት የምትለየው አንዱ የራሷን ፊደል መጠቀም ነው። ህዝቡን የጋራ እሴት እንዳይኖረው አንድ ፊደል እንኳን እንዳይጠቀም፣ ኩቤ የሚባል የላቲን የፊደል ሾርባ ሾርበው ጋቱት።

ታላቋ የተዋጣላት ፌዴራሊስት አገር ብትኖር የተባበረችው አሜሪካ (United States of America – US) ናት። ከዚህ በኋላ እንዲቀለን፣ አሜሪካ እንበላት። እንደ አገሪቱ የሕዝብ ቆጠራ ስታቲስቲክስ ጽሕፈት ቤት፣ በአሜሪካ 350 ቋንቋዎች ይነገራሉ። ከንግሊዝኛ ሌላ፣ ከሦስቱ ሁለቱ የአሜሪካዊ የሚናገረው ስፓኒሽ ነው። የፌዴራሉ ቋንቋ ግን እንግሊዝኛ ነው። ትምህርቶቹም በቀደምትነት የሚሰጡት በእንግሊዝኛ ሲሆን፣ ተጨማሪ ቋንቋ እንደፍላጎቱ በትምህርት ቤትም በዩኒቨርሲቲም ይሰጣል። ግዕዝም ሳይቀር። በዚህ የተነሳ ከሎስ አንጀለስ እስከ ኒው ዮርክ ከተሞች፣ ሕዝቡ በአንድ ቋንቋ ይናገራል፣ ይግባባል፣ ይነጋገዳል፣ ከቦታ ቦታ ተዘዋውሮ ይሠራል። አስተርጓሚ አያሻውም። አገሪቷ፣ በሳይንስ፣ በቴክኖሎጂ፣ በኢኮናሚ በልጽጋ፣ ልዕለ ኃያል ህናለች። እነዚህ እንግዲህ በእውነቱ የተዋህዱ ሀምሳ አገራት ናቸው። እኛስ? አቦ ተወና!

ዘረኝነት የተጠናወታቸው የሕወሀት ሊሂቃን ተደራጅተው፣ የኢትዮጵያ ሕዝብን ተዋዶ፣ ተፋቅሮ፣ እና ተጋብቶ ተዛምዶ ከሚኖርበት፣ በዘር በታተኑት። በለስ ቀንቷቸው ለ27 ዓመታት በሕዝቡ ልብ ውስጥ ዘረኝነትን ዘሩት። ኢህአዴግ የሚባል ካባ ደርበው፣ የዘረኞች ካድሬ አሰልጥነው ሕብረተሰቡን በዘረኝነት  መርዝ በከሉት። የዘረኛ ሕገ-መንግስትም ቀርጸው አከናነቡት። የዘሩት የዘረኝነት ዘር፣ ዛሬ ላይ በቅሎ አብቦ፣ ፍሬው ጎመራ። ዘረኝነትን ይጸየፍ የነበረውም ”ከሌላው በምን አንሼ፣” በሚል ስሜት ዘረኛ ሁኖ ቁጭ አለ። ታዲያ በአገራችን ፍሬው የጎመራው ዘረኝነት ውሎ አድሮ መልሶ ፈጣሪውን የትግራይ ጽንፈኛን ቀረጠፈው። ጄኖሳይድ እያለ ቢጮህ ማን ይሰማዋል? ሥራ ለሠሪው እሾህ ላጣሪው ይባላል። ሌላ የራበው ዘረኛ ተነሳለታ! ለሕዝቡም ተረፈለት። ለኃጢያን የመጣ ለጻድቃንም ይተርፋል ይባል የለ? መቅሰፍቱ እሱን ብቻ ይዞ በጠፋ! አማራውንና አፋሩን ረፈረፈው።

በወያኔ ሥር ተኮትኩቶ አድጎ ለቁምነገር በቅቶ፣ ጊዜ ጠብቆ፣ የሕዝቡን ብሶት ተጠቅሞ፣ አሳዳጊዎቹ ላይ በብልሀትና በዘዴ አምጾ፣ በተለይ አማራውን አግባብቶና አወናብዶ (convince and confuse)[iii] የአራት ኪሎን ወንበር የነጠቀው ተረኛው ዘረኛ የኦሮሞ ጽንፈኛ ሁኖ ተገኘ። ኮቱን ገለበጠና “ብልጽግና” ነኝ አለ እንጂ ያው እህአዴግ ነው። ያው የዘረኝነት እንጂ ሌላ ሥርዐት እኮ አያውቅማ። ለውጥ መጣልን ብለን አሸሻ ገዳሜ ያልን ሁላ ካለንበት ወርደን ከድጡ ወደ ማጡ ወድቀን እየዳከርን ነው።

እርካቡን ረግጠው መንበሩን የተቆጣጠሩት ዶር ዐቢይ

አንድ ዲራአዝ የተባለ ጸሐፊ በደረሰው “እርካብና መንበር" የተባለ ድንቅ መጽሐፍ ክፍል አንድን፣ በአልበርት አንስታየን አባባል እንዲህ ሲል ይጀምራል፡ “ችግሩን በፈጠረው አስተሳሰብ፣ ችግርን መፍታት አይቻልም” ይላል። ድንቅ ጥቅስ ነው። አንድ ዘፋኝ እንዲህ ይላል።

በሀሰት ስትምዪ፣ ምላስሽ ልስልስ ነው፤
ቅርሽም እንደ አፍሽ፣ ቢሆንልኝ ምነው?

ዶክተር ዐቢይ የመጡልን (ዋ! የመጡብን አላልኩም፣ ነገሬን አታጣምሙብኝ) የወያኔ የዘር ፖሊቲካ ከገማና ከገለማ በኋላ ነው። እሳቸውም የሄዱበት መንገድ በዚያው ፍልስፍና ነው። ሕዝቡ ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ፣ በግፍ ሰንሰለት ታስሮ የጭቆና አስተዳደሩ ብሶት አንገብግቦት ምድሪቱን ቀውጢ አደረጋት። ኦሮሞው በቄሮ ተደራጅቶ መትረየስና ቦምብ የታጠቀውን በዶ እጁን ከአናቱ በላይ አጣምሮ ተጋፈጠ። የሚችሉትን ያህል ገደሉ። ቆራጡ አማራ በፋኖ ተደራጅቶ፣ ሀምሳ ቢሞትበት አሥሩን እየደፋ፣ ተመመ። “በከንቱ ኦሮሚያ ውስጥ የሚፈሰው የኦሮሞ ደም ደሜ ነው” ብሎ ሲያውጅ፣ የወያኔ የዘረኛ መንበር ተነቃነቀ። ጉራጌው ዘርማ በሚል የወጣት ክንፍ ተጋፈጠው። ደቡቡ ነብሮ ብሎ ተነሳበት። ጥግ ይዘው ተራቸውን ይጠባበቁ የነበሩት፣ ብልሀተኛ የኦሮሞ ሊሂቃን ተመካከሩና፣ “ኢትዮጵያ ሱሴ ናት”ን  እየዘመሩ ዐባይን ተሻገሩ። “ትግሬ ከፋፈለን እንጂ አንድ እኮ ነን” ሲሉ አማራው እጁን ዘርግቶ እንባውን እየረጨ፣ አርባ ጉጉን ረስቶ፣ በደኖን ረስቶ፣ ወተርን ረስቶ ... አቅፎ ተቀባላቸው። ካባ አለበሳቸው። ኢትዮጵያዊነት በደም ሥሩ የሰረጸው አማራ፣ ያለምንም ማቅማማት፣ በውሸት ትርክት ጭራቅ ሁኖ መሳሉን ረስቶ፣ የተቆረጠ ጡት ባልዋለብት እሱ እንደቆረጠው ተቀርጾ የቆመውን ሐውልት እንኳን ዞር ብሎ ሳያይ፣ “ኦሮማራ” በሚል ወጥመድ ገባላቸው። ዶር ዐብይ “በሬ ሆይ ሣሩን አየህና ገደሉን ሳታይ” የሚሉት ይኸንን ነው። ከሁለቱ እርካብ አንዱ ሆነላቸውና ለዶክተር ዐብይ ወደ መንበር መወጣጫ ተመቻቸላቸው።

ዶክተር ዐብይ ልዩ ስጦታ ያላቸው ተናጋሪ (ኦራቶር) ናቸው። እንደመጡ ልባችንን መርምረው ስለሚያውቁት የምንፈልገውን እየነገሩን፣ በፍቅር አናወዙን። “ኢትዮጵያዬ” ስሉን፣ ዓይናችን ጭልምልም ልባችን ስልምልም አለላቸው። ተነጠፍንላቸው። የትግሬው ዘረኛ ገዥ መንበሩን ጥሎላቸው ወደመቀሌ ነጎደ። የኦሮሞው ገዥ መደብ በዶክተር ዐብይ እየተመራ ወደ አራት ኪሎ ሂዶ መንበሩ ላይ ጉብ አለ! የበሻሻው አራዳ፣ ዶር ዐብይ ሆዬ፣ ተቃዋሚውን “ና ግባ” ብለው ቀይ ምንጣፍ አስነጠፉለት። ከኦሮሞ ነጻ አውጪ ሠራዊት በስተቀር እያንዳንድዱ ተቃዋሚ መሣሪያውን ቁጭ አድርጎ ገባላቸው። እሳቸውም፣ “ከዚህ በኋላ ስምህ "ተፎካካሪ” እንጂ “ተቃዋሚ” አትባልም አሉት። ጌታ እየሱስ ሳናስበው በአቋርጭ ተመልሶ መጣ እንዴ ያልንም ነበርን። ሁሉም አዚም አንዳዞሩብት በያለበት በፍቅር ገበረላቸው። ተቃዋሚውን በዚህ መንገድ እሹሩሩ ብለው አስተኙት። ፈርንጆች እንዲህ ዓይነቱን ሁኔታ “hypnotic stupor”  ይሉታል። አፈዝ አድንግዝ እንበለው? እስረኞችን፣ የሞት ፍርድ ላይ ያሉትን ሳይቀር ፈቱልን። ከዚህ በኋላ አንድ ሰው ወንጀሉ ሳይጣራ አንሳርም። አስረን አንመረምርም አሉን። ዘፈን ተዘፈነላቸው። የጉራጌ ምስኪን እናቶች አታሟቸውን (ዲቤያቸውን) እየደለቁ፡

በአማርኛ ውሀ፣ በእንሊዝ ወተር
ዐቢዬን የጠላ፣ ሆዱን ይተርተር

 ብለው በሚጣፍጥ አማርኛቸው ዘፈኑላቸው። ባሀሩን የሚያሻግረን ሙሴ መጣልን ተባለ። ሱዳን ሂዱና ጃንሆይ እንዳደረጉት፣ የሱዳን ተቃዎሚዎች አገሪቱን ከማያበራ የእርስ በርስ ጦርነት አፋፍ መለሱት። ወደኤርትራ ሳይጋበዙ ሂደው የኢሳይያስን ልብ ብልት አድርገው፣ ወያኔ አልጀርስ ላይ የፈረመላቸውን ባድሜ አስርከቡት። ምን መጣ ተባለ! አሜሪካ ሰተት ብለው ሂደው፣ ስደተኛ የኦርቶዶክስ ፓትሪያርኩን አግባብተው ወድ ኢትዮጵያ መልሰው ከአባ ማትያስ ጎን አስቀመጧቸው። ዐብይ ማኒያ አሉት ፈረንጆቹ።

ኖርዊይ የኖቤል የሰላም ሽልማት ቸረቻቸው። አሜሪካ ሂደው የወያኔ ባልሥልጣናትን ያዋክብ የነበረውን ዲያስፖራ እሹሩሩ ብለው አስተኙት። ጀርመን ሂደው፣ የአውሮፓውን ዲያስፖራ አፍዘውት በድል ተመለሱ። መንበራቸው የጸና መሰለ! ህወሃት ኢህአዴግን እንዲያገለግል እንደፈጠረችው ሁሉ፣ ኦህዴድ እንዲያገላቸው ብልጽግና መሠረቱ። የኔ ቃል አይደለም። የሽመልስ አብዲሳ ቃል ነው።

ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ አንድ መልክት አለኝ! ሰው እንዳማረበት አይሞትም። ዛሬ ከሕገወጡ መፈንቅለ ሲኖዶስ የፈጸመው፣ የኦሮሚያ ሲኖዶስ ነኝ ላለው “በቋንቋዬ ልቀድስ ብሎ መነሳቱ ትክክል ነው” በማለት ዕውቅና ሰጥተውታል። በዚያ ምክንያት የኦሮሞ ልዩ ኃይልና ሚሊሺያ በየቦታው የኦርቶዶክስ ምዕምናን ሕይወት ቀጥፎ ቤተክርስቲያን ሰብሮ ገብቶ ለህገወጦቹ አስረክቧል። አንዱ እርካባቸው ተበጥሷል። መንበራቸውም ተነቃንቋል። አንድ እርካብ አይስተማምንም። የደርግና የወያኔ እጣ ይጥብቃቸዋል።

ባለጊዜዎቹ! ያሁኑ ይባስ!

ቀድም ብዬ፣ ሁሉም ተቃዋሚ መሣሪያውን አስቀምጦ አዲስ አበባ ተመልሶ ጎዝጉዞ ሲተኛ፣ የኦነግ ሠራዊት ብቻ ነበር ከነትጥቁ በአሶሳ በኩል ወደ ኢትዮጵያ የገባው። ብልጽግና ለምን ሸኔ እንደሚለው አትጠይቁኝ። አላውቅም። ሞጋሳ ሲችሉበት! ለምሳሌ፣ አብሮ አደግ ኦሮሞ ጉደኞቼ፣ ሁንዴ ጦሬ እያሉ በአንድ ስፖርተኛ ስም ይጠሩኝ ነበር። በፍቅር ነው ታዲያ! እንግዲህ ይኽ የኦነግ ሠራዊት፣ በመጀመሪያ ሥራ ላይ ባዋለው ዕቅድ ወያኔ “ኦሮሚያ” ብሎ ጠፍጥፎ ከሸለመው ክልል ኦሮሞ ያልሆኑትን ዘሮች መንጥሮ ማጽዳት ነው። አማራ የተባለውማ አይወራ። በደኖ፣ አርባ ጉጉ፣ ወተር፣ አረካ፣ አሰቦት ገዳም የጀመረውን ዕልቂት ክግቡ ማድረስ ነበረበት። ይኸን ቆሻሻ ሥራ ሲሠራለት፣ የቀድሞ ኦህዴድ ዝም ብሎ ያያየዋል። ወለጋ የደም መሬት ሆነች። ስለዚህ ወለጋ ውስጥ ደርግ ያሠፈራቸውን ብቻ ሳይሆን ከጥንት፣ አንዲያው ቢያንስ ቢያንስ ከአጼ ዮሐንስ ዘምነ መንግሥት ጀምሮ የነበሩትን አማሮች ማረዱን ቀጥሎበታል። ለዚያ ደሞ፣ የቀድሞ ኦህዴድ የአሁኑ የኦሮሞ ብልጽግና መቶ በመቶ እየተደገፈና እየታጠቀ ደማቸውን ደመ-ክልብ አደረጎታል። ማን ከልካይ፣ ማን እ-ሽ ባይ አለበትና። ከአማራው በተጨማሪ፣ አዲስ አበባ ጠጋ ብለው፣ ቡራዩ ላይ በሰላም የሚኖሩትን የጋሞ ተወላጆችን አረደ! ማን ነክቶት? የጨፈጨፈውን ያህል ጨፍጭፎ ከሄደ በኋል መከላከያ ደረሰ አሉን። ጀብ ከኼደ ውሻ ጮኸ ይሉሀል። ያ ወደዚያ ሂዶ የነበረው የታጠቀ ሠራዊት፣ የሚያደርገው ነገር ሲያጣ፣ ወደ ቤተ መንግሥት ጎራ ብሎ ደሞዝ ጭማሪ ለመጠየቅ ሲመጣ፣ ጠቅላይ ሚንስትራችን አባብለውት ፑሽ አፕ አሠርተውት ሸኙት።

በዚያ አላቆመም። አንድ እነሱ “ዓይናችን” የሚሉት ፖሊቲከኛ “ጥበቃ ተነስቶብኝ ተከብቤያለሁ” ብሎ በነበረው የሬዲዮና የማኅበራዊ ሚዲያ ሲያስተጋባ፣ ከዳር ዳር የኦሮሞ ሕዝብ ግር ብሎ ወጥቶ፣ አማራ ነው ብሎ የገመተውን ሁሉ በሜንጫ ጨፈጨፈው። የጉዲሳ የልጅ ልጅ የሆኑትን የራስ መኰንን ሐውልት ሐረር ላይ ፈነገለው። ናዝሬት ላይ፣ አንዱን ምስኪን ዘቅዝቀው ሰቅለው ገደሉት። ጉራጌዎችም አልተረፉም።

ትንሽ ቆይተው፣ አማራውን የሚገድሉበትን ምክንያት ሲጠፋቸው፣ ተወዳጅ የነበረውን የራሳቸውን የኦሮሞ ዘፋኝ ሀጫሉ ሁንዴሳን ገድለውት፣ “አማራ ገደለው ብለው” አማራውን በተገኘበት፣ በባሌ፣ በሸዋ፣ በሐረር፣ በወለጋ ጨፈጨፉት። ዝዋይ ላይ ከአንድ ቤተሰብ አምስት ሰዎች በአንድ ቤት አረዷቸው። የሻሻምኔን ከተማ ዶጋመድ አደረጓት። አንድ ምስኪን ባለ ልኳንዳ ቤት ጉራጌ አርሲ አግኝተውት ገድለውት በድኑን ከሥጋው ጋር ሰቅለው ሂዱ። እናንተ ባለጊዜዎች፣ ተው ሕዝቡን አታስመርሩት!

ይኸ ሁሉ የአማራ፣ የጋሞ፣ የጉራጌ ግዲያ ሲደረግ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ እንዳላየ ሁነው ማለፋቸው ነው የሚገርመው። በክልላቸው የባሰውኑ፣ ጭፍጨፋ በተፈጸመ ቁጥር፣ እሳቸው፣ ወይ አበባ ወደመትከል፣ ወይ ዛፍ ወደመትከል፣ ወይ ወደእርሻ ይኸዱ ነበር። በአንድ ወቅት፣ አንዱ እንዴት ሰው አልቆ እስዎ ወደ ዛፍ ተከላ ይኸዳሉ ቢባሉ፣ “ምናለበት ባይሆን ዘመዱ የሞተበት፣ ዛፍ ጥላ ሥር ተቅመጦ ያዝናል” ብለው አሾፉ። አማራው ክልል፣ አንድ ነገር ኮሽ ባለ ቁጥር ቅጠልያ የጦር ልብሳቸው ለብሰው ክቸች ማለታቸው ለተመልካች ግርም ይላል።

መስሏቸው ነው እንጂ የኦሮሞ ጽንፈኛ፣ ለሳቸውም አይተኛ። ከዚህ በፊት በመስቀል አደባባይ ሊግድላቸው ነበር። አንዱ የተጠመዱበት ትልቁ ነገር፣ ለምን አዲስ አበባን ከሌሎቹ ብሔር ብሔርሰቦች አጽድተው ለኦሮሞ አልስጡም የሚል ነው። የአፍሪካም ዋና ከተማም ስልሆነች ከአፍሪካኖችም መጽዳት ነበረባት ባዮች ናቸው መሰሉኝ። ፊንፊኔ እያሉ ፊን ፊን ይላሉ። ፊንፊኔ አማርኛ መሆኑን ማን በነገራቸው!

እንደመሰለኝ ከሆነ፣ ሁለት ዓይነት የኦሮሞ ብሔርተኞች ያሉ ይመስለኛል። አንዱ ወገን፣ ከኢትዮጵያ ተገንጥለው፣ የሚችሉትን ያህል መሬት ነጥቀው ታላቋን ኦሮሚያን መመሥረት ይመስለኛል። እየመረቀኑ በሳሏት ካርታ፣ እራሳቸውን ለጥጠው ከትግራይ ጋር አገናኝተዋል። ልብ ዕንቅርት የመኛል አሉ፣ አባቶች። ሌሎቹ ግን፣ እንደትግሬዎቹ የበላይነቱን ይዘው፣ ኢትዮጵያን እንደፈልጉት መግዛት ነው። ሁለቱም ወገኖች፣ የኦሮሚያን ኦሮሞ ካልሆኑት ማጽዳትና፣ ኬኛ የሚሏቸው ግዛቶች ጠቅልሎ መያዙ ላይ ልዩነት የላቸውም። አዲስ አበባንም የመውረር ሕልም አላቸው። ሁሌ የሚገርመኝ፣ የኦሮሞ ጽንፈኞች፣ አዲስ አበባ ዋጠችን እያሉ ሲጮሁ፣ አሁን ደሞ፣ አዲስ አበባን ካልዋጥናት ያዙን ልቀቁን ማለታቸው ነው። አብዛኛው ኦሮሞ ዝም ማለት ከትግሬ ጋር እያመሳሰለው መጥቶብኛል።



ሰሞኑን ኦነግ ከዚህም የባሰ ስፋት እንደሚይዝ ነግሮናል። ጠቅልይ ሚኒስትሩ፣ ይኸን ሁሉ የጽንፈኛ ኦሮሞን መቧረቅ እያዩ እንዳላየ መሆን፣ ይሁንታቸውን መስጠታቸውም ነው የሚያረጋግጠው። አንዳንዴም ድጋፋቸው በግልጽ ነው የሚያስቀምጡት። ሰንደቅ ዓላማውን በየትምህርት ቤቶች ሊሰቅል ሞክሮ፣ የአዲስ አበባ ሕዝብ “ወዲያልኝ ወዲያ!” ሲል፣ የአዲስ አበባ ህዝብ ኦሮሞ ጠሊታ ነው ብለው በአደባባይ ተናገሩ። በውቅቱ እንደማይባል ለማለት ሞክሬያለሁ[iv]። ትምሀርት ቤት ባንዲራችን ካልተሰቀለ፣ መዝሙራችን ካልተዘመረ፣ በቁቤ በየትምህርት ቤቱ ኦሮሚኛ ካልተሰጠ ብለው ያዙን ልቀቁን፣ ሲሉ፣ የመንግሥት ጽጥታ ጠባቂዎች ሕጻናትን እያነቁ እሥር ቤት ማጎራቸውን ዝም ብሎ ማየት ወገናዊነት ነው።

በነገራችን ላይ፣ ዶር ዐብይን የሚገለብጠው ወይ በብብታቸው የያዙት የኦሮሞ ጽንፈኛ ነው፣ አለበለዚያም ሚሊታሪው ነው።ይኸ ሀቅ መነገር አለበት። አማራው እሳቸውን ለመገልበጥ ፍላጎቱም፣ አቅሙም የለውም። እራሱን ለመከላከል ብቻ ነው የሚፍጨረጨረው። በዝምታ እንደበግ ግን አይታረድላቸውም። “ኦኛን ያስቸገረን የኦሮሞ ሸኔና የአማራ ሸኔዎች ናቸው፣” ያሉት ግን ምንኛ ፍርደ ገምድል መሆናቸውን ያሳያል። ገዳዩንም፣ ሟቹንም በአንድ ላይ መደባለቅ የመደመር ፍልስፍናቸው ይሆን? አጣዬ 9 ጊዜ ስትነድ፣ ያነደዳት አማራ ነው? ሸዋ ሮቢትን ያጋያት አማራ ነው? ደራን ወሮ ደም ያፈሰሰው አማራ ነው? በየቦታው ከተማ እይወረረ ወንጀለኞችን ከእሥር ቤት የሚያስመልጠው አማራ  ነው? ከዳንጎቴ የሲሚንቶ ፋብሪካ ሰዎችን እያፈነ እየወሰደ ማስለቀቂያ ግንዘብ የሚቅበለው፣ አማራ ነው?

የኦሮሞ ብልጽግና ከኦነግ ሠራዊት ጎን ሁኖ አገሪቷን እያሸበረ ነውና፣ መንግሥት በመንግሥትነት ለመቀጠል ከፈለገ በመጀመርያ ደረጃ፣ የዶክተር ዐብይ መንግሥት፣ አበባ መትከሉን፣ ለአትክልተኞች፣ ስንዴ ማምረቱን ለግብርና ሚኒስቴር፣ ፓርክ ማሠራቱንና አዲስ ቤተመንግሥት መሥራቱን ለመሀንዲሶችና ሥራ አከፋፍለው ወይም ደሊጌት አድርገው፣ እሳቸው የሕዝብ ደኅንነትና ሰላም ላይ አጥብቀው መሥራት ይጠበቅባቸዋል።

የዘር ፖሊቲከኞቹ ለመንበር ጦርነት

“When the elephants fight, the grass gets trampled.ዝሆኖች ሲጣሉ ሣሩ ነው የሚረጋገጠው!

ከመንበሩ ተፈናቅሎ መቀሌ ላይ የመሸገው የትግሬ ጽንፈኛ ቡድን፣ ይጠብቀው የነበረውን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በተኛበት እምሽክ አድርጎት፣ ለዳግመኝ ንግሥና ጎዞውን ከመቀሌ ጀመረ። ዳሩ ግን፣ ከዚህ በፊት ርስቱን ቀምቶ፣ በጭራቅነት ስሎ በነበረው የአማራ ሕዝብ መሬት ውስጥ ማለፍ ነበረበት። አማራው ተነሳ። ጎንደሬው አላርምድ አለው። በብልጽግና የሚዘወረው የዶክተር ዐብይ ጦር ከሰማይ በአይሮፕላንና በድሮን ሲያጋየው፣ የትግሬዎቹ ዘረኛ ገዢዎች የሞቱት ሙተው መቀሌን ለቀው ወደ ተምቤን በረሀ ሸሹ። መቀሌም ከ20 ቀን ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ወደቀች። የመከላከያ ጦሩ በድንገት መቀሌን ለቆ ወደ መሀል አገር ሲሂድ፣ የብልጽግና መንግሥት ወያኔን ለእርቅ ልመና ገባ። አማራውን ለወያኔ ትቶ ማለት ነው። “የምን ዕርቅ” አለች የዘረኝነት ፈላስፋዋ ወያኔ!

ወያኔዎች የልብ ልብ ተሰምቷቸው ዳግም ጉዟቸውን ጀመሩ። የጎንደር ፋኖ ደሙን ዘርቶ እየተዋደቀ፣ ያስመለሰውን የወልቃይት ሁመራን ርስቱን እንደያዘ አላነቃንቅ አላቸው። እሱን ትተው በአፋርና በወሎ በኩል፣ አሜሪካና መዕራብ አውሮፓውያን እየረዷቸው ጉዞ ጀመሩ። አፋርም ተጨፈጨፈ። ፋኖ አማራውና ሚሊሺያው በወሎ በኩል ረገፈ። ቆቦም፣ ላሊበላም ተያዘች ወልዲያም፣ ደሴም ኮምፖልቻም ወደቁ። ወያኔዎች ሸዋ ሮቢት ደረሱ። እንደገና ዶር ዐብይ የሸሚዛቸውን እጄጌ ስብስበው ለ15 ቀናት ወደ ውጊያ ገቡ። ህዝቡም ዘር ሀይማኖት ሳይለይ፣ “ተመልከት ዓላማህን፣ ተከተል አለቃህን!” በሚባለው ከአባቶቹ በወረሰው ጀግንነት መሪውን ተከትሎ ሆ ብሎ ተነሳ። የዐብይ ዝና በአገሪቱ እንደገና ገነነ። ዐብይ እንደቀድሞ መሪዎች፣ እንደአባቶቻቸው ጦር ሜዳ ገቡዋ! ውጭ ያለነውም ተጠናክረን የአውሮፓና የአሜርካ ከተሞችን ቀወጥናት። የምዕራባውያንም የውሸት ሚዲያ ተጋፈጥን። ከውስጥም ከውጭም ተረባረብን። ወያኔ በሚይስደንቅ ፍጥነት ቀኟ ኋላ ዙራ ፍርጥጣ በ15 ቀን ውስጥ ሬሳዋንም መሣሪያዋንም እያዝረከረከች፣ አላማጣን አልፋ ኮረም ደረሰች። የመከላከያ ሠራዊት ትግራይ ገብቶ ይጫርሳታል ብለን ስንጠብቅ ጦራችን ዋጃ ላይ እንዲቆም ተደረገና፣ ወያኔን ለሁለተኛ ጊዜ ለዕርቀሰላም ልመና ተገባ።

እንደመሰለኝ ከሆነ ይኸ ሁሉ ውሀ ቅዳ ውሀ መልስ፣ የኦሮሞ ብሔርተኞች፣ የትግራይን ብሔርተኞች ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ አከርካሪያቸውን መምታት፣ እንደሞት የሚፈርቱን አማራውን ያጠናክራል ብለው የፈሩ ይመስላል። ከላይ የትግሬ ጽንፈኞች አማራውንና አፋሩን ሲጨፈጭፉ፣ መንግሥት ሸኔ የሚለው የኦሮሞ ነጻ አውጪ ሠራዊት በወለጋና በሌሎች ቦታዎች የሚኖሩትን መጨፍጨፉን አልገታም ነበር። የሁላችንም አዕምሮ በሰሜኑ ጦርነት ላይ አትኩሮ ስለነበረ፣ እስከዛሬ ስንት አማራ በኦሮሚያ እንድተገደለና አንድተሰደደ ገና ቁጥሩን አላወቅንም። የኦሮሞው መንግሥት የድፍረቱ ድፍረት ስንት መስዋዕትነት ተከፍሎ በህይወት የተያዙትን ቆንጮ የሕወትሀት መሪዎች፣ እነስብሀት ነጋን ሲፈቱ፣ ያኔ ነበር ለኔ የበቁኝ።

ወያኔ ትንሽ እፎይታ ከወሰደች በኋላ፣ የተሰጣትን የዕርቀሰላም ዕድል ረግጣ 3ኛ ዙር ወረራ ጀመረች። የፈረደብትን ቆቦን በቀናት ውስጥ ብትይዝም፣ ወልዲያን መያዝ አቃታት። አማሮቹ፣ ከተወሰኑ መከላከያዎች ጋር ገትረው ያዟት። እንደበፊቱ መንገዱ አልጋ በአልጋ አልሆነላቸውም። መከላከያው ወያኔዎች ባላሰቡት መንገድ ከኋላ መታቸው። የትግራይ ከተሞች አንድ በአንድ እየወደቁ፣ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት መቀሌ ደጃፍ ደረሰ። ወያኔ አድኑኝ ብላ ወደ ጌቶቿ፣ ወደ አሜሪካና አውሮጳ ለቅሶ ገባች። የወያኔም ጦር ከቆቦና፣ ከዋጃ፣ ከአላማጣ ፈርጥጣ ወጣች። ወያኔም “የምን ዕርቅ” ስትል የነበረችው፣ ያለምንም ቅደመ ሁኔታ እንቀበላለን ብላ አወጀት። ወያኔም ወደ ፕሪቶሪያም አሜሪካኖት መሪዎቿን ወስደው፣ አስታረቅን ብለው፣ መቀሌን ታደጓት። እንግዲህ ወያኔና ብልጽግና፣ እንደገና አሸሻ ገዳሜ ፍቅር ላይ ናቸው። በአማራ ግን፣ ፋኖውን መሣሪያ ለማስፈታት ማሳደዱና በጅምላ ማሠሩ ቀጥሏል። ስሞኑን የኦሮሞ ጽንፈኞች ቤተክርሲያናችንን ከውስጥ ሲነድሏት፣ እኔጌታቸው ረዳ የመጡት ዶ/ር ዐብይን እንኳን ድስ አለዎት ሊሉ ነው?

አሁን በዓይኔ መጣሽ!

የሰሞኑ፣ የኦሮሞ “ሆንዱምቱ ኬኛዎች”፣ ዓይን ያወጣ ድርጊት ፈጽመዋል። የማይነካውን ነክተዋል። በኦርቶዶክ ቤተክርስቲያን ላይ ያደረጉት፣ ጽንፍ የረገጠ ሕገ ወጥነት ዓይናውጣነትና፣ በኢትዮጵያ ላይ የተሰነዘረ ወንጀል ነው። የጠቅላይ ሚኒስቴሩ፣ አቋም የመንግሥታቸው እጅ በዚህ ወራዳ ሥራ መኖር ከሚናገሩትና የጽጥታ ክፍላቸው ከሚውስደው እርምጃ፣ ይታወቃል። ምናልባት መንግሥቱ ኃይለማሪያም ነባሩን ፓትርያርክ ገድሎ፣ የራሱን ፓትርያርክ እንደሾመ፣ መለስ ዜናዊ መንበር ላይ የነበሩትን እንዲሰደዱ ካደረግ በኋላ የእርሱን ፓትርያርክ እንደሾመ፣ እሳቸውም በተራቸው፣ የራሳቸውን ፓትርያርክ መሾም አምሯቸው ይሆን? አባ ሳዊሮስ ወይም አቶ አካለወልድን መደገፋቸው ያን አይመስልም? የማስፈራሪያ ንግግራቸው በጣም የኦርቶዶክስ ዕምነትን ተከታዮችን ያሳዘነ ነው። የሚግርም ነገር ነው የምንሰማው። በጦርነት ላይ እያለን፣ “የትርግራይ ኦርቶዶክስ ቤትክርስቲያንና የእስልምና ሀይምኖት ጽህፈት ቤቶች ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ተለይቻለሁ ስትል፣ ምንም አላላችሁም። ይኸ ኦሮሞ ጠሊታነት ነው” ለማለት ሞክረዋል። “እኛ እኮ፣ እንደ ደርግም ፓትርያርኩን አልገደልንም፣ ወይም እንደወያኔ አላሳደድንም፣ ምናለ ፓትርያርኩ እንዳሉ እነዚህ እራሳቸውን ከቀኖና ውጪ እራሳቸውን ፓትርያርክ አድርገው የሾሙትን ሳዊሮስና ጳጳሳችን በእርቅ አብራችሁ ጎን ለጎን አትሆኑም ዓይነት ነግግር አደረጉልን። መሠረታቸውም፣ ሁለት ፓትርያርክ በአንድ ጊዜ መንበር ላይ ነበሩ፣ ለማለት ዳድቷቸዋል። ያንን ለቤተክርስቲያኗ ልተውና፣ የዶክተር ዐብይ መንግሥት እጅ በመፈንቅለ ሲኖዱሱ አንዳለ ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ። ሁሉም ድርጊታቸው ያንን ነዋ የሚያመለክተው።

ስለነዚህ ሰዎች እስቲ ትንሽ እንበል። ስለ አባ ሳዊሮስ ብዙ የሚነገር ነገር ቢኖርም፣ አሉባልታን ትቼ፣ በአንድ የአሜሪካ ቤተክርስቲያን ውስጥ “ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ኦሮሚያ ውስጥ ተቀባይነትን የላትም” ሲሉ ሰምቼ አዝኜባቸዋለሁ። ስለዚህ ጸረ ኦርቶዶክስ እንደሆኑ ነው የሚሰማኝ። እንዲያው ትኩር ብዬ ሳያቸው፣ ምንም የፓትሪያርክነት ሞገስ የላቸውም። የሆኑ ጎረምሳ እኮ ናቸው። አንድ ጳጳስ ሲናገሩ፣ ሀገር ስብክታቸውን ትተው አዲስ አበባ ሲያውደለድሉ ነው የሚውሉት አሉ። አይ ጵጵስና! እንዲህ ተዋረዶ አረፈው። አዲስ አበባ ገዳም መሆኑ ነው?

ስለአባ ዜና ማርቆስ በተጨባጭ የማውቀ ነገር ስለሌላ ምንም ማለት አልችልም። ከዚህ በፊት አላውቃቸውም።

ከቆሙስነት ስለተሾሙት ጳጳሳትና ኤጵስ ቆፖሳት ብዙ ማለት ይቻላል። የሆኑ ጎረምሶች ናቸው። ከመሀላቸውም፣ በፍጹም የመንኩሴነት ማዕረግ ያልነበራቸው፣ እንዳሉበት መረጃ በገፍ እየደረሰን ነው። እግዚኦ መሀረነ ክርስቶስ። ሳይበቁ መመንኮስ፣ ሳይገባቸው መጰጰስም ይቻላል ለካ።

ሌላው ቆብ የጫኑ ነውረኛ ሰው፣ አባ ኤውስጣቲዎስ የተባሉት ግለሰብ ናቸው። ከ10 ዓመት በፊት የአባ ኢዎስጣቴዎስን አስነዋሪ ድርጊት ከሜሪካ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን (The Orthodox Church in America) በቅዱስ ቲኮን ሰሚናሪ (St Tikhon’ Seminary) በሚማሩበት ጊዜ ሁለት የሴት ጉደኞችን እያፈራረቁና፣ ከሊሎችም ጋር ፍትወት እንደሚፈጽሙ ተረጋግጦ እንደተባረሩ፣ እንዲሁም እኚህ ሰው፣ አስገድዶ የመድፈርን ያካተተ የወሲብ ቀበኛ (sexual predator) በመሆናቸው ሴቶች አካባቢ እንዳይደርሱ የሚያስጠነቅቅ ለአቡነ ዘካሪያስ፣ የኒው ዮርክ አገረ ስብከት የተጻፈ ደብዳቤ ደርሶኝ ነበር። ሲኖዶሱ እርምጃ ይወስዳል ብዬ ስጠብቅ ጭራሹኑ ብጹዕ ወቅዱስ ብሎ ሾመቻቸው። ሰሞኑን እኚሁ ሰው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶን ቤተክርሲያን ከውስጥ ከነደሏት ሶስት “መነኮሳት ነን” ባዮች አንዱ ሁነው ተገኙ።

ምስኪን የኦሮሞ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አማኞች እነኚህ በሞራል የዘቀጡ ሰዎች እንምራቸው ብለው በጉልበት ሲመጡባቸው ምን ይሰማችሁ ይሆን?



በመንግሥት የጸጥታ ጠባቂዎች አጃቢነት፣ ወለጋ ውስጥ፣ አንድ የቤተክርስቲያን ቁልፍ ሰብረው ገብተው በእንሊዝኛ ሲያስተምሩ በቪዲዮ አንዱን ጳጳስ ነኝ ባይ አይቼ፣ የወለጋ ምዕምናን እንግሊዚኛ ነው እንዴ የሚናገሩት ብዬ ጉድ አልኩ። በአረቢኛም እንዲሁ ሲያስተምሩ አየሁ። እንደጴንጤዎቹ በልሳን መናገራቸው ይሆን?

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማንም የካቢኔ አባል መሀላቸው እንዳይገባ ሲሉ ቀጭን ትዕዛዝ ሲያስተላፉ ሰማኋቸው። ይገርማል። ሕገወጦቹን ግን የጸጥታ ጠባቂዎቻቸው በሙሉ ጥበቃ እያጀቧቸው፣ ቤተክርስቲያን ሲያሰብሩ አይተናቸዋል። ጂማ ደብረ መዌዕ በድኃኔዓለም እና እንዲሁም የሻሻማኔው ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን የኦሮሞ ብልጽግና “የጸጥታ ጠባቂዎች” ተብዬዎች ቁልፎቹን ሰብረው ቤተክርስቲያኖቹን ለሕገ ወጡ መፈንቅለ ሲኖዶስ ወንጀለኞች ሲአስረክቡ ምዕምኑ በዕንባ እየተራጨ ተመልክቷል። በሻሻማኔ የጸጥታ ጥበቃቸው ዛሬ ቤተክርስቲያናቸውን ለመጠበቅ ከወጡት የመንግሥት ስናይፐሮች ብዙ ምዕምናን በጭካኔ ገድለዋል። ደማቸውን ከብልጽግና እጅ እንጠይቃለን። በአርሲና በተለያዩ ቦታዎች ያሉትን የሕጋዊ ቤተክርስቲያኗ ተሿሚዎችን እያፈኑ ሲያስዷቸውና ሲያዋክቧቸው እያየን ነው። መንግሥት ጭሬም ልደታማሪያም መእምናን በጪስ አፍነው ተኩስ ከፍተውባቸዋል። አቡነ ያሬድ፣ ሊቀ ሕሩያን ታምራት ወልዴ፣ ሊቀ ልሳናት ቀሲስ ወንድወሠን ጥላሁን፣ መምህር ሰሎሞን ዘገየ፣ አቡነ እስጢፋኖስ፣ መጋቢ ጸጋዘአብ አዱኟ... በዛሬው ዕለት ደሞ ሻሻሻማኔ የመንግሥት ጸጥታ ኃይል ተወስደዋል። ምናልባት፣ ካቢኒያቸው  በጸረ ኦርቶዶክስ የተጠቀጠቅ ካልሆነ፣ በዝምታ ማለፉ ከወንጀለኞች ጋር መተባበር ነው። ሌላ የእርስ በርስ ጦርነት ጠብቁ። ዝም ብሎ የሚሞትላቸው የለም። መከልከያ ውስጥ ብዙ ዘመዶቻቸው የሚገደሉባቸው መኖራቸውን መርሳት ሞኝነት ነው።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስን በዚህ መልኩ መናድ፣ ማለት ለኔ በግሌ በዓይኔ እንደመጡብኝ ነው የምቆጥረው። ቁጭ ብሎ ማየት ማንም አይችልም። ፕሮቴስታንቱም፣ እስላሙም፣ ነግ በኔ ብሎ ድምጹን እያሰማ ነው። ያንን ድምጽ ማፈን አይቻልም። እንደወያኔ ያንን ለማፈን መግደል ማንግላታት፣ የወያኔ ጽዋ ለመቀብል ሕዝቡን ማመቻችት ማለት ነው። በዓይናችን መጥታችኋል። ስትነቁርን ዝም አንላችሁም። ታረሙ!

በነገራችን ላይ፣ እነዚህ ቆብ የደፉት፣ ነውረኞች፣ ለኦሮሞ ብቻ አልነበረም፣ ጳጳስ ሾምን የሚሉት። ለጉራጌ ሶዶ ሀገርስብከት ቆሙስ አባ ወልደገብሬል ዮሐንስ የሚባሉትን አቡነ ጢሞቲዎስ ብለው ሹመውላቸዋል። ለካምባታ ሀገረስብከት ቆሙስ አባ ሚካኤል ገብረማርያም ይባሉ የነበሩትን ብጹእ አቡነ ኤልሳ ብለው ሹመውላቸዋል። ለካፋ ሀገረስብከት፣ ቆሙስ አባ ኃይለ እየሱስ መንግሥቱ የሚባሉትን አቡነ እዝራ ብለው ሹመውላቸዋል። ለሃዲያ ሀገረስብከት ቆሙስ አባ ጳውሎስ ከበደ ይባሉ የነበሩትን አቡነ ዳኒኤል ብለው ሹመውላቸዋል። ለዳውሮ ኮንታ ሀገር ስብከት ቆሙስ አባ አብርሀም መስቀሌ ይባሉ የነበሩትን አቡነ ኒቂዲሞስ ብለው ሹመውላቸዋል። ለጊዴዎ ገርጂ አማሮ ዞን ሀገረስብከት ቆሙስ አባ መርሀጽድቅ ኃይለማርያም የነበሩትን አቡነ ልብሲዮስ ብለው ሹመውላቸዋል። ለጎፋ በስኬቶ አገረ ስብከት ቆሙስ አባ ገብረማርያም ገብረመድኅን የተባሉትን ብጹዕ አቡነ ኡራኤል ብሎ ሹሞላቸዋል።

ይኸ በወጣ ሰዓታት ውስጥ ኦነግ፣ የማህበራዊ ደረ-ገጽን ፕሮፋየል (አርማ እንበለው) በዚህ መልኩ ቀይሮታል። ምን ችግር አለ። አባቱ ዳኛ፣ ልጁ ቀማኛ!



ማጠቃለያ

የማጠቃልለው ደሜ ከደማቸው ለተደባለቀው ለኦሮሞ አባቶችና እናቶች፣ እንዲሁም ወንድሞች እህቶች ነው። ጽንፈኞቹን የሠራችሁትን ነውር ነው አቁም በሏቸው። በናንተ ስም ወንጀል እየተሠራ ነው። አንድ ነገር ልበል። በአድዋ ጦርነት ጊዜ የኦሮሞ የጦር መሪዎች አኩሪ ገድል ፈጽመው፣ ጣሊያንን እንዳባረሩና እንዳዋረዱ ታሪክ የመሰክራል። ያንን ታሪክ የሚያረክስ አጥንታቸው ይወጋቸዋል። ከአሥራ ሁሉቱ ዋና ዋና የአድዋ ጦር መሪዎች ሰባቱ ዕውቀን ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲናግዴን ጨምሮ ኦሮሞዎች ነበሩ። ያንን አኩሪ ተጋድሎ ያየ ጣሊያን፣ ከ40 ዓመት በኋላ፣ ጦሩን በዘማናዊ መልክ አድራጅቶ፣ የኢትዮጵያን ታሪክ አጥንቶ፣ ትልቅ ታክቲክና ስትራተጂ ነድፎ በ1928 ሊዘምትብን ሲናሳ፣ ከታሪክ እንዳነበብኩት፣ ኦሮሞዎችን በአማራው ላይ አስነስቶ በጎኑ ለማቆምና የክህደት ወንጀል በሰፊው እንደፈጽሙ  ማነሳሳት ነበር። ከትግራይ ተባባሪዎች አንዳንድ እንደ ኃይለሥላሴ ጉግሳና፣ የመልስ ዜናዊ አያት እንደባሻ አስረስ ያሉትን መመልመል ቢችልም ከኦሮሞ ግን አልቀናውም ማለት ይቻላል። ብዙ የኦሮሞ አርበኞች ጣሊያንን ዛፍ ያጣ ጉሬዛ አድርገውት ነበር። ከነዚህ የኔ ጀግና ደጃዝማች ገረሱ ዹኪ ነበሩ!

አይጎነጎንም፣ የፈረሱ ጭራ፣
ለሰንደቁ ታማኝ፣ ገረሱ አባ ቦራ።

ተብለው የተወደሱ! ደጃዝማች ገረሱ ኪ፣ አምስቷን ዓመት ጣሊያንን መግቢያ መውጫ ያሳጡት፣ ገድላቸው በወርቅ ቀለም ተጽፎ ከትውልድ ትውልድ ሲዘከር ይኖራል። አዲሱ የኦሮሞ ትውልድ፣ ያንን ገድል እንዳያቆሽሽ አባቶች ልጆቻችሁን ምከሯቸው!

ከሰላሌ፣ እነአቢቹ የሚመሩት፣ እስከመጨረሻዋ ሰዓት ድረስ ወጣቶችን አሰልፈው፣ ሲፋለሙት፣ ዓምስቷን አመት ጨርሰው፣ የአበሻ ጀብዱ ተብሎ በፈረንጆቹ ሳይቀር ተምስክሮላቸዋል። አዲሱ ትውልድ፣ የአቢቹ አጽም እንዳይወጋህ፣ ከክህደት እራስህን አርቅ። ጄኔራል ጃከማ ኬሎን ቅርብ ቀን ነው ያጣናቸው። በታሪካችን ግን ወጣትነታቸው የሰው ታላቅ የኦሮሞ ኢትዮጵያዊ አርበኛና የጦር ጄነራልን መካድ አይቻልም።

 የእነ ኮሎኔል አብዲሳ አጋማ ገድል መቼ ተውስቶ ያልቃል። የበረሀው ተኩላ ተብለው፣ በአውሮጳ ምድር እነማርሻል ቲቶን እየመሩ የኢትዮጵያን ጀግንነት አስመስክረዋል።

ከጥሩ ዘር አንዳንድ እንክርዳድ እንደማይጠፋ፣ ከኦሮሞ መሀል፣ አንድ ከሀዲ ብቻ እንዳገኙ ጣሊያኖቹ በሮም ወመዘክር ጽፈው አስቀምጠዋል። ጣሊያኖች ጂማ ሲገቡ፣ የተቀባላቸው፣ አባ ጆቢር ወይም አባ ጆቢራ የተባለ ባላባት ነበር። ታርኩን፣ ወልቃይቴው የታሪክ ተመራማሪ አቶ በሪሁን ከበደ፣ እንዲህ ሲሉ ጽፈው አስቀምጠዋል።

ጅማ ጣሊያን እንደገባ፣ የጅማ ባላባት አባ ጆቢራ አብዱላሂ፣ የአማራን አንድ አንገት ቆርጦ ለአቀረበ 30 የጠገራ ብር ይከፈለዋል ብሎ ስለአወጀ 30 የአማራ አንገት ተቆርጦ ቀርቦለታል።[v]

በኢዮጵያ ታሪክ፣ የኦሮሞን አንጸባራቂ ሚና፣ ተውስቶ አያልቅም። በየአንዳንዱ፣ ኢትዮጵያ ላይ የተሰነዘሩትን ጥቃቶች ለመመክት፣ ከወለጋ፣ ከኢሉባቦር፣ ከባሌ፣ ከሐረር ለኢትዮጵያ ደማቸውን ያፈሰሱና አጥንታቸውን የከሰከሱ፣ ጀግኖች ሞልተውናል። በቅርቡ እንኳን፣ ሞፈርና ቀንበሩን ሰቅሎ፣ ከወለጋ ገስግሦ ሚሊሺያውን ተቀላቅሎ፣ ሶማሌ ላይ አኩሪ ድል ያስመዘገበውን የጦር ሜዳ ጀብዱ ሜዳሊያ ተሸላሚ፣ አሊ በርኬን እናስታውሳለን። ያ ሁሉ በጦር ሜዳ ጀብዱ ነው። በኃይማኖታችንስ? በሀይማኖቻን መጠንቀቅ የሚኖርብን ትልቅ ግዝት አለብን። ግዝቱም ከታላቁ፣ ሰማዕት አባታችን ከአቡነ ጴጥሮስ ነው። አቡነ ጴጥሮስ ከመጀመሪያዎቹ አራቱ የኢትዮጵያ ጳጳሳት አንዱ ነበሩ። ሰማዕቱ አባታችን፣ ብጹዕ ወቀዱስ አቡነ ጴጥሮስ በ1885 ዓመት ምህረት በፊቼ ነበር የተወለዱት። ዓለማዊ ስማቸው ማጋርሳ በዻሳ ነበር።



ሕዝቡ የፋሺስት ጣሊያንን አገዛዝ እንዲቀብሉ እንዲስብኩና ከመሞት እንዲተርፉ ሲጠይቃቸው እኚህ አባታችን ወደ ህዝቡ ዙረው ፋሺሽቶች የአገራችንን አርበኞች ሽፍታ ቢሉ እውነት እንዳይመስላችሁ። ሽፍታ ማለት ያለአገሩ መጥቶ የሰውን አገር የሚወር ይህ በመካከላችሁ የሚገኘው አረመኔው የኢጣሊያ ፋሺሽት ነው! የኢትዮጵያ ሕዝብ ለርሱ እንዳይገዛ ውጉዝ ነው! የኢትዮጵያ መሬት እንዳትቀበለው የተገዘተች ትሁን!” ብለው ደረታቸውን ለጥይት ሰጥተው ተሰውተዋል። የሰማዕቱ የአቡነ ጴጥሮስ የሞቱላትን ቤትክርስትያንና ሀገርን ለሚክድ ትልቅ ውግዘት አለበት። በረከታቸው በላያችን ላይ ይደር።

ስለዚህ፣ የኦሮሞ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አባቶች፣ ሕዝባችሁን ከመሳሳት እንድትመክሩ እለምናለሁ። ሲኖዶሱ፣ ያደረገው ትክክል፣ ይመስለኛል። በአንደኛው ቆሮንጦስ፣ ምዕራፍ 5 ቁጥር 13 ላይ ባለው መሠረት “ክፉውን ከመካከላችኹ አውጡት።” እነዚህ ሲኖዶሱን ከውስጥ የነደሉት ሰዎች፣ ክፉ ሥራ ሠርተዋልና፣ በጊዜውም ንሰሀ ገብተው አልተመለሱምና፣ ታይቶ ተሰምቶ በማይታወቅ መንገድ መፈንቅለ ሲኖዶስ አድርገዋልና፣ መወገዛቸውና መወገዳቸው ትክክል  ነው ብዬ እንደ አንድ ምዕምን አምንበታለሁ።

ምስጋና ለእግዚአብሔር ይሁን።

“.., ንስሐም ካልገባህ መቅረዝህን ከስፍራው እውስድብሀለሁ::” ብሎ ይጨርሳል የዮሐንስ ራዕይ መዕራፍ 2 ቁጥር 5

 

 



[i] Abyssinia: The Powder Barrel, 1935

[ii] Savage Abyssinia, 1928

[iii] የሺመልስ አብዲሳ ቃል

[v][v][v][v][v] የአጼ ኃይለሥላሴ ታሪክ፣ በሪሁን ከበደ፣ አዲስ አበባ 1993 ገጽ 804